1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የመለያ ምርጫ በአፍጋኒስታን

ዓርብ፣ ግንቦት 8 2006

አፍጋኒስታን በሚያዝያ ወር ባካሄደችዉ ፕሬዝደንታዊ ምርጫ የብዙሃኑን አብላጫ ድምፅ ያገኘ ተፎካካሪ ባለመኖሩ የመለያ ምርጫ ለማካሄድ ወሰነች። የመለያ ምርጫዉ ለፊታችን ሰኔ 17 2006ዓ,ም እንዲካሄድ የአፍጋኒስታን የምርጫ ኮሚሽን ትናንት ወስኗል።

https://p.dw.com/p/1C1NB
Woche des Buches in Afghanistan
ምስል DW/H. Sirat

«የምርጫ ኮሚሽኑ እንዳረጋገጠዉ በአፍጋኒስታን ሕገ መንግስት አንቀፅ 61 እንዲሁም በምርጫ ሕጉ አንቀፅ 20 እንደሚለዉ ከተፎካካሪዎቹ አንዱም ከ50 በመቶ ድምፅ በላይ ስላላገኙ የመለያ ምርጫ ይካሄዳል። ድጋሚዉ ምርጫ በዚሁ ዓመት ሰኔ 17ቀን ይሆናል። ዶክተር አብዱላ አብዱላ 45 በመቶ ድምፅ፣ ዶክተር አሽራፍ ጋህኒ አህማድዛይ 31,6 በመቶ እንዲሁም ዶክተር ዛልሚ ራሱል 11,4 በመቶ ድምፅ ነዉ ያገኙት።»

የአፍጋኒስታን የምርጫ ኮሚሽን ኃላፊ ዩሱፍ ኑሪስታን ነበሩ ትናንት የመለያዉ ምርጫ መካሄድ እንደሚኖርበት የተላለፈዉን ዉሳኔ ከነምክንያቱ የገለፁት። ሁለቱ ለመለያ ምርጫ የሚቀርቡት እጩ ፕሬዝደንታዊ ተፎካካሪዎች በኋላ ታሪክና በአኗኗር ዘይቤያቸዉ ይለዩ እንጂ በያዟቸዉ ርዕሰ ጉዳዮች እጅም እንደማይለያዩ ነዉ የሚነገርላቸዉ። የቀድሞዉ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር አብዱላ አብዱላ በአፍጋኒስታኑ የፀረ ሶቭየት ኅብረት የሽምቅ ዉጊያ ታዋቂ የነበሩት አህመድ ሻህ ማሱድ አማካሪና ቃል አቀባይ ነበሩ። አህመድ ማሱድ ከጎርጎሪዮሳዊዉ መስከረም 11 2001 የአሸባሪዎች ጥቃት ሁለት ቀን በፊት ነዉ በአልቃይዳ የተገደሉት። ኮኖምቢያ ዩኒቨርሲቲ የተማሩት የገንዘብ ሚኒስትር የነበሩት አሽራፍ ጋህኒ አህማድዛይ ደግሞ የስነሰብ ተመራማሪና በ1990ዎቹ በዓለም ባንክ ተቀጥረዉ አገልግለዋል። ሁለቱም በምርጫዉ ማሸነፉ ከተሳካልን የያዝነዉ ጎርጎሪዮሳዊ ዓመት ሲያበቃ የዩናይትድ ስቴትስ ወታደሮች አፍጋኒስታን እንዲቆዩ የሚፈቅደዉን ስምምነት እንፈርማለን እያሉ ነዉ። በሀገሪቱም ሰላም እንዲሰፍን አስፈላጊዉን ሁሉ ለማድርግ መዘጋጀታቸዉን በምርጫ ቅስቀሳ ወቅት ደጋግመዉ ገልጸዋል፤ ይህን ለማድረግ የሚያስችላቸዉን ዝርዝር ባይናገሩም። ከታሊባን ጋ ስለሚኖረዉ ዉይይት ወይም የአፍጋኒስታን አሜሪካን ግንኙነት እንዴት ሊቀጥል እንደሚችል ያቀረቡት የተለየ ሃሳብ ሳይኖርም የአፍጋኒስታን ሕዝብ ከፕሬዝደንት ኻሚድ ኻርዛይ በኋላ ሀገር የሚመራዉን ሰዉ ለመለየት ሰኔ 17 ወደምርጫ ጣቢያዎች ሄዶ ዳግም ድምፁን እንዲሰጥ ከወዲሁ ተጋብዟል። መምረጥ ከሚችለዉ 7 ሚሊዮን አፍጋናዊ 60 በመቶዉ ባለፈዉ ሚያዝና የታሊባንን የጥቃት ዛቻ ወደጎን ብሎ ድምፁን ሰጥቷል። ለአብዱላ አብዱላ የመለያ ምርጫዉ ከአምስት ዓመት በፊት ከነበረዉ የቀጠለ ነዉ የሚለስለዉ። ያኔም ከኻርዛይ ጋ ለተመሳሳይ ምርጫ ቀርበዉ ነበር ሆኖም በወቅቱ ከፍተኛ ማጭበርበር ተፈጽሟል በማለት ከዉድድሩ በመዉጣታቸዉ አጋጣሚዉን ለተፎካካሪያቸዉ ቀላል እንዳደረጉላቸዉ አይዘነጋም። ይህኛዉ የመለያ ምርጫ በተቃራኒዉ ጠንከር ያለ ፉክክር እንደሚታይበት ነዉ የሚገመተዉ ምንም እንኳን የጎሳ ጉዳይ ስፍራ ሊኖረዉ ይችላል። የ53ዓመቱ አብዱላ የፓሽቱና ታጂክ ቤተሰብ የተገኙ ናቸዉ፤ የ64ዓመቱ አህመድዛይ ደግሞ ፓሽቱ። ጉዳዩን በቅርበት የሚከታተሉ ወገኖች በዚህኛዉ የመለያ ምርጫ አብዱላ የኋላ ታሪካቸዉ ሊረዳቸዉ እንደሚችል ግምታቸዉን ይሰነዝራሉ። አብዛኛዉ የሀገሬዉ ሰዉ የሰላይ አየር የመተንፈስ ምኞቱ ከፍተኛ በመሆኑም በፀረ ታሊባን ዉጊያ ተሳትፏቸዉ ለሚታወቁት እጩ ፕሬዝደንታዊ ተፎካካሪ ዶክተር አብዱላ በዚህ ወገን መሰለፋቸዉ የብዙሃኑን ድምፅ ለማግኘት ይረዳቸዉ ይላሉ ዋሽንግተን የሚገኘዉ የዉድሮዉ ዊልሰን ማዕከል የደቡብ እስያ ጉዳዮች ተንታኝ ማይክል ኩግልማን። በሌላ በኩል ደግሞ አብዱላ ምንም እንኳን ከፓሽቱ ቢወለዱም ታጂኮች ከሚበረክቱበት ከሰሜኑ ወገን በመሆናቸዉ ደቡቡን የሚወክሉት ፓሽቱዎች ሙሉ በሙሉ ፍላጎታችን በእሳቸዉ ይሟላል የሚል እምነት እንደሌላቸዉ ይነገራል።

