1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የሶሪያ አማፅያንን ማስታጠቅና ዉዝግቡ

ረቡዕ፣ ሰኔ 12 2005

አሳድ «በርግጥ ምዕራባውያን አማፅያንን ካስታጠቁ የአውሮፓ ምድር በአሸባሪዎች እጅ መውደቁ አይቀሬ ነው ብለዋል። አውሮፓ ለአማፅያን በምትሰጠው የጦር መሣሪያ እርዳታ የእጅዋን ማግኘትዋ አይቀርም ሲሉም አስጠንቅቀዋል። በዚህ የተነሳም በሶሪያው ፕሬዝዳንት አመለካከት አውሮፓ ከደማስቆ መንግሥት ጋር ከመተባበር ውጭ ሌላ ምርጫ አይኖራትም።

https://p.dw.com/p/18syK
ምስል Reuters

የሶሪያ አማፅያን ከዓለም ዓቀፉ ማህበረሰብ የጦር መሣሪያ እርዳታ እንደሚያስፈልጋቸው አጥብቀው ያሳስባሉ ። አሜሪካንን የመሳሰሉ አንዳንድ ምዕራባውያን ሃገራት አማፅያኑን ሊያስታጥቋቸው አቅደዋል ። ይህ እርምጃ ግን በእጅጉ እየተተቸ ነው ። ብዙዎች የጦር መሣሪያዎቹ የማይፈለጉ ወገኖች እጅ መግባታቸው አይቀርም የሚል ስጋት አላቸው ። የሶሪያው ፕሬዝዳንት በሽር አል አሳድ ደግሞ ምዕራባውያን ፣አማፅያንን ካስታጠቁ የእጃቸውን ማግኘታቸው አይቀርም ሲሉ እያስጠነቀቁ ነው ።
የሶሪያው ፕሬዝዳንት በሽር አልአሳድ ፣ ምዕራባውያን ለሶሪያ መንግሥት ተቃዋሚዎች የጦር መሣሪያ መስጠት ከጀመሩ አሸባሪነትን መደገፋቸው መሆኑ ግልፅ ነው ብለዋል ። አሳድ ፍራንክፉርተር አልገማይነ ከተባለው እለታዊው የጀርመን ጋዜጣ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ «በርግጥ ምዕራባውያን አማፅያንን ካስታጠቁ የአውሮፓ ምድር በአሸባሪዎች እጅ መውደቁ አይቀሬ ነው ብለዋል ።

Syrien Bürgerkrieg Freie Syrische Armee Panzer in Deir ez-Zor
ምስል Reuters

አውሮፓ ለአማፅያን በምትሰጠው የጦር መሣሪያ እርዳታ የእጅዋን ማግኘትዋ አይቀርም ሲሉም አስጠንቅቀዋል ። በዚህ የተነሳም በሶሪያው ፕሬዝዳንት አመለካከት አውሮፓ ከደማስቆ መንግሥት ጋር ከመተባበር ውጭ ሌላ ምርጫ አይኖራትም ። አሳድ በርግጥ እንደ አንድ ገለልተኛ የውይይት ተሳታፊ የሚታዩ ሰው አይደሉም ። በምዕራቡ ዓለም ውስጥ ለሶሪያ ተቃዋሚ ወገኖችም ቢሆን ጦር መሣሪያ መስጠቱ ብዙ ወቀሳዎች እየቀረቡበት ነው ። የጀርመን መንግሥትም ሆነ በርካታ ጠበብት ለተቃዋሚዎች የጦር መሣሪያ መሰጠቱን በጥራጣሬ ዓይን ነው የሚያዩት ። ዩናይትድ ስቴትስ ብሪታኒያና ፈረንሳይ ደግሞ አማፅያንን ለማስታጠቅ እያሰቡ ነው ። ዩናይትድ ስቴትስ እስካሁን በአብዛኛው ጥይት የማይበሳው ሰደሪያ ና የምሽት አጉሊ መነፅሮችን የመሳሰሉትን ነበር ወደ ሶሪያ የምትልከው ። ዋሽንግተን የአሳድ መንግሥት መርዘኛ የጦር መሣሪያዎችን መጠቀሙን አረጋገጥኩ ካለች ወዲህ ለሶሪያ አማፅያን የጦር መሣሪያ በመስጠት ድጋፏን ለማጠናከር ትፈልጋለች ። ስቶክሆልም ስዊድን በሚገኘው የሰላም ተቋም አጥኚ ፒተር ቬትዘማን የጦር መሳሪያዎችን መስጠት ግጭቱን ያስቆማል ብለው አያምኑም ። የጦር መሳሪያዎቹ ወደ ሌላ ወገን ሊተላለፉ ይችላሉ ፣ ይህ ምናልባትም ጦርነቱ እንዲባባስ ሊያደርግም ይችላል ።

