1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የመካከለኛዉ ምሥራቅ ዉዝግብ

ሰኞ፣ መጋቢት 13 2002

የጠቅላይ ሚንስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ መንግሥት በሐይል በተያዙ ግዛቶች አዲስ የአይሁድ ሠፈራ መንደር ማሳነፁን ለአስር ወራት ያሕል እንደሚያቋርጥ ባለፈዉ ሕዳር ቃል ገብቶ ነበር።

https://p.dw.com/p/MZOI
የሞስኮ ጉባኤተኞችምስል AP


22 03 10


የዩናይትድ ስቴትስና የእስራኤልን ግንኙነት ለዘመናት አጣብቆ የያዘዉ የብረት ማገር ከሰፊ፣ጥልቅ፣ ጥብቅ ቁመት-ወርዱ ቅንጣቱን ያወረዛዉ ጠብታ ዝገት ባፍታ ተጠረገ።ጥብቁን ወዳጅነት የዘመን ሒደት፣የሰዉ ልጅ እድገት፣ የእዉቀት ስርፀት አደረጀዉ እንጂ በርግጥ አልሸረሸረዉም።፣ወዳጅነቱን ያጠበቀዉ የዘመን፣ የትዉልድ ለዉጥ እድገትም ሆነ የወዳጅነቱ ጥብቀት፣ ወዳጅነቱ አንድ ሲል እንዳዲስ አንድ ያለዉን የአረብ እስራኤሎችን ጠብ፣ ግጭት ጦርነት ከማወሳሰብ፣ ዉዝግብ ግጭቱን ለማስወገድ የሚደረገዉን ሽምግልና እየጣለ-ከማንሳት ባለፍ የተከረዉ በርግጥ የለም።ሰሞኑንም ነባሩ ወዳጅነት፣አሮጌዉ ግጭት ዉዝግብ፣ የተለመደዉ ጉባኤ ጉብኝት እንዳዲስ ናረ-ደራበት።መካከለኛዉ ምሥራቅ።ለኛም እንደገና አዲስ ርዕስችን ሆነ።ላፍታ አብራችሁኝ ቆዩ።

«ስድብ ነበር።ይሕ ምክትል ፕሬዝዳቱን ጭራሽ የማይገባቸዉ ስድብ ነበር።እሳቸዉ እዚያ የነበሩት የሰላም ሒደቱ እንዲሳካና ከእስራኤል ሕዝብ ጋር ላለዉ ወዳጅነት የግልፅ ቁርጠኝነት መልዕክት ይዘዉ ነበር።ግን እሳቸዉን ብቻ ሳይሆን ዩናይትድ ስቴትስን መስደብ ነዉ።»

ዩናይትድ ስቴትሷ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ሒላሪ ክሊንተን።ባለፈዉ ሳምንት ማክሰኞ።

እስራኤል በ1967 (ዘመኑ በሙሉ እንደ ጎርጎሮሳዉያኑ አቆጣጠር ነዉ) ከአረቦች ጋር በገጠመችዉ ጦርነት በሐይል በያዘችዉ የፍልስጤም ግዛት በገነባቻቸዉ አንድ መቶ ሠፈራ መንደር ከአምስት መቶ ሺሕ በላይ አይሁዳዉያንን አስፍራለች። የእስራኤል እርምጃ ለፍልስጤሞች የዘር-መኖሪያን ማሳጣት፣ ግዛትን መቀማት ነዉ።በአለም አቀፍ ደንብም ሕገ-ወጥ።

የአለም የሚባለዉን ሕግ ያስረቀቀ-ያስፀደቀዉ፣ ሕጉን አክብሬ፣ አስከብራለሁ፥ለሕዝብ ቆሚያለሁ፣ የሚለዉ ሐያል አለም፣ እስራኤል የፍልስጤሞችን መብት እንድትጠብቅ፥የራሱን ሕግ እንድታከብር ለማስገደድ የቃጣበት ጊዜ ከነበረ በርግጥ ጥቂት ነዉ።እስራኤልና ፍልስጤሞች የሰላም ድርድር ከጀመሩበት ከ1991 ወዲሕ ግን ለድርድሩ ስምረት እስራኤል የአይሁድ ሠፈራ መንደርን ሲሆን እንድታፈርስ ይሕ ቢቀር አዳዲስ እንዳትገነባ ሐያሉ አለም በተለይም የድርድሩም የአለምም መሪዋ፣የእስራኤል ጥብቅ ወዳጅዋ ዩናይትድ ስቴትስ በየጊዜዉ መጠየቋ አልቀረም።

