1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የስፖርት ዘገባ

ሰኞ፣ ሐምሌ 2 2004

የኢትዮጵያ ወጣት አትሌቶች ባለፈው አርብ ፓሪስ ላይ ተካሂዶ በነበረው የአትሌቲክስ ዳያመንድ ሊግ ውድድር ድንቅ የአምሥት ሺህ ሜትር ውጤት በማስመዝገብ በትክክለኛው ወቅት በትክክለኛው ዝግጅት ላይ መሆናቸውን አመልክተዋል።

https://p.dw.com/p/15U8l
ምስል picture-alliance/dpa

የኢትዮጵያ ወጣት አትሌቶች ባለፈው አርብ ፓሪስ ላይ ተካሂዶ በነበረው የአትሌቲክስ ዳያመንድ ሊግ ውድድር ድንቅ የአምሥት ሺህ ሜትር ውጤት በማስመዝገብ በትክክለኛው ወቅት በትክክለኛው ዝግጅት ላይ መሆናቸውን አመልክተዋል። ደጀን ገ/መስቀል፣ ሃጎስ ገ/ሕይወትና መሰሎቻቸው በዚህ ጥንካሬ በለንደን ኦሎምፒክ ከኬንያ ተፎካካሪዎቻቸው ጥላ ወጥተው ለድል ሊበቁ የማይችሉበት ምክንያት አይኖርም።

የለንደኑን ኦሎምፒክ ካነሣን የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌደሬሺንም በውድድሩ ላይ አገሪቱን የሚወክሉትን 33 አትሌቶች መርጦ ሰይሟል። በነዚሁ ሁለት ጉዳዮች ላይ የፓሪስ ወኪላችንን ሃይማኖት ጥሩነህን በስልክ አነጋግሬያለሁ። ያድምጡ!

Wimbledon 2012 Roger Federer Finale Pokal Sieg
ምስል Reuters

በሌሎች የስፖርት ዓይነቶች ላይ እናተኩርና የዘንድሮው የዊምብልደን የቴኒስ ውድድር ትናንት በወንዶች በስዊትዘርላንዱ ተወላጅ በሮጀር ፌደረርና በብሪታኒያው ኮከብ በኤንዲይ መሪይ መካከል በተካሄደ ፍጻሜ ግጥሚያ ተጠናቋል። በዚሁ ግጥሚያ ፌደረር 2-1 በሆነ ውጤት ለሰባተኛ የዊምብልደን ድሉ ሲበቃ በዓለም የማዕረግ ተዋረድ ላይም ወደ ቀድሞ ቁንጮነቱ በመመለስ ብዙዎች ታዛቢዎችን ነው ያስደነቀው።

የብሪታኒያ ሕዝብ በኤንዲይ መሪይ አማካይነት ከ 76 ዓመታት በኋላ መልሶ ለዊምብልደን ድል ለመብቃት የጣለው ተሥፋ በአንጻሩ እንደገና ከንቱ ሆኖ ቀርቷል። በሴቶች አንድ ቀን ቀደም ሲል አሜሪካዊቱ ሤሬና ዊሊያምስ የፖላንድ ተጋጣሚዋን አግኔሽካ ራድቫንስካን በተመሳሳይ ውጤት በማሸነፍ ለአምሥተኛ የዊምብልደን ድሏ በቅታ ነበር።

Formel 1 Silverstone Mark Webber Siegerehrung Jubel
ምስል AP

በዚያው በብሪታኒያ ስንበቱን በተካሄደው የፎርሙላ-አንድ አውቶሞቢል እሽቅድድም ደግሞ የአውስትራሊያው የሬድ-ቡል ዘዋሪ ማርክ ዌበር አሸናፊ ሆኗል። የስፓኙ ተወላጅ የፌራሪው ዘዋሪ ፈርናንዶ አሎንሱ ሁለተኛ ሲሆን ጀርመናዊው ያለፉት ሁለት ዓመታት ሻምፒዮን ዜባስቲያን ፌትል ሶሥተኛ ወጥቷል። በአጠቃላይ ነጥብ አሎንሶ በ 129 የሚመራ ሲሆን ዌበር በ 116 ሁለተኛ፤ እንዲሁም ፌትል በ 100 ነጥቦች ሶሥተኛ ነው።

በእግር ኳስ ለማጠቃለል በዘንድሮው የአፍሪቃ ሻምፒዮና ሊጋ ውድድር ሰንበቱን በተካሄዱ የመጀመሪያ ግጥሚያዎች በምድብ-አንድ ውስጥ የቱኒዚያ ክለቦች ገዳሞቹ ነበሩ። ኤስፔራንስ የናይጄሪያን ሰንሻይን ስታርስ 2-0 ሲረታ ኤቱዋል ሣሄልም የአልጄሪያ ተጋጣሚውን ኤኤስኦ ችሌፍን 1-0 አሸንፏል። በምድብ ሁለት ውስጥ አል አህሊ ካይሮ የዴሞክራቲክ ሬፑብሊክ ኮንጎ ተጋጣሚውን ማዜምቤን 2-1 ሲያሸንፍ የጋናው ቤርኩም ቼልሢይ ደግሞ የግብጹን ዛማሌክን 3-2 ረትቷል።

መሥፍን መኮንን

ሸዋዬ ለገሠ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