1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአጥንት መሳሳት

ማክሰኞ፣ ጥር 20 2006

አጥንት ከሰዉነት ክፍል ጠንካራዉ አካል ነዉ። እንደ ጥንካሬዉ ግን በተለያዩ ምክንያቶች ለጉዳት በሚዳረግበት አጋጣሚ ወደቀድሞ ይዞታዉ ለመመለስ ቀላል አይሆንም። አጥንት ከአካል እድገትና ከእድሜ መጨመር ጋ እያደር እያደገና እየጠነረ ሄዶ በጉርምስና እድሜ ማብቂያ ላይ እድገቱን ያቆማል።

https://p.dw.com/p/1Aybm
ምስል Fotolia

አጥንት ጠንካራ የሰዉነት አካል መሆኑ ቢታወቅም በተለያዩ ምክንያቶች አቅም የሚያጣበትና ለስብራትም ሆነ ለመሰንጠቅ የሚጋለጥበት ሁኔታ አለ። የጥንካሬዉን ያህል ታዲያ እክል ሲገጥመዉ በቀላሉ ላይጠገንም ይችላል። የዓለም የጤና ድርጅት እንደሚለዉ ከወንዶች ይልቅ የሴቶች የአጥንት ጥንካሬ ከእድሜ አኳያ እየቀነሰ ይሄዳል። ጥንካሬዉ የቀነሰ አጥንት ደግሞ ለመሰበርም ሆነ ለመሰንጠቅ አደጋዎች እጅግ የተጋለጠ ነዉ። እንደድርጅቱ የሚያጋጥመዉ የአጥንት መሰንጠቅ አደጋ ከእድሜ አኳያ ይበረታል፤ ከ50 ዓመት በላይ ከሆኑ ሴቶች 40 በመቶዉ ለዚህ ችግር ይዳረጋሉ።

እግር ወይም እጅ የመሠበር አደጋ ሊያጋጥም ይችላል፤ በእርግጥ ይህ በተገቢዉ ህክምና ሊጠገንና ወደቦታዉ እንዲመለስ ሊደረግ ይችላል። እንዲህ ያለዉ ችግር የሚወሳሰበዉ ግን አንድም አጥንቱ ሲሳሳ አለያም አቅም አጥቶ ለመሰንጠቅ ሲዳረግ ነዉ። ይህ ችግር በአብዛኛዉ በእድሜ የገፉ ሰዎች ላይ የሚታይ ሲሆን በተለይ ሰዎቹ እንደልብ የማይንቀሳቀሱ ከሆነ ሌላ ተጨማሪ የጤና እክልም ሊያስከትል ይችላል። እንደሃኪሞች ግምትም ከ50 ዓመት በላይ ከሆናቸዉ ሴቶች ከሶስት አንዷ ወይም ከዚያ በላይ የወር አበባ ዑደት ከቆመ በኋላ በሚከሰት የሆርሞን ለዉጥ የአጥንት መሳሳት ወይም የመሰንጠቅ ችግር ይገጥማቸዋል። እንዲህ ዓይነቱን ችግር ለመከላከል ይላሉ እዚህ ጀርመን ባድ ኖየንሃር የሚገኘዉ የአጥንት ህክምና ኪሊኒክ ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ቶማስ ካዉሽ፤ ከተቀመጡበት ሲነሱ በጥንቃቄ መቆም ተገቢ ነዉ፤

Röntgenbild Knochenbruch
ምስል picture-alliance/dpa

«ብዙም የማይንቀሳቀሱ ከሆነ እና ተስተካክሎ የመቆም እርግጠኝነት ከሌለ በመዉደቅ የሚመጣዉ መዘዝ ከፍተኛ ነዉ። እንዲህ ባለ ሁኔታ ላለ ሰዉ መንቀሳቀስ እጅግ ወሳኝ ነዉ። አጥንቱ በእንቅስቃሴዉ ሊነቃቃ እንደሚችል መረዳት ያስፈልጋል፤ ይህም የተዳቀቀዉ አጥንት እንዲጠናከር የማድረግ አስተዋፅኦ አለዉ።»

