1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የማዕከላዊ አፍሪቃ ሪፐብሊክ ዕልቂት

ሰኞ፣ የካቲት 10 2006

ያዩ እንደሚሉት በርግጥም ዘግናኝ ነዉ።የሰዉ አንገት በገጀራ ይቀነጠሳል።እጅ፥ እግር፥ በጎራዴ ይቆረጣል።ሌላ አካል በጩቤ ይጨቀጨቃል። መንገዶች በደም አበላ ጨቅይተዋል-እየጨቀዩም ነዉ።አስከሬን በየጉርጓዱ ይከመራል።ከተንቀሳቃሽ ሥልክ እስከ ምግብ፥ ከሐብል እስከ ብስክሌት ያሉ ቁሳቁሶች ይመዘበራሉ። ቤቶች፥ መደብሮች፥ ቁሳቁሶች፥ መሳጂዶች ይነዳሉ።

https://p.dw.com/p/1BAd2
ምስል picture alliance/AA

የዋሽግተን-ሞስኮ፣ የለንደን-ቤጂንግ ሐያላን ከቁብ አልቆጠሯትም።ፓሪሶች እንዳይረሷት የድሮ ቅኝ ተገዢ ናት።እንደ ሊቢያ እንደ ኮትዲቯር፥ ወይም እንደ ማሊ ሐያል ተባባሪዎችን አስተባብረዉ እንዳያዘመቱባት ነዳጅ፣ ሥልታዊነት፣ መጥፋት ያለበት ገዢ ጠላት የለባትም።ማዕከላዊ አፍሪቃ ሪፐብሊክ።አፍሪቃዉያን የደቡብ ሱዳንን ያክል እንዳይጨነቁላት ነዳጅ፥ አዲስ ገበያ የላትም።ፈረንሳዮችም፣ አፍሪቃዎችም የሉም እንዳይባሉ በጥቂት ጦር አለን ሲሉ፣ የአዉሮጳ ሕብረት አለሁ ለማለት እያዘገመ ነዉ።የደሐይቱ ሐገር ሕዝብ ግን ይረገፋል።የማዕከላዊ አፍሪቃ ሪፐብሊክ እልቂት መነሻ፥ የዓለም ትኩረት ያልሳበበት ምክንያት መድረሻችን ነዉ። ላፍታ አብራችሁኝ ቆዩ።

የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ ፓን ጊ ሙን እንደ ብዙዉ ዓለም ፖለቲከኛ ዲፕሎማት ሁሉ ዘግይተዋል።ግን ቢያንስ በቀደም የግጭት፥ እልቂት ጥፋቱን አሳሳቢነት ተናገሩ።

«ለትዉልዶች ተሳስሮ የኖረዉ ማሕበረሰብ ተከፋፋል እየተጫረሰ ነዉ።ማሕበረሰቡን ደም ያቃባዉ ግጭትን ለማቆም እርምጃ ካልተወሰደ ለአስርታት የሚዘልቅ ግጭት ያስከትላል።»

እልቂቱ፥ ያዩ እንደሚሉት በርግጥም ዘግናኝ ነዉ።የሰዉ አንገት በገጀራ ይቀነጠሳል።እጅ፥ እግር፥ በጎራዴ ይቆረጣል።ሌላ አካል በጩቤ ይጨቀጨቃል።ሴቶች ይደፈራሉ። መንገዶች በደም አበላ ጨቅይተዋል-እየጨቀዩም ነዉ።አስከሬን በየጉርጓዱ ይከመራል።ከተንቀሳቃሽ ሥልክ እስከ ምግብ፥ ከሐብል እስከ ብስክሌት ያሉ ቁሳቁሶች ይመዘበራሉ። ቤቶች፥ መደብሮች፥ ቁሳቁሶች፥ መሳጂዶች ይነዳሉ።

