1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የመን ልትፈራርስ  ነዉ፤ የተመድ ማስጠንቀቂያ

ሐሙስ፣ ግንቦት 24 2009

የተመድ የመን ልትፈራርስ ነዉ ሲል አስጠነቀቀ። የመንግስታቱ ድርጅት እንደሚለዉ ሀገሪቱ ላይ የሚታየዉ እልቂት ሰዉ ሰራሽ ሲሆን ዓለም ዝም ብሎ እያየነዉ። የመንግሥታቱ ድርጅት የአስቸኳይ ጊዜ ርዳታ ማስተባበሪያ በኮሌራ የተጠቁት ከ200,000 እንደሚበልጡ በማመልከት ለዓለም አቀፉ ኅብረተሰብ የእርዳታ ጥሪዉን አቅርቧል።

https://p.dw.com/p/2dzyB
Jemen Cholera
ምስል Reuters/A.Zeyad

UN-Jemen - MP3-Stereo

«ከተረሳችዉ የመን ነዉ የመጣሁት።» አሉ ራዲያ አልሙትዋከል ከእምባቸዉ ጋር እየታገሉ። ሂጃብ የተከናነቡት ከየመን የመጡት የመብት ተሟጋች በኒዉዮርክ የተመድ የፀጥታዉ ምክር ቤት አዳራሽ ዉስጥ ተቀምጠዋል። ለመብት የሚሟገተዉ ማዋታና የተባለዉ ድርጅት ባልደረባ፤ ልትፈራርስ ከተቃረበችዉ እና ተረስታለች ካሏት ሀገር መምጣታቸዉን በመናገር ጀመሩ።

«ሀገሬ ከመፈራረስ ደረጃ ላይ ትገኛለች። የየመን ሕዝብ ዓለም እየተመለከተ ለረሃብ፣ ለእጦት እና ለሞት ተጋልጧል።»

የሞቱ ሰዎች፣ ቁም ስቅል የደረሰባቸዉ፣ በዘፈቀደ ስለሚካሄደዉ ተኩስ፣  በትምህርት ቤቶች በሃኪም ቤቶች በመስኪዶች እና በገበያ ስፍራ ሳዉድ አረቢያ መራሹ ወታደራዊ የአየር ድብደባን የተመለከቱ ታሪኮች። ቤተሰቦቻቸዉ ሊንከባከቧቸዉና ሊመግቧቸዉ  ስለማይችሉ ብቻ በግዳጅ የሚዳሩ የአዳጊ ልጃገረዶች ታሪክ። የመን፣ በተዘነጋች ሀገር ዉስጥ የሚካሄድ ጦርነት። 

«የየመን ሕዝብ ዓለም እየተመለከተ ለረሃብ፣ ለእጦት እና ለሞት ተጋልጧል።»

Jemen Cholera
ምስል Getty Images/M.Huwais

የተመድ የሰብዓዊ ርዳታ ማስተባበሪያ ኦቻ ኃላፊ ስቴፋን ኦብሪያን ናቸዉ። የመን ላለፉት ሁለት ዓመታት በእርስ በርስ ጦርነት ታምሳለች፤ ሺዎች ሞተዋል፣ 17 ሚሊየን ሕዝብ የአስቸኳይ ጊዜ ርዳታ ፈላጊ ነዉ፤ ስድስት ሚሊየን ሕዝብ ለሞት ለሚያሰጋ ርሃብ ተጋልጧል። በዚህ ላይ ደግሞ ኮሌራ የሚያደርሰዉ ጉዳት ተጠናክሯል፤ የዓለም ሃገራት መሪዎች ደግሞ በፀጥታዉ ምክር ቤት ተሰብስበዋል በማለት የመን ተዘንግታለች የሚለዉን የመብት ተቆርቋሪዋን ሃሳብ አጠናክረዋል። 

«ቀዉሱ አሁን እየመጣ አይደለም፤ የተባባሰም አይደለም፤  እዚሁ እኛ እያየን ሰዎች እዚያ ዋጋ ሲከፍሉ ቆይተዋል። መረጃዎች እንደሚጠቁሙት በመጪዎቹ ስድስት ወራት አዳዲስ ታማሚዎቹ 150ሺህ እንደሚደርሱ ይገመታል፤ በዚህ ላይ ካለፈዉ ሚያዝያ አንስቶ ካሉት 60 ሺህ ሰዎች ጋር በዚህ ጉዳይ የሞቱት ቁጥር 500 ደርሷል።»

እንደመንግሥታት ድርጅቱ ባለስልጣን ኮሌራ፣ ረሃብ፣ ጦርነት መፍትሄ የሚሹ ሰዉ ሰራሽ አጣዳፊ ችግሮች ናቸዉ። እነዚህ ሦስቱም በአረብ ባህረ ሰላጤ በምትገኘዉ ደሀዋ የመንን ካለችበት ወደታች አዉርደዋታል። የመንግሥታቱ ድርጅት የሰብዓዊ ርዳታ አስተባባሪ ተቋም ኃላፊዉ ንግግር በፀጥታዉ ምክር ቤት አዳራሽ የተገኙትን ተሰብሳቢዎች ስሜት ነክቷል። ከዚህ የበለጠ ግን ያደረገዉ ነገር የለም። ሳዉድ አረቢያ መራሹ ጥምረት ከዩናይትድ ስቴትስ በተገዛ የጦር አዉሮፕላን እና መሣሪያ፤ የመንን ወደድንጋይ ዘመንነት እስክትቀየር ድረስ መደብደቡን፤ በኢራን የሚደገፉት የሁቲ አማፅያን እንቅስቃሴ ለአሸባሪ ቡድኖች በር መክፈቱን ግን እዚያ ከተገኙ ከ15 የፀጥታዉ ምክር ቤት አባላት አንዳቸዉም ትንፍሽ አላሉም። ስቴፋን ኦብሪያን ሁሉንም ተመለከቱ።

Jemen Kindersoldaten in Aden
ምስል Getty Images/AFP/S. Al-Obeidi

«ለዚህ ምክር ቤት ዛሬ ያቀረብኩትን መግለጫ በምፈጽምበት ጊዜ የመን ዉስጥ መከላከል በሚቻል በሽታ ሌላ ልጅ ሊሞት ይችላል። ጊዜዉ አሁን ነዉ።»

የተዘነጋዉን የየመን ቀዉስ አስመልክተዉ ለ14 ደቂቃ ንግግር ካደረጉ በኋላ ኦብሪያን ለዓለም ተማጽኗቸዉን አቅርበዋል። እዉነታዉ የመን በቅርቡ በዓለም ከፍተኛዉ የጤና እና የረሃብ እልቅት ሊያጋጥማት ይችላል፤ ይህ እንዳይከሰት የማድረጉ ከፍተኛ ኃላፊነት በተመድ ላይ የወደቀ ነዉ።

ጊዮርግ ሽቫርተ/ ሸዋዬ ለገሠ

ኂሩት መለሰ