የአጥንት መሳሳት ወይም አቅም ማጣት የሚያጋጥማቸዉ ሰዎች ለረዥም ጊዜ ምንም ዓይነት የጤና እክል እንዳለባቸዉ ሊያዉቁት አይችሉም። ለአስር ወይም አስራ አምስት ዓመታት ያለምንም እንከን ሊንቀሳቀሱበት ይችላሉ። የከፋ ችግር መኖሩን የሚረዱት ልክ እንደወ/ሮ ሬጊና ብሩወር ባልታሰበ ሁኔታ ስብራት ሲያጋጥማቸዉ ይሆናል።

«ከሥራ እረፍት በነበርኩበት ወቅት ነዉ፤ ምግብ ቤት ዉስጥ የወለሉ ንጣፍ አንሸራቶኝ ወደቅኩ። ታፋዬ ላይና ትከሻዬ ላይ ተሰበርኩ። ዶክተሮቹ የትከሻሽ ስብራት ቀጥተኛ በመሆኑ ተጋጥሞ የመዳን ተስፋ አለዉ አሉኝ። እናም አጥንቱን ስበዉ አያያዙት እንጂ የተፈረካከሰ እንጨት መስሎ ነበር።»

ከዚያም የ69ዓመቷ ወይዘሮ ባድ ኖየንሃር በሚገኘዉ የማገገሚያ ክሊኒክ ለሶስት ሳምንታት እንዲቆዩ ተደረገ። እዚያም በየሠዓቱ በተዘጋጀላቸዉ መርሃግብር መሠረት በየቀኑ የስነልቦና ምክር አገልግሎትን ጨምሮ የሰዉነት እንቅስቃሴ ሲያደርጉ ከረሙ። በቆይታቸዉም ታማሚዋ አንድ ሰዉ ለመዉደቅ አደጋ ሲጋለጥ እንዴት መዉደቅ እንደሚኖርበት ስልት እንዲያጠኑ ተደርጓል። መዉደቅ ድንገተኛ በመሆኑ አንድ ሰዉ አወዳደቅን እንዴት ሊያስተካክል ይችላል የሚል ጥያቄ ሊነሳ ይችላል፤ የስነልቡናዉ የምክር አገልግሎት ሚናዉ ይሄ ነዉ። አጥንት ጥንካሬ ከሌለዉ የሚገጥመዉ አደጋ የተለያዩ መዘዞችን ማስከተሉ ግድ ነዉ። ጥናቶች እንደሚያመለክቱትም በመዉደቅም ሆነ በተለያዩ አጋጣሚዎች ከሚደርሱ ስብራቶች በተለይ አንገት ላይ የሚያጋጥም ስብራት ለህልፈተ ህይወት ሊዳርግ ይችላል። ዶክተር ቶማስ ካዉሽ ምክንያቱን ያስረዳሉ፤

Tod durch Kekse Flash-Galerie
ምስል Fotolia/ArTo

«ይህ ከመንቀሳቀስ ጋ የተገናኘ ነዉ፤ በተወሰነ እድሜ አንድ ሰዉ ረዥም ሰዓታት አልጋ ላይ የሚተኛ ከሆነ እና የማይንቀሳቀስ ከሆነ በቀላሉ ለተለያዩና ተያያዥ በሽታዎች ይጋለጣል። ማለትም የደም መርጋት፤ የሳንባ መታፈን፤ የልብ ምትና የደም ዝዉዉር ችግር የመሳሰሉት ሁሉ ያጋጥማሉ። እናም እነዚህ ተባብረዉ ህመምተኛዉን ለህልፈት ይዳርጋሉ።»

