1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የሜርክልና የትራምፕ የመጀመርያ ዉይይት ምን ይሆን?

ዓርብ፣ መጋቢት 8 2009

ባለፈዉ ማክሰኞ በዩኤስ አሜሪካ በደረሰው ከፍተኛ የበረዶ ወጀብ ምክንያት  የአሜሪካ ጉዟቸዉን የሰረዙት የጀርመንዋ መራሂተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል አርብ ዋሽንግተን ገቡ። ሜርክል የዩኤስ አሜሪካ ፕሬዚደንት ዶናልድ ትራምፕ ሥልጣን ከያዙ ወዲህ ወደ አሜሪካ ሲሄዱ ይህ የመጀመርያቸዉ ነዉ።

https://p.dw.com/p/2ZKEW
Bildcollage Donald Trump Angela Merkel lächelnd
ምስል picture-alliance/dpa/J. Knappe & Reuters/K. Lamarque

Merkel trifft Trump: Worum geht es? - MP3-Stereo

ይህ  ጉብኝት ከእስከ ከዛሬዉ የዩኤስ አሜሪካ ጉብኝታቸዉ ሁሉ ፈታኝ ሳይሆን እንደማይቀር እየተነገረ ነዉ። የፊታችን ሐምሌ ጀርመን ሃምቡርግ ከተማ የቡድን -20 ጉባዔን የሚያስተናfዱት ሜርክል ፤ ከፕሬዚዳንት ትራምፕ ጋር ከሚወያዩባቸዉ ርዕሰ ጉዳዮች መካከል የዩኤስ አሜሪካ እና የአዉሮጳ ግንኙነት እንዲሁም የሩስያ ጉዳይ ይሆናሉ ተብሎ ይጠበቃል።  የጀርመንዋ መራሂተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል ከአትላንቲክ ባሻገር ስላለው ግንኙነት እና ስለ አሜሪካን ፕሬዝዳንቶች  ብዙ አይተዋል ብዙም ያዉቃሉ ማለት ይቻላል። እጅግም የማይወደዱትን የቀድሞዉ የዩኤስ አሜሪካን ፕሬዚዳንት ጆርጅ ቡሽን በስልጣን ላይ ሳሉ ጀርመን  ባልቲክ ባህር አቅራብያ «ባርቢኪዉ»  ጋብዘዋቸዉ ነበር። በጣም ተወዳጅን ባራክ ኦባማንም  በባቫርያ አልፐን ተራራ ግርጌ የጀርመንን ባህላዊ ምግብ እና ቢራ  ጋብዘዋቸዋል።ሜርክል በነዚህ ሁለት የዩኤስ አሜሪካ ፕሬዚዳንቶች የስልጣን ዘመን ከአትላንቲክ ባሻገር ያለው ግንኙነት በኢራቁ  ጦርነት  እና በአሜሪካዉ ብሔራዊ የስለላ ተቋም የ« NSA» ስለላ ያሳደረው ቅሪታ  ከባድ ቀዉስ ቢያስከትልም ሜርክል ከዋሽንገተኑ መንግሥት ጋር በጣም የተቀራረበ ግንኙነት በማድረግ በቡሽም ጊዜ ሆነ በኦባማ ጊዜ በአዉሮጳ ጉዳይ የመጀመርያ የቅርብ አማካሪ ሆነዉ ቆይተዋል። ይሁን እና በበርሊን የዉጭ ግንኙነቶች ጉዳይ ላይ የአዉሮጳ ም/ቤት ቢሮ ሊቀመንበር ዮሴፍ ያኒንግ እንደሚሉት ሜርክል ከአሁኑ የዋሽንግተን መንግሥት ጋር ፈታኝ ሁኔታ ነዉ የሚገጥማቸዉ።