ዋና ፀሐፊ ፓን ጊ ሙን ከኒዮርክ የእልቂት ፍጅቱን አስጊነት ሲናገሩ ፖላንዳዊዉ የካቶሊክ ቄስ ንዛኮን የተባለችዉ መንደር የምታስነግደዉን ግፍ ይታዘቡ ነበር።ስማቸዉ መጠቀሱን ያልፈለጉት ቄስ እንደሚሉት ከመንደሪቱ ሲደርሱ ጣራ-ግርግዳቸዉ የጋዩ ቤቶች፥ በደም የራሰ ዓመድ፥ ከሰል፥ ዝንቦች የወረሩት አስከሬን----አዩ።የንዛኮን አስደንጋጭ ትርዒት ቄሱ እንደሚሉት በዚሕ አላበቃም።

«እዚያ እንደደረስን ሃያ-ሁለት ሰዎች ተገደሉ።ወደዚያዉ ሃያ-አምስት ቤቶች ጋዩ።ወደ መንደሪቱ መሐል ስንደርስ የተቃጠሉ ሞተር ብስክሌቶች፥ ብስክሌቶች፣የጋየ መድሐኒት ቤት አየን።ሰዎቹ በጣም መጥፎ ነገር ነዉ የፈፀሙት።»

ሙስሊሞች የሚበዙበት የሳሌካ አማፂያን ሕብረት የቀድሞዉን ማዕከላዊ አፍሪቃ ሪፐብሊክ አምባገነን ገዢ ፍራንሷ ቦዚዜን አስወግዶ ሥልጣን ከያዘበት ካለፈዉ ዓመት መጋቢት ወዲሕ ማዕከላዊ አፍሪቃ ሪፐብሊክ ሠላም ኖሯት አያዉቅም።በቀድሞዉቹ አማፂያን እና አማፂያኑን በሚቃወሙት በቦዚዜ ታማኞች፥ ቦዚዜ ባስታጠቋቸዉ ወጣቶች መካካል ለወራት የተደረገዉ ዉጊያ ግጭት ሐገሪቱን ለዘራፊ ወሮበሎች አጋልጧቷል።

ወዲያዉ ግጭት ዉጊያዉ ፖለቲካዊ መልክ ባሕሪዉን ለዉጦ ሐይማኖታዊ ሆነ።ሙስሊሞች የሚበዙበትን አማፂያን የሚቃወሙት የክርስቲያኒያን ሚሊሺዎች የታጠቀዉንም፥ ያልታጠቀዉንም፥ ሴቱኑም ወንዱኑም፣ ልጁንም አዋቂዉንም ሙስሊም ሲያሰኛቸዉ በጥይት፥ ሲፈልጋቸዉ በቆንጨራ ይረሽኑት፥ ያርዱ፥ ይቆራርጡ፥ ያሰደዱት ገቡ።

ቻናል ፎር የተሰኘዉ የብሪታንያ ቴሌቪዥን ጣቢያ ጋዜጠኛ ባለፈዉ ሳምንት እንደዘገበችዉ ደግሞ ሰዎች እንደበግ እየታረዱ ነዉ።

«ማዕከላዊ አፍሪቃ ሪፐብሊክ ዉስጥ የዘር ማጥፋት ዘር እየተዘራ ነዉ።የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት አስጠንቅቋል።የአይን ምስክሮች እንደሚሉት ደግሞ ሙስሊሞች እንደገበግ እየታረዱ ነዉ።»

የቀድሞዋ የማዕከላዊ አፍሪቃ ሪፐብሊክ ቅኝ ገዢ ፈረንሳይ የሠላማዊዉን ሰዉ እልቂት ፍጅት ያስቆማል ያለችዉን አንድ ሺሕ ስድስት መቶ ጦር ባለፈዉ ታሕሳስ አዝምታለች።ተጨማሪ አራት መቶ ወታደሮች ለማዝመት እየተዘጋጀችም ነዉ።የአፍሪቃ ሕብረት አባል ሐገራት በበኩላቸዉ አምስት ሺሕ ወታደሮች አዝምተዋል።