Biden / Netanjahu / Jerusalem / Israel / USA
ባይደንና ኔታንያሁምስል AP

የፕሬዝዳት ባራክ ኦባማ መስተዳድርም እንደ ብዙ ቀዳሚዎቹ ባደረገዉ ግፊት የጠቅላይ ሚንስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ መንግሥት በሐይል በተያዙ ግዛቶች አዲስ የአይሁድ ሠፈራ መንደር ማሳነፁን ለአስር ወራት ያሕል እንደሚያቋርጥ ባለፈዉ ሕዳር ቃል ገብቶ ነበር።

የዛሬ-አስራ አምስት ቀን ሰኞ። እየሩሳሌም-ረመላሕ መሸ።የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚንስትር በማግስቱ ጠዋት ለሚቀበሏቸዉ ትልቅ እንግዳቸዉ የሚሉትን ያሰላስላሉ።የሐገር ዉስጥ ጉዳይ ሚንስትራቸዉ ኤሊ ይሻይ ግን ኔታንያሁ የመሩት ካቢኔ ያሳለፈዉን ትዕዛዝ ለማወጅ ዝግጅታቸዉን አጠናቀዋል።አቡ-መዝን ለትልቅ እንግዳቸዉ ወቀሳ የሚያቀርቡበትን ቀን ይናፍቃሉ።ሮብን።

ብራስልስ፣ ደንገዝገዝ ብሏል።-ወይዘሮ ካትሪን አሽተን እንደ አዉሮጳ ሕብረት ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ለመጀመሪያ ጊዜ ለሚያደርጉት ጉብኝት ያረቀቁትን ሥልት እየሩሳሌም-ረመላሕ ከሚሆነዉ ጋር ለማጣጣም ሲሉ በገሚስ ተዉት።ደግሞም ጊዜ አላቸዉ።አንድ ሳምንት።

ሞስኮ-ላይን ይዟል። የሩሲያዉ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ሰርጌይ ላቫሮቮ፧ ከአስር ቀን በሕዋላ የሚያስተናግዱት ስብሰባ ይዘትን ለመወሰን-ወደ እየሩሳሌም፥ ረመላሕ፥ ካይሮ ዋሽንግተን እንዳማተሩ ሰኞ መሸ።ኒዮርክ ጠዋት ነዉ። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ ፓን ጊ ሙን በሞስኮ-ጋዛ ጉብኝታቸዉ የሚሉትን ለማርቀቅ ዋሽግተን-ሞስኮ፣ ለንደን ብራስልስ፣ እየሩሳሌም-ረመላሕ የሚባል የሚሆነዉን እያሰላሱ ቢሯቸዉ ገቡ።

ማክሰኞ ዋሽንግተን ጎሕ ቀደደ።ኒዮርክም እንደዚያዉ።ብራስልስ እና ሞስኮ ረፍዷል። እንደእየሩሳሌም ቀትር ነዉ።ረመላሕም።ጆ ባይደንና ከጠቅላይ ሚንስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ ዉይይታቸዉን ጨርሰዉ ካዳራሹ ወጡ።ትልቁ እንግዳ-አሉም።

«የእስራኤልን ፀጥታ በተመለከተ በዩናይትድ ስቴትስና በእስራኤል መካካል ምንም አይነት ክፍተት የለም።በዚሕና በሌሎችም ብዙ ምክንያቶች የኢራን የኑክሌር መርሐ-ግብር የመስተዳድራችን ልዩ ትኩረት ነዉ።»

የፕሬዝዳን ባራክ ኦባማ መስተዳድር ከተመሠረተ ወዲሕ አንድ የዩናይትድ ስቴትስ ትልቅ ባለሥልጣን አካባቢዉን ሲገበኝ ባይደን የመጀመሪያዉ ናቸዉ።ጋዜጠኛ-ተንታኙ የትልቂቱ ሐገር ሁለተኛ ትልቅ መሪ ላሉት አፀፋ የኢራንን አፀፋ ለማግኘት አይን ጆሮዉን ቴሕራን ላይ እንደተለ፥ የእስራኤሉ የሐገር ዉስጥ ጉዳይ ሚንስትር ኤሊ ዪሻይ መንግሥታቸዉ ምሥራቃዊ እየሩሳሌም ዉስጥ አንድ ሺሕ ስድስት መቶ አዳዲስ የአይሁድ መኖሪያ ቤቶች እ ንዲገቡ ማዘዙን አስታወቁ።

