1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአዉሮጳ ኅብረት ጉባኤ ፍፃሜ

ዓርብ፣ ታኅሣሥ 8 2008

የአዉሮጳ ኅብረት መሪዎች የተሰናባቹን ጎርጎሪዮሳዊ ዓመት 2015 የመጨረሻ ጉባኤ ዛሬ ከሰዓት በኋላ አጠናቀቁ። ለሁለት ቀናት በተካሄደዉ በዚህ ጉባኤ ላይ የኅብረቱ አባል ሃገራት መሪዎች አዉሮጳን ስላስጨነቀዉ የስደተኞች ጉዳይ ብዙ እንደተከራከሩ ከጉባኤዉ የወጡት መረጃዎች ያመለክታሉ።

https://p.dw.com/p/1HQ89
Belgien EU Gipfel Gruppenbild
ምስል Getty Images/D. Mouhtaropoulos

[No title]

ከኅብረቱ ስለመዉጣት ሕዝበ ዉሳኔ ልታካሂድ ያቀደችዉ ብሪታንያ፤ በአባልነት ሊያቆያት ይችላል በሚል ጠቅላይ ሚኒስትሯ ያቀረቧቸዉ ነጥቦች ላይም መሪዎቹ ተወያይተዋል። በጉባኤዉ ላይም ለስደተኞች መበራከት የኅብረቱ ፕሬዝደንት ዶናልድ ቱስክ የዉጭ ድንበርን ባግባቡ ካለመቆጣጠር የመጣ ስህተት መሆኑን ለተሰብሳቢዎቹ ማመናቸዉ ተገልጿል። የአውሮፓ ሕብረት አባል ሃገራት መሪዎች በአሸባሪነት ላይ የጀመሩትን ዘመቻ ለማጠናከርም ቃል ገብተዋል ። መሪዎቹ ትናንትናና ዛሬ ባካሄዱት በጎርጎሮሳዊው 2015 ዓም የመጨረሻ ጉባኤያቸው ራሱን እስላማዊ መንግሥት ብሎ ከሚጠራው በምህፃሩ IS ከተባለው ቡድን ጋር የሚካሄደውን ትግል አጠናክሮ መቀጠል በሚቻልባቸው መንገዶች ላይ መክረዋል ።መሪዎቹ ዛሬ ከሰዓት በኋላ ጉባኤያቸውን ሲያጠቃልሉ የፅንፈኞችን የገንዘብ ምንጮች ለማድረቅ አፈጣኝ እርምጃ እንዲወሰድም ጠይቀዋል። የአውሮፓ ህብረት አባል ሃገራትን የከፋፈለው በ2015 ወደ ክፍለ ዓለሙ የጎረፈው ስደተኛ ጉዳይም ጉባኤው ትኩረት ሰጥቶ ከተወያየባቸው ነጥቦች መካከል አንዱ ነበር ። የጀርመን መራሂተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል እንዳሉት አውሮፓ የገባውን ወደ አንድ ሚሊዮን የሚጠጋ ስደተኛ የመከፋፈል ጉዳይ በፍጥነት መከናወን እንዳለበት ግንዛቤ ጉባኤተኞቹ ግንዛቤ ወስደዋል ።
«እርግጥ ነው ስደተኞች በብዛት በሚገኙባቸው ሃገራት መከናወን የሚገባቸው ተግባራት ስደተኞችን መከፋፈልንና ተገን የማይሰጣቸውንም መመለስን በፍጥነት መሥራት እንዳለብን ተረድተናል ።»
የብሪታንያው ጠቅላይ ሚኒስትር ዴቪድ ኬምረን በበኩላቸው ብሪታንያ በአውሮፓ ህብረት ውስጥ እንድትቆይ ያወጡትን እቅድ ትናንት በእራት ሰዓት በተካሄደ ውይይት ላይ አቅርበዋል ።ኬምረን ብሪታንያ በአባልነት መቀጠል አለመቀጠሏ የሚታወቅበት ህዝበ ውሳኔ በ2017 ዓም ከመካሄዱ በፊት ከአንዱ የህብረቱ አባል ሃገራት ወደ ሌላው ለሚሰደዱ ሰዎች የሚሰጥ ድጎማን ማቆምን ጨምሮ ባቀረቧቸውን ሃሳቦች መሪዎቹ አብረዋቸው እንዲሰሩ ጠይቀዋል ። ሆኖም ኬምረን እንዳሉት ሂደቱ ቀላል አይሆንም ።
«ጥሩው ዜና ስምምነት ላይ የሚያደርስ ኃይል ያለዉ አካሄድ አለ ። ካካሄድነው ውይይት በኋላ በዚህ ላይ መተማመን አድሮብኛል። እውነታው ግን ሥራው ከባድ ነው ።በማህበራዊ ድጎማዎች መስክ ብቻ ሳይሆን ፣ለውይይት ያቀረብናቸው ጉዳዮች ሁሉ ከበዳ ሥራ ይጠይቃሉ ።ምክንያቱም ብዙ ጉዳዮችን ያካተቱና በ28 ቱም የአውሮፓ ህብረት አባል ሃገራት ትክክለኛ ለውጦችንና ውሳኔዎችን የሚፈልጉ ናቸው ።»

Belgien EU Gipfel Merkel
ምስል Getty Images/D. Mouhtaropoulos

ገበያዉ ንጉሤ

ሸዋዬ ለገሠ

አዜብ ታደሰ