«የአሜሪካንን ፖለቲካ በተመለከተ እንደ አሁኑ ዉስብስብ ሆኖ አያውቅም።» በኢጣልያ ቦለኛው የጆን ሆፒኪንስ ዩንቨርስቲ የአሜሪካዊዉ የዉጭ ጉዳይ ተመራማሪ ዶን ሃርፐር እንደገለፁት መራሂተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል ከአሜሪካ ፕሬዚዳንት ጋር ጥሩ ግንኙነት ለመፍጠር አዲስ መንገድን መፈለግ ይኖርባቸዋል። ትራምፕ ከኦባማም ሆነ ከቡሽ ፈፅሞ የተለዩ ሰዉ ናቸዉ። ትራምፕ  ከነዚህ ከሁለት የቀድሞ የአሜሪካ ፕሬዚዳንቶች ሆነ ከሜርክል የሚለዩት ምንም አይነት የፖለቲካ ልምድ ስለሌላቸዉ ፤ ከዚህ በተጨማሪ ትራምፕ ስለማንኛዉም ፖለቲካዊም ሆነ ሌሎች ርዕሶች ላይ በቅጽበት ጠብ አጫሪ የሆኑ አስተያየቶችን በትዊተር መገናኛ መረብ በማሰራጨት ነዉ የሚታወቁት ። ሌላዉ ትራምፕ ከብዙኃን መገናኛዎች የግል ጸብ ላይ ናቸው። ትራምፕ ይህን ሁሉ ነገር ይዘዉ  ዋይት ሃዉስ መገኘታቸዉ ብቻ ሳይሆን ልዩ የሚያደርጋቸዉ ከመራሂተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል ፍፁም ተቃራኒ መሆናቸዉም ነዉ። ሜርክል ረጋ ያሉ እና  ቁጥብ በመሆናቸዉ ይታወቃሉ። የትራምፕ እና የሜርክል የሕይወት ታሪክና መንግስታዊ አመራር ስልት የተለያየ በመሆኑ በሁለቱ መካከል ሊኖር የሚችለዉን ግንኙነት አስቸጋሪ ያደርገዋል። መራሂተ መንግሥትዋ በዓለም ላይ የጋራና በርካታ ሃገራትን ያካተተ ፖለቲካን  ማራመድ ነዉ የሚፈልጉት። ትራምፕ በተቃራኒዉ ለአንድ ዓለም አቀፍ ጉዳዮች  የአንድ ልዕለ ኃያል መንግሥት መፍትሄን ነው የሚደግፉት ። ብዙ ሃገራትን ያካተተ የአሰራር ዘይቤንም ይንቃሉ ። ትራምፕ እና ሜርልክ እንዲሁም ደጋፊዎቻቸዉ እስከዛሬ ያካሄዱት የቃላት ግጭት በአሁኑ ግንኙነታቸዉ ላይ ይህን ነዉ የሚባል ለዉጥን አያመጣም ሲሉ ያኒግም ሆነ ሃርፐር ይገምታሉ። የሜርክል የዚህ ጉብኝት ዓላማ ይላሉ በመቀጠል፤

Deutschland Münchner Sicherheitskonferenz 2017
ምስል Reuters/M. Dalder

«ከፍላጎታቸዉ አንዱ በቡድን -20 ሂደትና ያሉትን ችግሮች በትብብር መዋቅሮች ለመፍታት ከአዲሱ ፕሬዝዳንት ቢያንስ የቃል ቁርጠኝነት ማግኘት ነው። » ሜርክል አሁን ወደ አሜሪካ የሚጓዙት የፊታችን ሐምሌ  ሃምቡርግ ጀርመን ለሚያስተናግዱትን የቡድን -20 ጉባዔ ዝግጅት ነዉ ሲሉ ያኒንግ አክለዋል። ዋንናው እና ትልቁ የአሜሪካ ጉብኝት ዓላማ የአዉሮጳ ህብረት የወደፊት ጉዞን የሚመለከተዉ ጉዳይ ነዉ።

