1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የመሬት አጠቃቀም ቅሬታ በአዲስ አበባ

Merga Yonas Bulaሐሙስ፣ ግንቦት 18 2008

በኢትዮጵያ መሬትና መሬት ነክ የሆኑ ጉዳዮች በማሕበረሰቡ እና በመንግስት መካከል ቁርሾ መፍጠር ከጀመሩ አመታት ተቆጥረዋል። ግንባታዎች ተገንብተዉ ከከረሙ በዋላ መንግስት «ህገወጥ» በማለት ያፈርሳቸዋል፣ወይም አካባቢዉ ለልማት ይፈለጋል በማለት ግንባታዉ እንዲፈርስ ነዋሪዎችም እንዲፈናቀሉ ይደረጋል። ከማሕበረሰቡ የሚሰማዉ ቅሬታም እየተደጋገመ ነዉ።

https://p.dw.com/p/1Iuwf
Stadtansicht von Addis Abeba, Äthiopien
ምስል picture-alliance/dpa/M. Kappeler

[No title]

ሰሞኑ በአዲስ አበባ ከተማ በተለያዩ ቦታዎች በነዋርዎች እና በፀጥታ አስከባሪዎች መሃል በተፈጠረ ግጭት የሰዉ ህይወት ማለፉን ዘገባዎች ይጠቁማሉ። ባለፈዉ ሳምንት በአዲስ አበባ ከተማ በወረዳ 12 የቦሌ ክፍለ ከተማ ነዋርዎች የሰሯቸዉ ቤቶች የከተማዉ መስተዳድር «ሕገወጥ ግንባታ ነዉ» ብሎ ለማፍረስ ሲሞክር ግጭት መፈጠሩን እና ግጭቱ በዚህ ሳምንት መቀጠሉም ይነገራል። በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ደግሞ በተለምዶ አሜሪካን ግቢ ተብሎ የሚጠራ አከባቢም መንግስት <<በመልሶ ማልማት>> ስም የአከባቢዉ ነዋርዎች መኖሪያቸዉን ለቅቀዉ እንድሄዱ መገደዳቸዉን እየተናገሩ ነዉ።


የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር <<መልሶ ማልማት>> ወይም Land Development Plan (LDP) የሚለዉ ዕቅዱ፤ አካባቢዎችን መልቀቅ ለሚገባቸዉ ነዋሪዎች ተገቢዉን ካሳና የንብረታቸዉን ዋጋ እንደሚከፍል፤ ተለዋጭ ቦታዎች እንደሚሰጣቸዉ፤ የገንዘብ አቅም ካላቸዉ ደግሞ እዛዉ ቦታቸዉ ላይ እንዲያለሙ እድል እንደሚሰጠቸዉ ያትታል። በልማቱ ስም በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች እንዲነሱ ተደርገዋል።በዕቅዱ የተገባዉ የካሳ፤ የንብረት ዋጋ እና ተለወጭ ቦታዎች የመግኘት ቃል ግን ተግባራዊ እንዳልሆነ የአሜርካን ግቢን ጨምሮ ከተለያዩ ቦታዎች የተነሱ ነዋሪዎች ቅሬታቸዉን ማሰማት ቀጥለዋል። ብዙ በተሰቦች ለከፋ ችግር መጋለጣቸዉን እየተናገሩም ነዉ።


የአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ 10 ወረዳዎች ያሉት ሲሆን 864 ሄክታር መሬት ላይ ሰፍሮ እንደሚገኝ ከአድስ አበባ ከተማ አስተዳደር የተገኘ መረጃ ያሳያል። ስለ መልሶ የማልማት ስራ በክፍለ ከተማዉ፤ በጣም ተጠጋግተዉ የሚኖሩት ነዋሪዎች ማንሳት ከባድ እንደሆነ ጉዳዩን በቅርበት ተከታትሎ እየዘገበ ያለዉ ጋዝጠኛ ዉዲኔ ዘነበ ለዶቼ ቬሌ ይናገራል።

ይለማል የተባለዉ ቦታ አጥር ታጥሮበት ከአራት ዓመት በላይ እንዳስቆጠረ ዘገባዎች ያሳያሉ።ይለማል የተባለዉ ቦታ ሳይለማ ብዙ ዓመት መቀመጡ ነዋርዎቹን በችኮላ፣ ያለተገቢ ካሳ እና ተለዋጭ ቦታ ማስነሳቱ ትርጉሙ ምንድነዉ ብሎ የሚጠይቁም አልጠፉም።


የአድስ ከተማ ክፍለ ከተማ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ቸርነት በላቸዉ መልሶ እየለማ ያለዉ አካባቢ በጣም የተጠጋጋ እንደሆነ እና አንድ ቤት ዉስጥ ሁለት ወይም ሶስት ቤተሴቦች ሲኖሩ የነበሩት አሁን ለየብቻቸዉ ቦታ ወይም ቤት እየተሰጠቸዉ መሆኑን ይናገራሉ። ካሳ ወይም ተለወጭ ቦታን በተመለከተ <<እዉነተኛ የሆነ ቅሬታ>> ቀርቦ አለየሁም ይላሉ አቶ ቸርነት።

አዲስ አበባ 54,000 ሄክታር ስፋት እንዳላት፣ ከዝህም ወደ 30, 000 ሄክታር የሚሆነዉ መሃል ከተማ እንደምገኝ እና አካባቢዉም ያረጀ በመሆኑ መንግስት በመልሶ ማልማት እቅድ እንዳካተተዉ ጋዜጠኛዉ ዉዲኔ ዘነበ ይናገራል።

መርጋ ዮናስ

ነጋሽ መሓመድ