1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የማሊ ቀጣይ ዕቅድ

ቅዳሜ፣ ግንቦት 10 2005

ምዕራብ አፍሪቃዊቱ ሀገር ማሊ አሁንም ገና አልተረጋጋችም። በተለይ በሰሜናዊ የሀገሯ ከፊል በሚንቀሳቀሱት የቱዋሬግ ዓማፅያን እና በመዲናይቱ ባማኮ በሚገኘው የሽግግሩ መንግሥት መካከል ውዝግቡ አሁንም እንደቀጠለ ነው።

https://p.dw.com/p/18bu9

የሽግግሩ መንግሥት ሰሜናዊውን የሀገሩን አካባቢ ከዓማፅያኑ ነፃ ለማውጣት እና መልሶ ለማረጋጋት የጀመረው ጥረት፡ እንዲሁም፡ ይህንኑ ጥረት ለመደገፍ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ዝግጁነት አሳይቶዋል።
ከአንድ ዓመት ከሁለት ወር በፊት ውዝግብ ያጋጠማት የማሊ መንግሥት ወታደሮች በሰሜናዊ የሀገሩ አካባቢ ወደምትገኘው ወደ ኪዳል ከተማ ግሥገሣ ይዘዋል። ወታደሮቹ በዚሁ አካባቢ ነፃ ያወፁዋትን ሌላዋን የጋው ከተማን ባለፈው እሁድ በመልቀቅ ነበር ወደ ኪዳል መገሥገሥ የጀመረው። ወታደሮቹ የኤም ኤን ኤል ኤ የመጨረሻ ጠንካራ ሠፈር ወደሆነችው ኪዳል ከተማ መቼ እንደሚደርሱ በወቅቱ በግልጽ አልታወቀም። ለዶይቸ ቬለ ጋ ቃለ ምልልስ ያደረጉት የማሊ ጦር ቃል አቀባይ ሊየተና ዲያራ ኮኔም ቢሆኑ ይህንን መረጃ ለመስጠት ፈቃደኛ አልሆኑም። ይሁንና፡ ለቱዋሬግ ሕብ ነፃነት በሚታገለውና በምሕፃሩ ኤም ኤን ኤል ኤ በመባል በሚታወቀው ያማፅያን ቡድን ወደተያዘችው የኪዳል ከተማ በቅርቡ መድረሳቸው እንደማይቀር ለውሁዳን ብሖች መብት የሚሟገተው የጀርመናውያኑ ድርጅት የአፍሪቃ ጉዳዮች ተጠሪ ኡልሪኽ ዴልዩስ በመግለጽ ሂደቱን በቅርብ እንደሚከታተሉ አስታውቀዋል።
« የማሊ ጦር በታጠቁትና ባልታጠቁት የቱዋሬግ ቡድናት ላይ የሚውሰደውን ርምጃ በቅርብ እንከታተላለን። ተጨማሪ ጥቃት እንዳይካሄድ ሠግተናል። »
የማሊ ጦር ባለፈው ጥር ወር በፈረንሣይ እና ባንዳንድ አፍሪቃውያት ሀገራት ተረድቶ በብዛት የቱዋሬግ ሕዝብ የሚኖርባቸውን ከተሞችን እና መንደሮችን መልሶ በተቆጣጠረበት ድርጊት እስካሁን አራት መቶ ሲቭሎች መገደላቸውን ዴልዩስ ገልጸዋል። ኤም ኤን ኤል ኤ ኪዳልናና በዚሁ አካባቢ የሚገኙትን ሌሎች ከተሞች የተቆጣጠረው በሻምበል አማዱ ሳኖጎ የተመራው የጦር ኃይሉ ቡድን ባለፈው ዓመት መጋቢት ወር መፈነቅለ መንግሥት ባካሄደበት ጊዜ ነበር። ይሁን እንጂ፣ አክራሪው የአንሳር ዲን ቡድን አካባቢውን በተቆጣጠረበት ጊዜ የያዛቸውን ከተሞች እና መንደሮች ማስረከብ ተገዶዋል። የፈረንሣይ ጦር ከቻድ ጦር ጋ ባንድነት አንሳር ዲንን ከኪዳል ካባረሩ በኋላ ኤም አን ኤል ኤ ተፅዕኖውን እንደገና በዚችው ከተማ ለማጠናከር ችሎዋል። የማሊ ጦር ቃል አቀባይ ሊየተና ዲያራ ኮኔ እንዳስረዱት፣ የማሊ ጦር አሁን ወደ ኪዳል መገሥገሥ የጀመረበ።