Israel / Jerusalem / Unruhen
ግጭቱ-እየሩሳሌምምስል AP

የሕዳሩ ቃል ታጠፈ።የእስራኤልን እርምጃ ባይደን በማግስቱ አወገዙት።ክሊንተን ባለፈዉ ሳምንት ያሉትን ከማለታቸዉ ከአራት ቀን በፊት አርብ ጠቅላይ ሚንስትር ኔታንያሁ እቅዳቸዉን እንዲሰርዙ በሥልክ ጠይቀዋቸዉ ነበር።አልሆነም።ጠቅላይ ሚንስትር ኔታንያሁ ይብስ ብለዉ የመንግሥታቸዉን እርምጃ «ተገቢ» አሉት።ምሥራቅ እየሩሳሌምም-የእስራኤል እንደሆነች ትቀራለች።

«የአይሁዳዉያን ሠፈራ መንደር መመስረቱ የምሥራቅ እየሩሳሌም አረቦችን ኑሮ በምንም መልኩ አያዉክም።እነሱን የሚጎዳም አይደለም።ባሁኑ ጊዜ እየሩሳሌም ዉስጥ ከሚኖረዉ አይሁዳዊ ግማሽ ያህሉ የሚኖረዉ በዚሕ አካባቢ ነዉ።ለዚሕም ነዉ-ምንም እንኳን እዚሕ ቤት ዉስጥ የሐሳብ ልዩነት ቢኖርም በየትኛዉም የሰላም ሥምምነት ይሕ አካባቢ የእስራኤል መንግሥት አካል እንደሆነ መቅረት አለበት በሚለዉ ሐሳብ ምናልባትም ሙሉ በሙሉ መግባባት ያለዉ።»

ልዩ መልዕክተኛ ጆርጅ ሚቼል ባይደን የተነጋገሩበትን ደርዝ ለማስያዝ እሁድ ወደ መካከለኛዉ ምሥራቅ ሊሔዱ አቅደዉ ነበር።ቀሩ።

«ዉጪ ጉዳይ ሚንስትሯ በስልክ ሥላደረጉት ዉይይት የእስራኤሎች የነሱ ማለት የጠቅላይ ሚንስትሩ መልስ ምን እንደሆነ ሳንሰማ ጆርጅ ከዋሽንግተን የመሔዱ ፍሬያማነት ምንም አልሰማንም»
የዩናይትድ ስቴትሱ ዉጪ ጉዳይ ሚንስቴር ቃል አቀባይ ፊሊፕ ክሮዉሌይ።ማክሰኞ።የጥብቁ ወዳጅነት ድምቀት አንዳዴ ለቅፅበት እንደሚሆነዉ ሁሉ ደበዘዘ።የብሪታንያዉ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ዴቪድ ሚልባድ የዩናይትድ ስቴትስ አቻቸዉን ሐሳብ ለማጋራት አለመነቱም።ማክሰኞዉኑ የሊባኖሱ ጠቅላይ ሚንስትር ረፊቅ ሐሪሪ በርሊን ነበሩ።መራሒተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል ሐሪሪን ካነጋገሩ በኋላ እንዳሉት የባይደን-ክሊንተንን ያክልም ባይሆን የእስራኤል እርምጃ ሳያናድዳቸዉ አልቀረም።

«እኛ ምሥራቃዊ እየሩሳሌም ዉስጥ አዲስ መኖሪያ ቤቶች እንዲሰሩ መወሰኑ እስራኤልና ፍልስጤሞችን ለማቀራረብ የሚደረገዉን ዉይይት ከባድ ጥያቄ ዉስጥ የሚጥል እንቅፋት ነዉ (ብለን እናምናለን)።ከጠቅላይ ሚንስትር ኔትንያሁ ጋር ባደረግሁት የሥልክ ንግግርም ይሕንኑ ግልፅ አድርጌላቸዋለሁ።»

የሚሉ የሚያደርጉትን ካዲሱ ለወጥ ጋር አጣጥመዉ ወደ መካከለኛዉ ምሥራቅ የወረዱት የአዉሮጳ ሕብረት ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር-ካትሪን አሽተን ደማስቆ ነበሩ።

