የአበባ፣ አታክልትና ፍራፍሬዎች የውጭ ገበያ ገቢ
ረቡዕ፣ ሐምሌ 30 2006በተለይ ኢትዮጵያ ለውጭ ገበያ የምትልካቸው የፅገሬዳ አበባዎች በአውሮጳ ገበያ እውቅና አግኝተዋል። ኢትዮጵያ እንደ የአበባ ምርቱም ባይሆን ከአታክልት እና ፍራፍሬ ከመሳሰሉት ዘንድሮም ከውጭ ንግድ ገቢ አግኝታለች። እንደውም ካለፈው 2005 ዓ,ም ጋ ሲነፃፀር በ 6 . 4 ከመቶ አድጓል ይላሉ የኢትዮጵያ የአበባ፣ አትክልትና ፍራፍሬ ልማት ድርጅት ዋና ዳሬክተር አቶ አለም ወልደገሪማ። እንደ እሳቸው የዘርፉ ጠቅላላ የውጭ ንግድ ገቢ እንደውም ከ245 ሚሊዮን ዶላር ከፍ ሊል ይችላል።
ከአበባ199,74 ሚሊዮን ከአትክልት 40 ሚሊዮን እና 6 ሚሊዮን ደግሞ ከፍራፍሬ የዉጭ ሽያጭ እንደተገኘ ኃላፊው ገልፀውልናል። ከአበባው የተገኘው ገቢ ከሌሎቹ ዘርፎች ጋ ሲነፃፀር ጎልቶ የታየበት ምክንያት አብራርተውልናል።
እንደ ሶማሊያ እና ጅቡቲ ያሉ ሃገራት ብቻ ሳይሆን ኢትዮጵያ ሁሉንም የምርት ዘርፎቿን ለአውሮጳ ገበያ ማቅረብ ብትችል ፍላጎቷ ነው። ነገር ግን ይህ ያልሆነበት ሁለት ዋና ዋና ምክንያቶች አሉ። አንዱ የሽያጩ ዋጋ መጠነኛ መሆን፤ ሌላው ደግሞ የጥራት ጉዳይ።
ምንም እንኳን ወደአዉሮጳ ገበያ በስፋት ለመግባት የጥራት ማረጋገጫዉን ለማግኘት ቀላል እንዳልሆነ የኢትዮጵያ የአበባ፣ አትክልትና ፍራፍሬ ልማት ድርጅት ኃላፊ ቢገልፁም ከዘርፉ የሚገኘዉን የዉጭ ምንዛሪ የተመለከትን እንደሆነ ግን ቀላል እንደማይባል የዘንድሮዉ መጠን ያመላክታል። ነገር ግን በማምረቱ ሂደት ውስጥ ሥራ ላይ የሚዉሉት የተለያዩ ኬሚካሎች በአካባቢው ተፈጥሮ ላይ ተፅዕኖ እንዳይፈጥሩ እንዴት ያለ ጥንቃቄ ይወሰዳል። ለነዚህ ችያቄዎች በሙሉ አቶ ዓለም ወልደገሪማ ምላሽ ሰጥተውናል።
ልደት አበበ
ሸዋዬ ለገሠ