የሰዉነት ፈሳሾችና HIV
ማክሰኞ፣ ጥቅምት 6 2005ባለሙያዎች እንደሚሉት ግን ከግል ይልቅ ከምክር አገልግሎት ጋ የሚደረገዉ ምርመራ ይበልጥ ጥቅም አለዉ። የዛሬ 21ዓመት HIV በደሜ ዉስጥ እንዳለ ተመርምሬ ሳረጋግጥ ይላሉ አሜሪካዊዉ ጆንሰን፤ በወቅቱ ያስተዋልኩት ከባድ ፈተና የሰዎች ለመመርመር ፈቃደኛ ያለመሆናቸዉን ነዉ። እንደዉም ቫይረሱ በደማቸዉ ዉስጥ ከመኖሩ ይበልጥ የሚያስጨንቃቸዉ በአካባቢያቸዉና የሚያዉቋቸዉ ሰዎች ዉስጥ ሊፈጠር የሚችለዉ ስሜት፤ ስለነሱ የሚኖራቸዉ ግምትና የመሳሰዉ ነዉ ይላሉ ጆንሰን።
አሜሪካን ዉስጥ ቫይረሱ በደማቸዉ ከሚገኝ 1,2 ሚሊዮን ዜጎች መካከል ወደ240 ሺህ የሚገመቱት በቫይረሱ መያዛቸዉን አለማወቃቸዉ የሚነገረዉ። የHIV ቫይረስን ስርጭት ለመቀነስ ደግሞ ሰዎች ተመርምረዉ ስለጤናቸዉ ይዞታ ማወቅ መቻላቸዉ ወሳኝ እንደሆነ ይታመናል። ሃኪም ቤት ሄዶ ወይም ሌላ ሶስተኛ ሰዉ እያወቀ የመመርመር ድፍረት መጥፋቱን በማስተዋልም ሰዎች በግላቸዉ ይህን የሚመረምሩበትና የሚያዉቁበት ስልት እንዲኖር ሲታሰብ ቆይቷል። ሰዎች ቤት ዉስጥ በግላቸዉ የሚያደርጉት ምርመራ ባይከፋም ዶክተር ይገረሙ አበበ በኢትዮጵያ የካርተር ማዕከል ተጠሪ እንደሚሉት ግን በግል ከሚደረገዉ ምርመራ ይልቅ የባለሙያ ምክር ቢታገዙ ይመረጣል።
ከደም በተጨማሪም ምራቅ ላይ በሚደረግ ምርመራ HIV ቫይረስ አንድ ሰዉ በደሙ እንዳለ ወይም እንደሌለ ማረጋገጥ እንደሚቻል ጥናቶች ያመለክታሉ። ይህ የምርመራ ስልት ቀደም ሲል የሚታወቅ ቢሆንም ግለሰቦች በቤታቸዉ የራሳቸዉን የጤና ሁኔታ እንዲያዉቁበት ታልሞ የተቀየሰ ነዉ። የአሜሪካን የምግብና የመድሃኒት አስተዳደር ዜጎች የምርመራ ስልቱ ተቀባይነት እንዳለዉ በማፅደቅ ሰዎች በግላቸዉ የHIV ምርመራ ማድረግ እንዲችሉ ፈቅዷል። የቫይረሱን ስርጭት መቀነስ ብሎም መግታት የሚቻለዉ በምርመራ መሆኑን ያመለከተዉ አስተዳደር ሰዎች በግላቸዉ እንዲመረመሩ የማበረታታቱ ዓላማ መመርመር የማይፈልጉትን ወገኖች ለማደፋፈር ነዉ። በቤት ዉስጥ ለዚህ ምርመራ የሚረዱ የተለያዩ መሳሪያዎችንም ከመፍቀዱ ተያይዞም በተለይ የደም ምርመራ የግድ የሚሉ መሳሪያዎች ዉጤቱን ለማወቅ ወደቤተሙከራ መሄዳቸዉ እንደማይቀርም አስታዉቋል።
ሰዎች በአብዛኛዉ HIV ቫይረስ መተላለፍን የሚያገናኙት ከወሲባዊ ግንኙነት አለያም ከደም ንክኪ ጋ ነዉ። ዶክተር ይገረሙ የገልፁት መጠኑ ይለያይ እንጂ ከአካል በሚወጡ ፍሳሾችም ዉስጥ እንደሚኖር ነዉ፤ ባለፈዉ 2004ዓ,ም ኢትዮጵያ ዉስጥ ዘጠኝ ሚሊዮን ሰዎች የHIV ምርመራ እንዲያደርጉ ታቅዶ ከአስር ሚሊዮን በላይ ለሚሆኑ ተመርምረዋል።
ሸዋዬ ለገሠ
አርያም ተክሌ