,ት ድርጊት የፊታችን ሀምሌ ወር በመላ ማሊ ምርጫ ከመደረጉ በፊት ከተማይቱን አስተማማኝና የተረጋጋች የማድረግ ዓላማ ይዞዋል። ምክንያቱም በፕሬዚደንት ዲሺንኩንዳ ትራውሬ የሚመራው የሽግግር መንግሥት በዴሞክራሲያዊ መንገድ የተመረጠ አይደለምና። የዚህኑ ምርጫ ዕቅድ ለማሳካትና የሀገሪቱን መልሶ ግንባታ ለማገዝ ከጥቂት ቀናት በፊት በብራስልስ ቤልጅየም ጉባዔ ያካሄዱት ከአንድ መቶ የሚበልጡ ሀገራት እና ድርጅቶች ከተጠበቀው ሁለት ሚልዮን ዩሮ በላይ፣ ማለትም ሦስት ነጥብ ሁለት ሚልዮን ዩሮ ርዳታ ለመስጠት ቃል ገብተዋል። የአውሮጳ ህብረት ብቻ ለማሊ እአአ በ2013 እና 2014 ዓም 520 ሚሊዮን ዩሮ ዝግጁ ያደረጉ ሲሆን፣ የህብረቱ አባል የሆነችው ጀርመን ደግሞ ከህብረቱ ጋ በመሆን ከምተሰጠው ጎን 100 ሚልዮን ዩሮ ለመስጠት ቃል ገብታለች። ከአውሮጳ ህብረት ባንድነት የለጋሽ ሀገራቱን ጉባዔ ያዘጋጀችው እና ባለፈው ጥር ወር በማሊ ያማፅያኑን ቁጥጥር ለማብቃት ዘመቻ የጀመረችው የቀድሞዋ ቅኝ ገዢ ፈረንሣይ ደግሞ 300 ሚልዮን ዩሮ እንደምትሰጥ የፈረንሣይ ውጭ ጉዳይ ሚንስትር ሎውሮ ፋብዩስ ገልጸዋል። የአውሮጳ ህብረት ከዚሁ በተጨማሪ የማሊን ጦር የማሠልጠን ርዳታ ይሰጣል፤ በዚሁ የሥልጠና ተልዕኮ ውስጥ ጀርመን 180 የጦር መኮንኖችዋን ታሳትፋለች። ፈረንሣይ በማሊ ያሠማራቻቸውን 4500 ወታደሮችዋን በወቅቱ ማስወጣት ጀምራለች። ይሁንና፣ በብራስልሱ ጉባዔ የቱዋሬግ ሕዝብ ተወካዮች አልተጋበዙም፣ አልተካፈሉም። የፖለቲካ ጠበብት እንደጠቆሙትም፣ ካለ ቱዋሬግ ተወካዮች ለማሊ ውዝግብ መፍትሔ ለማፈላለግ የሚደረገው ጥረት ሁሉ ፍሬ አልባ ነው የሚሆነው። ከሁሉ በፊት ግን መሟላት የሚገባው የሕዝቡ መሠረታዊ ፍላጎት ነው። ጦርነቱ በዓለም እጅግ ድሆች ከሚባሉት ሀገራት መደዳ የምትቆጠረውን እና በደህና ጊዜም ቢሆን በውጭ ርዳታ ላይ ጥገኛ የሆነችውን ማሊ አብቅቶ ጎድቶዋል። እንደሚታወሰው፣ ከመፈንቅለ መንግሥቱ በኋላ ለጋሽ ሀገራት ለማሊ የሚሰጡትን የልማት ርዳታ አቋርጠዋል። የአውሮጳ ህብረት የአስቸኳይ የሰብዓዊ ርዳታ አስተባባሪ ክሪስቲና ጊዮርጊየቫ እንደሚሉት፣ ለማሊ በወቅቱ አስቸኳዩ ርዳታ ያስፈልጋል። « የውህ፣ የመፀዳጃ እና የጤና ጥበቃው አገልግሎት ያስፈልጋል። በጣም አሳሳቢው ግን 660,000 ሕፃናት ባልተመጣጠን አመጋገብ መጎዳታቸው ነው። 