1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የትራምፕ ቃለ-ምልልስ እና አውሮጳ

ሰኞ፣ ጥር 8 2009

የፊታችን ዓርብ በይፋ ስልጣናቸውን የሚረከቡት ሥዩሙ የዩኤስ አሜሪካ ፕሬዚደንት ዶናልድ ትራምፕ ስለ አውሮጳ ኅብረት እና የሰሜን አትላንቲክ የጋራ መከላከያ ኪዳን፣ ኔቶ፣ እንዲሁም፣ ስለሚከተሉት የኤኮኖሚ ፖሊሲ ለጀርመን «ቢልት» እና ለብሪታንያ «ዘ ታይምስ»  ጋዜጦች  ቃለ ምልልስ ሰጡ።

https://p.dw.com/p/2Vskz
USA Donald Trump im Interview mit Kai Diekmann
ምስል picture alliance/dpa/BILD/D. Biskup

 በቃለ ምልልሱ ላይ ትራምፕ የኔቶን አስፈላጊነት አጠያይቀዋል፣ ብሪታንያ ከአውሮጳ ኅብረት ለመውጣት የወሰደችውን ውሳኔ በማድነቅ ሌሎችም የርሷን አርአያ ይከተላሉ ብለው እንደሚጠብቁም  በቃለ ምልልሳቸው ጠቅሰዋል። ይህ አነጋገራቸው በዓለም አቀፍ ደረጃ ቅሬታን ፈጥሮዋል። ቃለምልልሱን ተከትሎ በርካታ የአውሮጳ ኅብረት አባል ሃገራት ኅብረቱ አንድነቱን እና ዓለም አቀፍ ትብብሩን እንዲያጠናክር ጥሪ አቅርበዋል። ትራምፕ የጀርመን መራሒተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል የተከተሉትን የስደተኞች አቀባበል ፖሊሲን በጥብቅ ነቅፈዋል። 
«ታላቅ ፣ ታላቅ መሪ ነበሩ። ግን፣ በጣም ብዙ ጥፋት ያስከተለ አንድ ከባድ ስህተት የፈፀሙ ይመስለኛል። ይኸውም፣ ከየትም የመጡትን እነዚያን ሁሉ ሕገ ወጥ ስደተኞች ሀገራቸው ማስገባታቸው ነው። በርግጥም፣ ከየት እንደመጡ ማንም የሚያውቅ የለም።»
 ከሥዩሙ አሜሪካዊ ፕሬዚደንት ትራምፕ ቃለምልልስ በኋላ የጀርመን መራሒተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፣ አውሮጳውያን ዕጣ ፈንታቸው በእጃቸው መሆኑን በማመልከት፣ 27ቱ የህብረቱ አባል ሃገራት ኤኮኖሚያቸውን ማጠናከር እና ወደፊት የሚጠብቁዋቸውን ፀረ ሽብሩን ትግል የመሳሰሉ ተግዳሮቶችን  ማሸነፍ እንዲችሉ ጠንክረው እንደሚሰሩ አስረድተዋል።

 

አርያም ተክሌ

አዜብ ታደሰ