1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአቶም ኃይል ማመንጫ አውታር

ረቡዕ፣ መጋቢት 7 2003

የዓለም መገናኛ ብዙኀን ፣ ባለፈው ሳምንት ዓርብ፤ ሰሜን ምሥራቅ ጃፓንን ክፉኛ የናጠውንና እጅግ ኃይለኛ የውቅያኖስ ማዕበል አስነስቶም በህዝብ ላይ ብርቱ ጥፋት በንብረት ላይም ሰፊ ውድመት ስላደረሰው የተፈጥሮ አደጋ በሰፊው ሲያትቱ ሰንብተዋል።

https://p.dw.com/p/R9pa
የአቶም ኃይል ማመንጫ አውታር
ምስል picture-alliance/ dpa

አደገኛ የምድር ነውጥ፤ የእሳተ ገሞራ ፍንዳታና የመሳሰለው የተፈጥሮ አደጋ በሚጠናወተው፣ «የእሳት ቀለበት» በተሰኘው የዓለም ክፍል የምትገኘው በዘመናዊ ቴክኖሎጂና እንዱስትሪ የበለጸገችው ጃፓን፣ የምድር ነውጥን የሚቋቋሙ ሰማይ ጠቀስ ህንጻዎችን በመገንባት የወቅያኖስ ማዕበልንም ለመከላከል የሚያስችሉ እርምጃዎችን በመወሰድ ግንባር ቀደም ሀገር መሆኗ ቢታወቅም፤ ባለፈው ሳምንት የደረሰባት ግን በዓይነቱ የመጀመሪያና ለመከላከልም ያልተቻለ መሆኑን ዓለም በመላ የመሠከረው ነው። በሪኽተር መለኪያ 9 ገደማ የደረሰው እጅግ ኃይለኛው ነውጥ፣ ያን ዕለት ቀኑን በ 1,6 ማይክሮ ሴኮንድ ከማሳጠሩም ፣ ምድራችን የምትሽከረክርበት የራሷ ዛቢያ ከመስመሩ በ 10 ሴንቲሜትር ያህል እንዲያፈነግጥ አድርጓል፤ እጅግ ኃይለኛው የውቅያኖስ ማዕበል፤ የጃፓንን ጠረፍ በ 2,4 ሜትር ገፍቶታል። የምድሩ ነውጥ፣ ይባስ ብሎ በአቶም ኃይል ማመንጫ አውታሮቿ ላይ፤ ፍንዳታዎች እስኪያጋጥሙ ድረስ ያስከተለው እንከን ፣ የሰሞኑ ዐቢይ መነጋገሪያ ሆኗል። አሁን ይበልጥ አነጋጋሪ የሆነው ፤ የአቶም ኃይል ማመንጫ አውታር ከጥቅሙ ጉዳቱ የሚያመዝንበት ሁኔታ መኖሩ ፣ ይበልጥ ግንዛቤ ያገኘ በመምሰሉ ነው። ጤናይስጥልኝ እንደምን ሰነበታችሁ? የአቶም ኃይል ማመንጫ አውታር፤ እንዴትና በምን ኃይል ነው የሚሠራው ? በዚህ ርእሰ ጉዳይ ላይ የላቀ ማብራሪያ ለማግኘት በማይንትዝ ጀርመን የዮሐንስ ጉተንበርግ ዩኒቨርስቲ ውስጥ፤ የኑክልየር ሥነ ቅመማ (ኬምስትሪ) ተመራማሪና መምህር የሆኑትን ዶ/ር ጌዴዎን ጌታሁንን አነጋግረናል ፤ ጭውውታችን ከ 15 ሴኮንዶች በኋላ ይቀጥላል። ተክሌ የኋላ --

ተክሌ የኋላ

ነጋሽ መሐመድ