የፈረንሳዩ ጦር አዛዥ ጄኔራል ፍራንሲስኮ ሶሪያኖ ባለፈዉ ሳምንት እንዳሉት ሰሞኑን በሕዝብ ላይ ለሚፈፀመዉ ጭፍጨፋ ፀረ-ባላካ በሚል ቡድን የተደራጁት የክርስቲያን ሚሊሺያ አብዛኞቹ አባላት ወንጀለኛ እና ወሮበሎች ናቸዉ።ወንጀለኛና ሽፍቶቹ የሚፈፅሙትን ጥቃት ለመከላከል ግን የሐያሊቱ ሐገር ጠንካራ ጦር ቢያንስ እስካሁን የተከረዉ የለም።

አምና መጋቢት የማዕከላዊ አፍሪቃ ሪፐብሊክን የመሪነት ሥልጣን ይዘዉ የነበሩት የቀድሞዉ የሳሌካ አማፂ ቡድን መሪ ሚሼል ጆቶዲያ እና ጠቅላይ ሚንስትራቸዉ በፈረንሳይ ፍቃድ፥ በቻድ ግፊት ሥልጣን ለቀዉ በምትካቸዉ ሌሎች ከተሾሙ ወር አለፈ። እልቂቱ ግን ባሰ እንጂ አልቆመም። የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የዘር ማጥፋቱ ጭፍጨፋ እየተዘራ መሆኑን ሲናገር ዓለም አቀፉ የመብት ተሟጋች ድርጅት አምንስቲ ኢንተርናሽናል በበኩሉ የዘር ማጥፋት ወንጀል መፈፀሙን ይዘግባል።

የዓለም አቀፉ የጦር ወንጀለኞች መዳኛ ፍርድ ቤት ICC ጠቅላይ አቃቢት ሕግ ፋቶ ቤን ሶዳ በበኩላቸዉ የሳሌካ አማፂያንም፥ የፀረ-ሳሌካ ሚሊሻዎችም በሰላማዊ ሕዝብ ላይ የፈፀሙትን ወንጀል ለማጣራት ማቀዳቸዉን አስታዉቀዋል።በፈረንሳይ ድጋፍ በቅርቡ ሥልጣን የያዙት የማዕከላዊ አፍሪቃ ሪፐብሊክ ጊዚያዊ ጠቅላይ ሚንስትር አንድሬ ንዛፓዬከ ግን እኒያኑ የፈረንሳዩ ጀኔራል ወንጀለኛ እና ወሮበላ ያሏቸዉን የክርስቲያን ሚሊሺያ አዛዦች ሰብስበዉ ጥቃቱን እንዲያቆሙ መማፀናቸዉን ዛሬ አስታዉቀዋል።

ሕዝብ ግን ፖላንዳዊዉ የካቶሊክ ቄስ እንዳሉት ከቻለ ይሰደዳል፥ ካልቻለ ግን ዕለት በዕለት እየተጨፈጨፈ ነዉ።የጠቅላይ ሚንስትር ንዛፓዬከ መንግሥት፥ የፈረንሳይ እና የአፍሪቃ ሕብረት ጦር ጭፍጨፋዉን ለማስቆም ሁነኛ እርምጃ እንዲወስዱ ፖለንዳዊዉ ቄስና ብጤዎቻቸዉ የሚያሰሙት ጩኸት ሰሚ አላገኘም።

