1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የተመ የልማት ፋይናንስ ጉባኤ በአዲስ አበባ

ማክሰኞ፣ ሐምሌ 7 2007

በርካታ የሀገር መሪዎች እና በብዙ ሺህ የሚገመቱ ተሳታፊዎች የተገኙበት የተባበሩት መንግሥታት የልማት ፋይናንስ ጉባኤ ዛሬ አዲስ አበባ ውስጥ ተከፈተ።

https://p.dw.com/p/1Fy1a
Äthiopien International Conference on Financing for Development in Addis Abeba
የፋይናንስ እና የልማት ጉባኤምስል picture-alliance/dpa/M. Wondimu Hailu

[No title]

ድህነትን ለማጥፋት እና የአየር ንብረት ለዉጥን ስለመቋቋም የሚነጋገር የአራት ቀናት ጉባኤ ዛሬ አዲስ አበባ ላይ ተጀመረ። የስብሰባዉ ዋና ዓላማ አዳጊ ሃገራት ዘላቂነት ላለዉ ልማት የሚያዉሉትን በጀት ልዩነት ማጥበብ የሚችል ለድጋፍ የሚዉል ገንዘብ የሚገኝበትን መንገድ መቀየስ ነዉ። እንዲህ ዓይነቱ ጉባኤ ሲካሄድ የአሁኑ ለሶስተኛ ጊዜ ሲሆን ፣ በአፍሪቃ ሲደረግ ደግሞ የአዲስ አበባው የመጀመሪያው መሆኑ ነው። የተመ የልማት ፋይናንስ ጉባኤ ከዚህ ቀደምም ሞንቴሪ እና ዶሃ ላይም በተለያዩ ጊዜያት ተካሂዷል። አዲስ አበባ ላይ ተገኝተዉ የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የተመድ ዋና ጸሐፊ ባን ሙን በስብሰባዉ የተገኙት መሪዎችና ሚኒስትሮች አግባቢ ዉሳኔዎች ላይ ለመድረስ የየግል ፍላጎቶቻቸዉን ወደጎን እንዲተዉ አሳስበዋል። አያይዘዉም፤

«እነዚህን እንቅፋቶች ለማለፍ እንዲሁም ያሉትና የሚመጡትን ችግሮች በመወጣት ግቦችና ዓላማዎችን ለማሳካት፤ የተደረሱ ስምምቶች፣ እርምጃዎችና ተነሳሽነቶች አሁን ያለዉን ዓለም አቀፍ የልማት ትብብር ከግብ እንዲያደርሱ የተባበረ የጋራ የገንዘብ ድጋፍ ያስፈልጋል። የገንዘብ ድጋፍ ዓላማዎችም ለሶስት ዘላቂ የልማት ዘርፎች እንዲሁም እአአ ከ2015,ም በኋላ ለሚዘልቀዉ የተመድ የልማት አጀንዳዎች ይሆናል።»

የተመድ ለአምዓቱ አቅዷቸዉ የነበሩት የልማት ግቦች በያዝነዉ ጎርጎሪዮሳዊ ዓመት መጨረሻ በቀጣይ የ15ዓመት ዘላቂ የልማት ግቦች እንዲተካ አቅዷል። ከጎርጎሪዮሳዊዉ 2015 እስከ 2030 በሚዘልቀዉ እቅድም ድህነትን ማጥፋት እና ዓለም አቀፍ ዘላቂ የኃይል ምንጭን ማቅረብን ጨምሮ 17 ዓበይት ጉዳዮች ተካተዉበታል። ከጉባኤው ተካፋዮች አንዱ ፤የጀርመኑ የልማት ሚኒስትር ጌርድ ሙለር ጀርመንን ወክለው አዲስ አበባ ይገኛሉ። የጀርመኑ ፖለቲከኛ የበለፀጉ ሀገራት በቅናሽ ዋጋ ምርቶቻቸውን እንዲያቀርቡ ሲባል አዳጊ ሀገራት የሚበዘበዙበት ሁኔታ መቅረት አለበት ሲሉ ተሰምተዋል። ጉባኤውን የአዲስ አበባው ዘጋቢያችን ጌታቸው ተድላ ኃይለ ጊዮርጊስ ተከታትሏል።

ጌታቸው ተድላ ኃይለ ጊዮርጊስ

ልደት አበበ

አርያም ተክሌ