Straßenszene Kabul
ምስል Jennifer Collins
Afghanistan Präsidentschaftskandidat Abdullah Abdullah
ዶክተር አብዱላ አብዱላምስል picture-alliance/dpa

ይህን ስጋት ለማስወገድም ፖለቲከኛዉ የፓሽቱዎች ድጋፍ እንዳላቸዉ የሚነገርላቸዉን በሚያዝያዉ ፕሬዝደንታዊ ምርጫ ፉክክር በሶስተኛነት ያጠናቀቁትን ሳልሚ ራሱልን ፖለቲካዊ ድጋፍ አረጋግጠዋል። አብዱላ እና ራሱል በኻርዛይ የቅርብ ወዳጅነታቸዉ ይታወቃሉ። ሌላኛዉ የመለያ ምርጫ ተፎካካሪ ጋህኒ ለረዥም ጊዜ በቆዩበት በሙያና እዉቀታቸዉ የሚተማመኑ ሲሆን ሙስናን በማጥፋት መልካም አስተዳደርን ለማስፈን እጥራለሁ የሚል መቀስቀሻቸዉ ምናልባትም ብዙ ድምፅ ላያተርፍላቸዉ እንደሚችል ነዉ ተንታኞች የሚናገሩት። በዚያም ሆነ በዚህ ሁለቱ እጩ ተወዳዳሪዎች በየግላቸዉ ያላቸዉን ተቀባይነት ይዘዉ ምናልባትም የጥምር መንግስት ሊመሠርቱ እንደሚችሉ ይገመታል።

ዋስላት ሃስራት ናዚሚ

ሸዋዬ ለገሠ

ነጋሽ መሐመድ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