1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የሽብር ጥቃት ሥጋትና የጸጥታ ቁጥጥር በጀርመን

ዓርብ፣ ኅዳር 10 2003

ናምቢያ የተያዘው ቦምብ መሳይ ጥቅል ቦርሳ ለሙከራ የተዘጋጀ እንደሆነ ተገለጸ። ጀርመን እስከመጪው ታህሳስ መጨራሻ የሚዘልቅ የደህንነት ቅጥጥር እንደምታደርግ አስታወቀች።

https://p.dw.com/p/QDj1
ዲ ሚዚየርምስል dapd

የአውሮፕላኑ መነሻ ዊንድሆክ ናምቢያ። መድረሻ ሙኒክ ደቡባዊ ጀርመን። 296 መንገደኞችንና 10 የአውሮፕላኑን ሰራተኞችን የያዘው አውሮፕላን ግን ዊንድሆክን በተያዘለት የጊዜ ሰሌዳ አለቀቀም። 6 ሰዓታትን የሚያዘገየው ድንገተኛ ክስተት ተፈጠረ። አውሮፕላኑ ላይ ሊጫን የተዘጋጀውና በሰዓት የተጠመደ ቦምብ መሳይ ጥቅል መሳሪያ በፍተሻ ተገኘ የሚለው የፖሊስ መረጃ በእርግጥ አስደንጋጭ ነበር። የናምብያ ፖሊስ እንዳስታወቀው ቦርሳ ውስጥ በፕላስቲክ የተጠቀለለ በሽቦ የተያያዘና ሰዓት ጠብቆ የሚፈነዳ ቦምብ የሚመስል ጥቅል መሳሪያ እሮብ ዕለት ተገኝቷል። ቦርሳው ወደየት ሊወሰድ እንደታሰበ የሚገልጽ መረጃ በላዩ ላይ ባለመኖሩ በተፈጠረው ጥርጣሬ ፖሊስ ከሻንጣዎች መሃል ለይቶ ሊያጣው እንደቻለ የናምቢያ ፖሊስ አስታውቋል። የጀርመን የሀገር ውስጥ ደህንነት ሚኒስትር ቶማስ ዴ ሚዜሪ ዛሬ እንደገለጹት ቦምቡ መሳዩ ጥቅል ለሙከራ የተደረገ ነው።

ድምጽ

ወደሙኒክ የታሰበው በረራ በእርግጥ በስድስት ሰዓት ዘግይቷል። ሙከራው በህንድ ሙምባይ የተፈጸመውን የሽብር ጥቃት ዓይነት ሊሆን እንደታሰበ ነው የጀርመን የሀገር ውስጥ የደህንነት ሚኒስቴር ከትላንት በስቲያ ያስታወቀው።ዛሬ ግን ለሙከራ የተቀመጠ የደህንነት ስራውን ለመፈተሽ የታሰበ እንደሆነ ነው የተገለጸው።ጀርመን ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ የሽብር ጥቃት ሊፈጸምባት እንደሚችል ምልክቶች እንዳሉ የሚሳዩ መረጃዎች እየወጡ ነው። የሀገር ውስጥ የደህንነት ሚኒስቴር ዴ ሚዜሪ እንዳስታወቁት ጀርመን በዚህ ወር ውስጥ ከፍተኛ የሆነ የሽብር ጥቃት የፈጸምባት እንደሚችል የተለያዩ የደህንነት ምንጮች መረጃዎችን አቅርበዋል። መረጃዎቹ በአሜሪካና በአውሮፓ በተለይም በጀርመን በአልቄይዳ የታቀዱ ጥቃቶች ሊፈጸሙ እንደሚችሉ የሚያሳዩ ናቸው። ያለፈው ረቡ በናምቢያ አውሮፕላን ማረፊያ ተያዘ የተባለው ተጠርጣሪ የቦምብ ጥቅል ጀርመን በሽብር ጥቃት አንጻር የተደቀነባትን ስጋት ያመላከተ ነው የሚል አስተያየት ተስጥቷል። ዛሬ ለሙከራ የታቀደ ነበር የተባለው የናምቢያው የቦም መሳይ ቦርሳ ጉዳይ መነሻ አድርገው የተናገሩት የአፍሪካ የደህንነት ጥናት ተቋም ባለሙያ ሄነሪ ቦሾፍ እንዲህ ዓይነቱ ሙከራ ጀርመን ላይ ያነጣጠረው በአፍጋኒስታን ባላት ወታደራዊ ተሳትፎ ሊሆን እንደሚችል ነው የገለጹት።