ትራምፕ የ« ብሪግዜት »ን ብሪታንያ ከአዉሮጳ ኅብረት እንድትወጣ የመጀመርያ ንድፈሃሳብ ያስቀመጡትን ኒግል ፋራዥን ምርጫዉን እንዳሸነፉ የመጀመርያዉ የዉጭ ሃገር እንግዳ አድገዉ በመጋበዛቸዉ ለአዉሮጳ ህብረት ያላቸዉን አቋም በግልጽ አሳይተዋል። ብሪታንያ ከአዉሮጳ ህብረት መዉጣትዋን በጣም አድርገዉ የሚደግፉት ትራምፕ ለተደጋጋሚ ጊዜ ከአዉሮጳ ኅብረት የሚጠብቁት ኢምንት እንደሆነና ይልቁንስ ከኅብረቱ ይልቅ ከእያንዳንዱ የአዉሮጳ ሃገር ጋር ግንኙነት ማድረግ እንደሚሻልም  አሳይተዋል። በዚህም ምክንያት ሜርክል በዚህ የአሜሪካ ጉብኝታቸዉ  የሚጠብቃቸዉ ስራ እንደ ትራምፕ  አመለካከት የአዉሮጳ  ኅብረት ለጀርመንና ለአዉሮጳ ሃገራት ብቻ ሳይሆን ለዩኤስ አሜሪካም ጠቃሚ መሆኑን ግልጽ ማድረግ ነዉ። እንደ ኒያግ እምነት ግን ጉዳዩ አስቸጋሪ ነዉ ምክንያቱም፤  ትራምፕ ከቀዳሚዎቹ የዩኤስ አሜሪካ ፕሬዚዳነቶች በተለየ ሁኔታ እንደተናገሩት አሜሪካን የአውሮጳ ኃይልም ሆነ ከአትላንቲክ ባሻገር ባለው ህብረትም ተፎካካሪ የሌላት መሪም አድርገው አይመለከቱም ። የአሜሪካዊዉ የዉጭ ጉዳይ ተመራማሪ ዶን ሃርፐር እንዳሉት ይህን የትራምፕን  አቋም ማስቀየር እንደት ትልቅ ስኬት የሚታይ ነዉ።

« ከዚህ ጉብኝት ይገኛል ብዬ ተስፋ የማደርገዉ ነገር ቢያንስ፤ ሜርክል ትራምፕ የአዉሮጳ ኅብረትን ማጥቃት እንዲያቆሙ ሊያስገድዱዋቸው ይችላሉ ። ማሪን ለ ፔን (የፈረንሳይ ቀኝ ጽንፈኛ ፖለቲከኛ)ን የመሳሰሉ ፖለቲከኞችን ማበረታታት እንዲያቆሙም ያደርጓቸዋል ብዬ አምናለሁ።  የሩስያ አጨቃጫቂ ርዕሰ ጉዳዮች በሚመለከት ሜርክል  በተመሳሳይ ሁኔታ ሞስኮን ለማሳተፍ  ከ 2ኛ ዓለም ጦርነት በኋላ የረቀቁትን ህጎች መሰረት ማድረግ እንደሚያስፈልግ ለትራምፕ ግልፅ ያደርጋሉ። በዚህም አለ በዚያ ትራምፕና ሜርክል ከዚህ ከመጀመርያ ግንኙነታቸዉ በኋላ አብረው መሥራት የሚያስችላቸው የጋራ መሠረት ይኑራቸው አይኑራቸው ግልጽ ላይሆን ይችላል ።  ። በመጀመርያ ደረጃ  ዶናልድ ትራምፕ በመጪዎቹ ስድስት ወር የስራቸዉን ዉጤት ማቅረብ ይኖርባቸዋል። ሜርክል ደግሞ የፓርላማ ምርጫን ማሸነፍ ይጠበቅባቸዋል። የአሜሪካዊዉ የዉጭ ጉዳይ ተመራማሪ እንደ ዶን ሃርፐር እምነት ደግሞ ይህ የሁለቱ ባለስልጣናት የመጀመርያ ውይይት ቢያንስ አንድ በአጭር ጊዜ ውስጥ የሚታይ ውጤት  ያስገኛል። « ትራምፕ ሜርክልን ፊት ለፊት ካነጋገሩ በኋላ ሴትየዋን ለመስደብ የሚከብዳቸዉ ይመስለኛል።» 

 

አዜብ ታደሰ / ሚሻኤል ክኒገ

ኂሩት መለሰ