1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአዉሮጳ ሕብረት፥ ግሪክና ፈረንሳይ

ማክሰኞ፣ ሚያዝያ 30 2004

የአዉሮጳ ሕብረት አባል መንግሥታት አመታዊ በጀታቸዉን ለመቀነስ ያሳለፉትን ዉሳኔ በግሪክና በፈረንሳይ ምርጫ ዉጤት ሰበብ እንዳይለዉጡ የሕብረቱ ኮሚሽን ጠየቀ።

https://p.dw.com/p/14rvY
ምስል dapd

የአዉሮጳ ሕብረት አባል መንግሥታት አመታዊ በጀታቸዉን ለመቀነስ ያሳለፉትን ዉሳኔ በግሪክና በፈረንሳይ ምርጫ ዉጤት ሰበብ እንዳይለዉጡ የሕብረቱ ኮሚሽን ጠየቀ።ግሪክና ፈረንሳይ ዉስጥ በተደረገዉ ምርጫ የአዉሮጳ ሕብረት የሚከተለዉን የገንዘብ መርሕ የሚቃወሙ ፓርቲዎች ማሸነፋቸዉ ሕብረቱን አስግቷል።በተለይ የግሪክ ሕዝብ የአዉሮጳ ሕብረትን የቁጠባና የብድር መርሕን በግልፅ የሚተቹ ፓርቲዎችን መምረጡ የአቴናንና የብራስልስን ግንኙነት እንዳያበላሸዉ አስግቷል።የሕብረቱ ኮሚሽን ቃል አቀባይ ፒያ አሕረንኪልደ እንዳሉት ግሪክ ከሕብረቱ ጋር ያደረገችዉን ስምምነት አዲሱ መንግሥት ማክበር አለበት። «የወደፊቱ የግሪክ መንግሥት ግሪክ የተቀበለቻቸዉን ዉሎች ያከብራል የሚል ተስፋ አለን»ግሪክ ዉስጥ ባለፈዉ እሁድ በተደረገዉ የምክር ቤት ምርጫ የሁለተኝነት ደረጃ ያገኘዉን ሴሪዛ የተሰኘዉ ፅንፈኛዉ የግራ ፓርቲ ተጣማሪ መንግት ለመመስረት ከሌሎች ፓርቲዎች ጋር ዛሬ መወያየት ጀምሯል።የፓርቲዉ መሪ አሌክሲስ ፀፒራስ በአበዳሪ ሐገራት የተጫነ «አረመኒያዊ» ያሉትን የቁጣ መርሕ የሚቃወም ካቢኔ ለማማቋቋም ይጥራሉ።የፀፒራስ ፓርቲ መንግሥት እንዲመሠርት የተጠየቀዉ በእሁዱ ምርጫ የመጀመሪያዉን ደረጃ ያገኘዉ አዲሱ ዲሞክራሲ የተሰኘዉ ወግ አጥባቂ ፓርቲ መንግሥት መመስረት ሥላልቻለ ነዉ።

አዜብ ታደሰ

ሸዋዬ ለገሰ