750,000 ስዎችም አስቸኳዩ የምግብ ርዳታ ያስፈልጋቸዋል። ሁኔታው እየከፋ ሄዷል። » በአውሮጳ ህብረት ዘገባ መሠረት፣ 500,000 የማሊ ዜጎች አንድም በዚያው በሀገራቸ ተፈናቅለዋል ወይም ወደ ጎረቤት ሀገራት ተሰደዋል። ለማሊ ርዳታ ለማቅረብ ዝግጁነት ያሳዩት የአውሮጳ ህብረት፣ የተመድ፣ የዓለም ገንዘብ መርህ ድርጅት፣ ሁሉም ቅድመ ግዴታ አሳርፈዋል። የአውሮጳ ህብረት ኮሚሽን ፕሬዚደንት ኾዜ ማኑዌል ባሮዞ የዴሞክራሲ ሂደት እንዲመቻች ጠይቀዋል። « ለአውሮጳ ህብረት በመላ ማሊ የመንግሥቱ ሥርዓት መልሶ የሚተከልበት፣ ለፖለቲካው የሰላም ሂደት የተዘጋጀው የሰላም ዕቅድ መሆንና ማሊን ወደ ዘላቂ የሰላም ጎዳና ለመውሰድ የተነደፈው ዕቅድ በስራ የሚውልበት ድርጊት አብረው የሚጓዙበት ሁኔታ ወሳኝ ነው። የፀጥታው፣ የፖለቲካ ፣ የኤኮኖሚና የማህበራዊ ልማት ሂደቱ በስራ መተርጎም ይኖርበታል። » የዓለም ባ,ንክ ተጠሪ ስሪ መሉዋኒ ኢንድራዋቲም የፍትሑ አውታርና ፀረ ሙስናው ትግል እንዲጠናከር ጠይቀዋል። « ባጠቃላይ ሲቭሉን ሕዝብ፣ በተለይ ሴቶችን እና ድሀውን ሕዝብ ለመከላከል የፍትሕ አውታሩ እና በሙስና አንፃር ተግሉ እንዲጠናከር እናበረታታለን። » የተመድ የልማት መርሀግብር ተጠሪ ሬቤካ ግሪስፓንም የማሊ ፖለቲከኞች ከሁሉም የሕዘብ ከፍል አባላት ጋ ብሔራዊ ውይይት እንዲያካሂዱ ጠይቀዋል፤ ምክንያቱም ማሊ ውስጥ ሥር የሰደደው ፖለቲካዊና ማሕበራዊ ችግር መፍትሔ ሊያገኝ የሚችለው በሀገሪቱ ዴሞከራሲያዊው ሥርዓት ሲተከል ብቻ ነው። የማሊ ፕሬዚደንት ዲዩንኩንዳ ትራውሬ ዓለም አቀፉ ማሕበረሰብ ያቀረበውን ቅድመ ግዴታ ለማሟላት ፍላጎቱ እንዳላቸው በበራስልሱ ጉባዔ ላይ ገልጸው፣ እስከ ፊታችን ሀምሌ መጨረሻ በሀገራቸው ምርጫ ለማካሄድ ያላቸውንም ፅኑ ፍላጎት አረጋግጠዋል። ትራውሬ እንዳሉት፣ በምርጫው የሽግግሩ መንግሥት አባላት፣ ፕሬዚደንቱ ጭምር አይሳተፉም። ማሊ ችግር ቢበዛባትም የሽግግሩ መንግሥት ግልጽ፣ ነፃ እና ታማኝ ምርጫ እንደሚያካሂድ ፕሬዚደንት ትራውሬ በማረጋገጥ፣ ያልተረጋጋች ማሊ ለራሷ ብቻ ሳይሆን ለጠቅላላው ላካባቢው መዘዝ እንደምትሆን አስጠንቅቀዋል።

Versorgung in Mali für den 8. Mai 2013
ምስል DW/K. Gänsler
Mali Geberkonferenz in Brüssel Coulibaly Barroso
ምስል Georges Gobet/AFP/Getty Images
Soldaten Armee Mali
ምስል JOEL SAGET/AFP/Getty Images
Mali/ Tuareg/ MNLA/ Kidal
ምስል Reuters

ፔተር ሂለ/አርያም ተክሌ

መሥፍን መኮንን

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