«ሥለ ሠፈራዉ ያለንን አቋም ግልፅ አድርገናል።መግለጫዉን አረጋግጣለሁ።ለአዉሮጳ ምክር ቤትም የተናገርኩት ይሕንኑ ነዉ።እስራኤል ይሕን እንዳታደርግ እንመኛለን።ይሁንና ድርድሩ ዉጤታማ በሚሆንበት ሁኔታ መስራት እንዳለብን አዉቃለሁ።»

የዋሽንግተን፥ ብራስልስ፥ ኒዮርክ ሹማምንታት በጠቅላይ ሚንስትር ኔታንያሁ መንግሥት እንደተበሳጩ፥ እርምጃዉን እንደተቃወሙ አራትዮሽ ላሉት ስብሰባ ሞስኮ ታደሙ።አርብ።ከስልሳ ዘመን በላይ የሚታወቀዉን የሸምጋዮች መግለጫ ባዲስ መልክ ደገሙት።ተናገሪዉ አስተናጋጁ ነበሩ የሩሲያዉ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ሰርጌይ ላቭሮቭ።

«ሁሉም የአራትዮሹ አባላት ያፀደቁት ይፋ የአቋም መግለጫ አፅድቀናል።እስራኤልና ፍልስጤሞች ተዘዋዋሪዉን ዉይይት እንዲጀምሩ ለማሳማን አቅማችን በፈቀደዉ መጠን ለመጣር የአራትዮሹ አባላት በሙሉ ተስማምተናል።ዛሬ ያፀደቅነዉ የአቋም መግለጫ፣-እስራኤልና ፍልስጤሞች መጀመሪያ ተዘዋዋሪ ቀጥለዉ ቀጥተኛ ድርድር የሚጀምሩበትን መንገድ ያመለክታል ብለን እናምናለን።»

በአሜሪካ-እስራኤሎች እራፊ ልዩነት እየጦዘ-ሲከስም፥የሠፈራ ግብባታ ዉሳኔ-ተቃዉሞ-ወቀሳዉ እየጋመ-ሲከስም፥ ስብሰባዉ-እየደራ ሲበተን ፍልስጤማዊዉ ለዘመናት እንደኖረበት ከእስራኤል ፀጥታ አስከባሪዎች ጋር ይጋጭ ገባ።የፍልስጤም ነፃ አዉጪ ድርጅት ትልቅ አንጃ የፈትሕ ዋና ፀሐፊ መሕር ጉናዪም ለኔታንያሁ አፀፋ አረፋት እድሜ ልካቸዉን ያሉትን፥ አባስ ሁሌም-ያሉ የሚሉትን እንዳዲስ ደገሙት።

«እንደዚያ የሚናገር በተጨባጭ ሰላም አይፈልግም።እየሩሳሌም ከ1967 ጀምሮ በሐይል የተያዘ ግዛት ነዉ።ከተማይቱ የፍልስጤም መንግሥት አንድ አካል ነዉ።ከዚሕ ለመድረስ ነዉ የምንታገለዉ።በዚሕም መሠረት የሰፈራ መንደር ግንባታ እንቅስቃሴ፣ እየሩሳሌም ዉስጥ የአሁድ ሠፈራ መንደር ግንባታ መቆም አለበት።»

የምሥራቅ እየሩሳሌምና የምዕራባዊ ዮርዳኖስ ወንዝ ዳርቻ ፍልስጤም ከእስራኤል ፀጥታ አስከባሪዎች ጋር እየተጋጨ-ሲሞት-ሲያቆስል፥ድንጋይ ሲወረር-በጢስ ሲታፈን፥ ሲሮጥ-ሲያዝ ዋና ፀሐፊ ፓን ጊ ሙን የጋዛ ፍልስጤምን ጎበኙ።እሁድ።

«ለጋዛ ሕዝብ ያለኝን ድጋፍ ለመግለፅ ተመልሼ ጋዛ መጣሁ።ለናንተ በጣም አስቸጋሪ ፈተና እንደሆነ ይገባኛል።ጋዛዎች በሙሉ በዚሕ በማይዘልቅ፥ ተቀባይነት በሌለዉ ሁኔታ ለቤተሰቦቻቸዉ የሚያስፈልገዉን ለማቅረብ የሚያደርጉትን ጥረት አደንቃለሁ።»

አደነቁ ሄዱ።ዕለት-ወቅት ሥፍራዉ እንጂ መልዕክታቸዉ በርግጥ አዲስ አይደለም።የድፍን ምድሩም ሐቅ-እንደዚያዉ።መካከለኛዉ ምሥራቅ።ነጋሽ መሐመድ ነኝ ቸር ያሰማን።