«ርዕሠ ከተማ ባንጉይ የሚገኙት የመንግሥት ባለሥልጣናት እና የፈረንሳይ ጦር (እልቂቱን) እንዲያስቆሙ በተደጋጋሚ ጠይቄ ነበር።ማንም የተቀበለኝ የለም።አሁን ያለሁት የሴሌካ አማፂያን ከማዕከላዊ አፍሪቃ ሪፐብሊክ እየለቀቁ በሚሸሹበት በካሜሩን እና በቻድ አዋሳኝ ድንበር ነዉ።እንደ ፀረ-ባላካ ሚሊሻዎች ሁሉ የሴላካ አማፅያንም ሲሸሹ የሚያደርሱት ጥፋት ከባድ ነዉ።»

ሱዳናዊዉ እዉቅ የጦር አበጋዝ ሱልጣን ረቢሕ ዓል ዙቤር ኢብን ፈድል አላሕ የዛሬዋን ማዕከላዊ አፍሪቃ ሪፐብሊክን ከቻድ ጋር ቀይጠዉ መግዛት ከጀመሩበት ከ1875 (ዘመኑ በሙሉ እንደ ጎሮጎሮሳዉያኑ አቆጣጠር ነዉ) ጀምሮ የዚያች ሐገር ሕዝብ የራሱን ጉዳይ በራሱ ፍላጎትና ፍቃድ ወስኖ አያዉቅም።

ማዕከላዊ አፍሪቃ ሪፐብሊክ፥ ቻድንና ሌሎች የአካባቢዉ ሐገራትን ከሱልጣን ረቢሕ አል ዙቤር ሐይላት የቀማችዉ ፈረንሳይ በ1960 ለማዕከላዊ አፍሪቃ ሪፐብሊክ የነፃ ሐገር እዉቅና ብትሰጣትም የዚያች ሐገር ፖለቲካዊ ሒደት አንድም በቀጥታ ከፓሪስ አለያም ለፓሪስ ባደሩት በእንጃሚና፥ በያዉንዴ፥ በኪንሻሳ ገዢዎች ያልተዘወረበት ዘመን የለም።

ማዕከላዊ አፍሪቃ ነፃ ከወጣችበት ጊዜ ጀምሮ በተቆጠሩት 53 ዓመታት በመፈንቅለ መንግሥት፥ እራሳቸዉን ወደ ንጉስነት እስከመቀየር በደረሱ የጦር መኮንኖች አገዛዝ፥በርስ በርስና በዉጪ ጣልቃ ገብ ጦር ግጭት ያልታበጠችበት ጊዜ ትንሽ ነዉ።በዚሕ ሁሉ ዘመን የዚያች ሐገር ደሐ ሕዝብ እኩል መጨቆን፥ መረገጥ መሰቃየቱ እንጂ ክርስቲያንና ሙስሊም በሚል ሐይማኖት ለይቶ የተጨፋጨፈበት ዘመን ግን የለም።

ዋና ፀሐፊ ፓን ጊ ሙን «ለበርካታ ትዉልድ ተሳስሮ የኖረ» ያሉት ማሕበረሰብ አንድነትን የበጠሰዉ እልቂት ፍጅትን ለማስቆም ፈረንሳይ እንደ ማሊ ያየር የምድር ጦሯን ማዝመት አልፈለገችም።የራስዋ የፓሪስ፥ የዋሽግተን፥ ለንደን መሪዎች እንደ ሊቢያ ሐያል ፈርጣማ ጦራቸዉን ለማዝመት ምክንያት የላቸዉም።ወደብ አልባ ደሐይቱ ሐገር የሐያሉን ዓለም ትኩረት ለመሳብ እንደ ማሊ ሥልታዊ ጠቀሜታ፥ እንደ ሊቢያ ነዳጅ ዘይት፥ የረጅም ጊዜ የምዕራባዉያን ጠላት ገዢ ሊኖታት ይገባል።የላትም።