Syrien Widerstandskämpfer Barrikade Waffe
ምስል Reuters

«ሶሪያ ውስጥ ለሚገኙ ማንኛቸውም አማጺ ቡድኖች የሚላክ የጦር መሣሪያ ወደ ማይፈለጉ ሰዎች እጅ ሊገባ የመቻሉ ግልፅ አደጋ አለ ። በአማፅያኑም በተሳሳተ መንገድ ጥቅም ላይ ሊውልም ይችላል ። ምናልባትም መሣሪያዎቹን የሚቀበሉት አማፅያን ዓለም ዓቀፍ የጦር ህግጋትና ደንቦችን የተከተለ ውጊያ እንዴት እንደሚካሄድ ላያውቁ ይችላሉ ። »
የሶሪያ አማፅያን በተለያዩ ቡድኖች የተለፋፈሉ ናቸው ወደ ሃገሪቱ የሚገባው የጦር መሣሪያም አክራሪዎች እጅ ይገባል የሚል ስጋት አለ ። መሣሪያዎቹ ለማይፈለጉ ወገኖች ከተሰጡ ደግሞ እንደ ቬትዘማን አባባል ጥፋቱ የከፋ ሊሆን ይችላል ።

« ያ ማለት የጦር መሣሪያዎቹን ህዝብን ለመፍጀት ይጠቀሙበታል ። በተለያዪ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶች ውስጥ ጥቅም ላይ ሊውልም ይችላል ። »
እነዚህ መሣሪያዎችም አንድ ቀን በምዕራቡ ዓለም ላይ ሊደገኑ የመቻላቸው ስጋት እንዳለ ነው ። ከልምድ እንደሚታወቀው በጦርነት ቀጣናዎች የጦር መሳሪያዎች ይጠፋሉ ።ለምሳሌ ከሊቢያው ጦርነት በኋላ የፈረንሳይ ፀረ ታንክ ሚሳይሎች ደብዛቸው ጠፍቷል ። እነዚህ መሳሪያዎች የማሊን መንግሥት በሚወጉት አማፅያን እጅ ሊሆኑ ይችላሉ ተብሎ ይገመታል ።

Krieg in Syrien Aleppo
ምስል Reuters

የጦር መሣሪያዎች ከሊቢያ ወደ ሶሪያ እየገቡ ነው የሚሉ ዘገባዎችም አሉ ። ከሁሉ አስጊው ግን ከምድር ወደ ሰማይ የሚወነጨፉ ፀረ አውሮፕላን ሚሳይሎች ጉዳይ ነው ። እነዚህ ሮኬቶች ለመንገደኛ አውሮፕላኖችም አደገኛ መሆናቸውን የጀርመን መንግሥት የጦር መሣሪያዎች ጠቢብ ሮልፍ ኒክል ያስረዳሉ
«በትከሻ የሚያዙ ፀረ አውሮፕላን ሮኬቶች በመሰረቱ አደገኛ ናቸው ።
በርሳቸው እምነትየህዝብ ማመላለሻ አውሮፕላኖችንም ለአደጋ ያጋልጣሉ ። ስለዚህ «ማንፓት» የሚባሉት እነዚህ መሳሪያዎች በዓለም ዓቀፍ የአየር ትራንስፖርት አገልግሎት ላይ አደጋ እንዳያስከትሉ መጀመሪያ ቁጥጥር ሊደረግባቸውና ተሰብስበውም ሊደመሰሱ ይገባል ። ሊቢያ ውስጥ እነዚህ መሳሪያዎች ተስብስበው ከጥቅም ውጭ እንዲሆኑ እገዛ አድርገናል ።»

ኒልስ ናውማን

ሂሩት መለሰ

አርያም ተክሌ