1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ትራምፕ በ45 ተኛ የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዝዳንትነት ተሰየሙ

ዓርብ፣ ጥር 12 2009

ትራምፕ እለቱን የጀመሩት ከባለቤታቸው ጋር በቤተ ክርስትያን ስነስርዓት በመታደም ሲሆን ከዚያ በኋላም ተሰናባቹ ፕሬዝዳንት ባራክ ኦባማ እና ባለቤታቸው ሚሼል ኦባማ የቁርስ ግብዣ አድርገውላቸዋል።

https://p.dw.com/p/2W9nk
USA Amtsübernahme Trump Eid
ምስል Getty Images/C. Somodevilla

ባለፈው ጥቅምት መጨረሻ በተካሄደው የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ ያሸነፉት ሪፐብሊካኑ ዶናልድ ትራፕምበ45 ተኛ የአሜሪካን ፕሬዝዳንትነት ቃለ መሀላ ፈጸሙ ። ትራምፕ ቃለ መሀላ ከፈፀሙ በኋላ የሚያሰሙት ንግግር ለሀገሪቱ ባላቸው ራዕይ ላይ ያተኮረ እና ከ20 ደቂቃ የሚበልጥ እንደማይሆን አማካሪዎቻቸው ተናግረዋል። ትራምፕ እለቱን የጀመሩት ከባለቤታቸው ጋር በቤተ ክርስትያን ስነስርዓት በመታደም ሲሆን ከዚያ በኋላም ተሰናባቹ ፕሬዝዳንት ባራክ ኦባማ እና ባለቤታቸው ሚሼል ኦባማ የቁርስ ግብዣ አድርገውላቸዋል።  የትራምፕን በዓለ ሲመት ለማክበር በርዕሰ ከተማ ዋሽንግተን በመቶ ሽህዎች የሚቆጠር ህዝብ ታድሟል። የትራምፕ ተቃዋሚዎች ኅብረት ፈጥረው በዓለ ሲመቱ ወደ ሚካሄድበት ስፍራ የሚያመሩ መንገዶችን በመዝጋት አከባበሩን ለማስተጓጎል ሙክራ ማድረጋቸው ተዘግቧል። ትናንት ማታ በትራምፕ ደጋፊዎች እና ተቃዋሚዎች መካከል ዋሽንግተን ውስጥ የተካሄደውን ግጭት ለማስቆም ፖሊስ ኬሚካሎችን ረጭቶ ነበር። የ70 ዓመቱ ቱጃሩ ዶናልድ ትራምፕ አሜሪካንን በፕሬዝዳንትነት በመምራት የመጀመሪያው በእድሜ የገፉ መሪ ይሆናሉ። ትራምፕ በዓለ ሲመታቸው ከመጀመሩ አስቀድሞ በትዊተር ባስተላለፉት መልዕክት ሁሉም ነገር ዛሬ ይጀመራል፤ ንቅስቃሴው ይቀጥላል ፤ ሥራው ይጀመራል ብለዋል። የትራምፕ በዓለ ሲመት በጥብቅ የፀጥታ ጥበቃ ነው የሚካሄደው። ወደ ፕሬዝዳንታዊ መኖሪያቸው የሚያመሩ ጎዳናዎች በሰው አልባ አውቶብሶች እና ከባድ ተሽከርካሪዎች እንዲዘጉ ተደርጓል።

ኂሩት መለሰ

አዜብ ታደሰ