1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአ.አ ዩኒቨርሲቲ የታሪክ የትምህርት ዘርፍና ፈተናው

ረቡዕ፣ መጋቢት 3 2006

በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የታሪክ የትምህርት ክፍል በተማሪዎች ብዙም የማይመረጥበት ሁኔታ የትምህርት ዘርፉን ሕልዉና ሳይፈታተን እንደሚይቀር እየተገነገረ ነዉ።

https://p.dw.com/p/1BOgt
Hauptcampus der Universität Addis Abeba AAU
ምስል DW

ወደዩኒቨርሲቲ የመግባት እድል ከሚያገኙ ተማሪዎች አብዛኞቹ ከምረቃ በኋላ ሥራ ከማግኘት እድል ጋ በተያያዘ የትምህርት ዘርፉን ከመምረጥ ሲቆጠቡ፤ 70/30 የተሰኘዉ የትምህርት ፖሊሲም የበኩሉን አስተዋፅኦ ማድረጉን ታዛቢዎች ያመለክታሉ። እንዲያም ሆኖ ከዘርፉ ምሁራን አንዳንዶች በቀጣይ በሚደረጉ እንቅስቃሴዎች ሕልዉናዉ ተጠናክሮ ይቀጥላል የሚል ተስፋ አላቸዉ።

በቅርቡ ነዉ የታሪክ የትምህርት ክፍል በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የተከፈተበትን 50ኛ ዓመት ያከበረዉ። በወቅቱም በያዝነዉ የትምህርት ዓመት በትምህርት ክፍሉ ለመማር የተመዘገበ ተማሪ አለመኖሩ ተገልጿል። ለዚህ እንደምክንያት ከተጠቀሱት መካከል 70/30 በተባለዉ መርኀግብር መሠረት በማኅበራዊ ሳይንስ የትምሕርት ዘርፍ ባጠቃላይ የሚመደቡ በመቶዎች የሚቆጠሩ ተማሪዎች ወደበርካታ የትምህርት ዘርፎች መከፋፈላቸዉ አንዱ ነዉ። በዚህም ተማሪዎች የተሻለ የሥራ ዕድል ያስገኝልናል ብለዉ ወደሚያምኑት የትምህርት ክፍል ማዘንበላቸዉ የታሪክ ትምህርት ዘርፍን መራጮች ቁጥር እንዳሳነሰ ብሎም ዘንድሮ ፈላጊም እንዳሳጣ ተገልጿል።

MStudenten auf dem Campus der Universität Addis Abeba
ምስል DW

የመጀመሪያ ዲግሪያቸዉን በታሪክ ያገኙት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የአርኪዮሎጂ እና የቅርስ አስተዳደር ትምህርት ክፍል አቶ መንግስቱ ጎበዜ ወርቁ ለዚህ ዋና ያሉትን አንደኛዉ ምክንያት ይኸዉ ተምሮ ሥራ ከማግኘት ዕድል ጋ የተገናኘ ነዉ።

ከዚህ ሌላም የትምህርት ፖሊሲዉ ለሳይንስ እና ቴክኒዎሎጂ የሰጠዉ ከፍተኛ ግምትም 70/30 በሚባለዉ አሠራር የሚገለጸዉ ሌላኛዉ የተጽዕኖዉ ምክንያት ሊሆን እንደሚል ነዉ አቶ መንግስቱ ያመለከቱት። በተጨማሪም ለታሪክ ትምህርት የሚሰጠዉ ትኩረት ማነስም አንዱ ሰበብ ሊሆን እንደሚችልም ገልጸዋል።

ሁኔታዉን በቅርብ የሚከታተሉ ወገኖች ዛሬ የተጀመረዉ የዘርፉ ተማሪዎችን ማጣት ዉሎ ሲያድር በሌሎች የትምህርት ደረጃዎች የታሪክ መምህር የማይገኝበትን አጋጣሚ በሂደት ሊፈጥር ይችላል የሚል ስጋት አላቸዉ። በዚህም ምናልባት ታሪክ ራሱ ታሪክ ሆኖ እንዳይቀር ከሚል እስቤ የዘርፉ ምሁራንና የሚመለከታቸዉ አካላት ትኩረት ሰጥተዉ እንዲንቀሳቀሱ ያሳስባሉ። ከዩኒቨርሲቲዉ ድረገጽ የተገኘዉ ዝርዝር መረጃ የታሪክ ትምህርት ክፍል በጎርጎሪዮሳዊዉ 1960/61 ከተከፈቱ ቀዳሚ የትምህርት ዘርፎች አንዱ መሆኑንና በዩኒቨርሲቲዉ ታሪክም አንጋፋነቱን ያመለክታል።

በነገራችን ላይ አድማጮች ይህን አስመልክቶ አስተያየታቸዉን የጠየቅናቸዉ የዩኒቨርሲቲዉ የታሪክ ትምህርት ክፍል ፕሬዝደንት መንገድ ላይ በመሆኔ ከደቂቃዎች በኋላ ደዉሉልኝ ብለዉ ደጋግመን ብንደዉል ስልካቸዉ መዘጋቱን የሚገልፅ ምልክት ብቻ ነዉ የሚሰጠዉ። የትምህርት ክፍሉ ክብረ በዓል ላይ ከተገኙና በዘርፉ አንጋፋ ከሚባሉ ምሁራን አንዳንዶቹን ስንጠይቅ ደግሞ የትምህርት ክፍሉ ኃላፊ ቢናገሩ እንደሚሻል በመጠቆም ለጊዜዉ ለመናገር እንደማይሹ ገለልጸዉ አስተያየታቸዉን ከመስጠት መቆጠብን መርጠዋል።

ሸዋዬ ለገሠ

ተክሌ የኋላ