የአዉሮጳ ሕብረት እልቂት ፍጅቱ በዓለም መገናኛ ዘዴዎች ወደ ዘር ማጥፋት ወይም የሐይማኖት ተከታዮችን ማፅዳት ከተሸጋገረ በሕዋላ እንኳን ለማዝመት ያቀደዉ ከስድስት መቶ የማይበልጥ ወታደር ነዉ።ሌላዉ ቀርቶ የአፍሪቃ መሪዎች እንኳን የደቡብ ሱዳንን ያክል ሙሉ ትኩረት ሊሰጧት አልፈቀዱም ወይም አልቻሉም።

እንደ ፈረንሳይ ሁሉ እልቂት ፍጅቱን በገሚስ ልብ የሚከታተሉት የአፍሪቃ መሪዎች ያዘመቱት ጦር እስካሁን እልቂቱን ለማስቆም እንደ ፈረንሳይ ጦር ሁሉ የተከረዉ ነገር የለም።እንዲያዉም MISCA በሚል ምሕፃረ-ቃል የሚጠራዉ የአፍሪቃ ሕብረት ጦር አዛዥ ጄኔራል ማርቲን ቱሜንታ ቹሙዋ እንደሚሉት ጦራቸዉ የሚተኩሰዉ በራሱ በጦሩ አባላት ላይ ከተተኮሰበት ብቻ ነዉ።

ጦሩ ሚሊሺያዎቹ ወይም አማፂያኑ በሰላማዊ ሕዝብ ላይ የሚያደርሱትን ጭጨፋ ለማስቆም እርምጃ ካልወሰደ ቦንጊ ድረስ የዘመተበት ዓላማ ምክንያት በርግጥ ግራ አጋቢ ነዉ።ካለፈዉ ታሕሳስ ወዲሕ መረን በለቀቀዉ ጭፍጨፋ ርዕሠ-ከተማ ቦንጊ እና አካባቢዋ ብቻ ከሁለት ሺሕ በላይ ሕዝብ መገደሉ ተዘግቧል።በየመንደሩ በየዕለቱ የሚያልቀዉን ሰዉ በትክክል የቆጠረዉ የለም።ዕልቂቱን ሽሽት የተሰደደ ወይም የተፈናቀለዉን ሕዝብ ከሚረዱት አንዱ ፖለንዳዊዉ ቄስ እንደሚሉት ግድያዉ ባሁን ይዘቱ ከቀጠለ እሳቸዉን ለመሰሉ የዉጪ ሰዎችም ማስጋቱ አይቀርም።ግን ጠመንጃ የታጠቀዉ ጦር የማያደርገዉን ለማድረግ የቆረጡ ይመስላሉ ቄሱ።

«የለም ከዚሕ አንወጣም።ከሕዝቡ ጋር መቆየት እንፈልጋለን።ሕዝቡ ይፈልገናል።በያለንበት በአሸዋ የተሞሉ ጆንያዎችን ደርድረን በምንሰራዉ ምሽግ እንጠለላለን።ጥቃቱ በኛ ላይ በጣም ከከፋ ግን እንወጣ ይሆናል።»

ጄኔራሎቹ ይፎክራሉ።ፖለቲከኞቹ ገና ያቅዳሉ።ዲፕሎማቶቹ ያወራሉ።ሕዝብ ያልቃል።ይሰደዳል።ሐብት ንብረት ይወድማል። ቄሶቹ፥ ርዳታ አቀባዮቹ እልቂት፥ ፍጅት ስደት ስቃዩን ይጋፈጣሉ።ማዕከላዊ አፍሪቃ ሪፐብሊክ።እስከ መቼ ነጋሽ መሐመድ ነኝ ቸር ያሰማን።

Zentralafrikanische Republik Versuche der Versöhnung
ምስል Bettina Rühl
Zentralafrikanische Republik Muslimische Flüchtlinge
ምስል Bettina Rühl
Zentralafrikanische Republik französische Soldaten
ምስል Getty Images/Afp/Johannes Eisele
Zentralafrikanische Republik französische Soldaten
ምስል picture-alliance/dpa/ECPAD

ነጋሽ መሐመድ

አርያም ተክሌ

















ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