ድምጽ

«ጀርመን በአፍጋኒስታን ባለው ጦርነት ተሳታፊ ነች። ወታደሮቿን አስገብታለች። ይህ እንደምክንያት ሊነሳ ይችል ይሆናል። የጀርመን አውሮፕላን ዒላማ የሆነውም ለዚያ ነው። ሆኖም ለዚህ ሙከራ ተባባሪ የሚሆነው ማን ነው የሚለው ጥያቄ ለጊዜው ክፍት እንደሆነ ነው ያለው።»

ምንም እንኳን የረቡ ለቱ በናምቢያ ዊንድሆክ የተፈጸመው ለፍተሻ የታሰም ይሁን ለሽብር ጥቃት የተዘጋጀ ቦም መሳይ ጥቅል ቦርሳ የመገኘቱ ዜና ናምብያን ከሽብር ጥቃት አንጻር ስሟን የሚያነሳ ሆኗል። የአፍሪካ የደህንነት ጥናት ተቋም ባለሙያ ሄነሪ ቦሾፍ ሙከራው ቢሆን እንኳን ከናምቢያ የተወጠነ ስለመሆኑ ይጠራጠራሉ።

ድምጽ

«ሰፊውን የደቡብ አፍሪካን ክፍል በተመለከተ ግምትህን ልታስቀመጥ ትችላለህ። ሆኖም ናምቢያን በተመለከተ አይመስለኝም። በናምቢያ ያለው ሙስሊሙ ማህበረሰብ ቁጥሩ እጅግ አነስተኛ ነው። እያንዳንዱ እንቅስቃሴአቸውበፖሊስና በአከባቢው የስለላ መስሪያ ቤት በቀላሉ ሊደረስበት የሚችል ነው። ያም ቢሆን እንኳን አጠራጣሪ ነው። ማንም ያድርገው ግን፤ በዚያ አከባቢ ቢሆን እንኳን ከምስራቅ አፍሪካ ውይም ከሌላው የዓለም ክፍል ሊሆን ይችላል።»

ጀርመን የደህንነት ኃይሏን በተጠንቀቅ እንዲሆን አዛለች። እስከ መጪው ታህሳስ ወር መጨረሻ ድረስ የሚዘልቅ ጥብቅ የደህንነት ስራ እነደሚኖር አስታውቃለች። ከተለያዩ የመረጃ ምንጮች የተገኙት መረጃዎች በጀርመን በተለይ በገና የገበያ ስፍራዎች ከፍተኛ የሽብር ጥቃት እንደሚፈጸም የሚስጠነቅቁ ናቸው። በዚህም ሳቢያ በተለይ በአውሮፕላን ማረፊዎችና በባቡር ጣቢያዎች ፍተሻው በተጠናከረ ሁኔታ እየተካሄደ ነው። ጀርመን በሙስሊም ጽንፈኞች በምድሯ ላይ ጥቃት ተፈጽሞባት አያውቅም። ይሁንና የከሸፉ ሙከራዎች በተደጋጋሚ ተከስተዋል። በ2006 እ.ኤ.አ በኮኝ የተገኘው በቤት ውስጥ የሚዘጋጅ ቦምብ የያዘ ቦርሳ ምናልባት ለሽብር ጥቃት በጣም የቀረበ ሙከራ ነበር። እ.ኤ.አ በ2001 መስከረም 11 በአሜሪካ በተፈጸመው ጥቃት ተሳታፊ ከሆኑት መሃል ሶስቱ ለጥቃቱ ወደ አሜሪካ ከመብረራቸው በፊት ሀምቡርግ በተሰኘችው የሰሜናዊ ጀርመን ከተማ ይኖሩ እንደነበር ይታወሳል።

መሳይ መኮንን

ነጋሽ መሐመድ