የአጥንትን ጥንካሬ ማጣት በዘመኑ ህክምና ቀድሞ ሊደረሰብበት እንደሚችል ነዉ የሚታመነዉ። የዘርፉ ሃኪሞች በኤክስሬይ ወይም ራጅ በማንሳት የአጥንቱን ክብደትና ጥንካሬ መመዘን ይችላሉ። ዶክተር ካዉሽ የሚያገለግሉበት የባድ ኖየንሃር ክሊኒክ በየዓመቱ ወደስምንት መቶ የሚደርሱ ይህን መሰል ምዘናዎችን ያካሂዳል። ሃኪሞቹ በሚያደርጉት በዚህ ምርመራ በተመረጠዉ የሰዉነት አጥንት አካባቢ ምን ያህል የካልሲየም መጠን እንዳለ ማወቅ ይችላሉ። በተለይ በዳሌ አካባቢ በሚገኘዉ አጥንት ላይ ነዉ ይህ ምርመራ በብዛት የሚደረገዉ። ይህ የሆነበት ምክንያትም ከሌላዉ አካባቢ ይልቅ በዚህ ስፍራ የሚገኘዉ አጥንት በቀላሉ ሊሰበር ስለሚችል ነዉ። እናም በምርመራዉ በተባለዉ አካባቢ ዝቅተኛ የካልሲየም መጠን የሚኖር ከሆነ አጥንቱ ጥንካሬ የጎደዉ መሆኑ አያጠራጥርም፤ ያም ዉሎ አድሮ በቀላሉ ለጉዳት ይዳረጋል። አንዳንድ መድሃኒቶች አጥንት የመጉዳት ባህሪ አላቸዉ ይላሉ ዶክተር ቶማስ ካዉሽ፤

Künstliches Hüftgelenk aus Titan
ምስል picture-alliance / dpa

«ለምሳሌ ሄፓሪን ያለባቸዉ፤ ለሚጥል በሽታ የሚወሰዱ መድሃኒቶች፤ ለሆድ ህመም እና ለጨጓራ የሚወሰዱ አንዳንድ መድሃኒቶች፤ ለረዥም ጊዜ የሚወሰዱ ከሆነ በጊዜ ሂደት ይህን ችግር ሊያስከትሉ ይችላሉ። ይህ ማለት ግን ለምሳሌ በሳምንት ሁለቴ በመዉሰድ ማለት አይደለም። ነገር ግን አንድ ሰዉ እንዲህ ያሉ መድሃኒቶችን በተከታታይ ለሁለትና ከዚያ በላይ ዓመታት የሚወስድ ከሆነ ይህ የጎንዮሽ ችግር አይቀሬ ነዉ።»

ከዚህም ሌላ ኮርቲዞን የተሰኘዉም የአጥንትን ጥንካሬ እንደሚጎዳ ነዉ ያመለከቱት። ይህ በተለይ የሪህ ህመምተኞችን ይመለከታል፤ ኮርቲዞንን ለመዉሰድ ይገደዳሉናል። ለካንሰር ህክምና የሚደረገዉ ኬሞቴራፒም እንዲሁ ለዚህ ሊያጋልጥ እንደሚችል ይታመናል። ወ/ሮ ሬጊና ብራወር የዛሬ 11 ዓመት የሆድ ካንሰር አጋጥሟቸዉ እጢዉ በቀዶ ጥገና ወጥቶላቸዋል። ከቀዶ ጥገናዉ በኋላ ኬሞቴራፒዉ ቀጠለ። ይህም የተገመተዉን የአጥንት መዳከም አስከተለ። በማገገሚያዉ ክሊኒክ ዕለት በዕለት ከሚሠሩት የሰዉነት እንቅስቃሴ ጎን ለጎን የአመጋገባቸዉ ሁኔታም ከፍተኛ ክትትል ይደረግበታል፤ ከየዕለቱ ምግባቸዉ ዉስጥ በቂ ካልሲየም የሚያገኙባቸዉ የሚበረክቱ ሲሆን ቫይታሚን ዲም ይወስዳሉ። ዶክተር ካዉሽ ቫይታሚን ዲ ለአጥንት ስለሚሰጠዉ ጥቅም እንዲህ ይላሉ፤

«ቫይታሚን ዲ በአጥንት አወቃቀር እና በካልሲየም ክምችቱ ላይ ቀጥተኛ የሆነ ተፅዕኖ ያደርጋል፤ ያለ ቫይታሚን ዲ ይህ ነዉ የሚባል የአጥንት ገጽታ አይኖርም።»

እድሜን ተከትሎ የአጥንት መሳሳት ችግር በብዛት ሴቶችን ያጋጥማል ቢባልም ወንዶችም ለችግሩ የሚጋለጡበት ሁኔታ መኖሩ ግልፅ ነዉ። በነገራችን ላይ በዳሌ አጥንት ላይ የሚደርስ መሰንጠቅ ከባድና አብዛኛዉን ጊዜ ሃኪም ቤት ተኝቶ ለመታከም ግድ የሚል፤ ሲከፋም ለአካል ጉዳት የሚዳርግ እንደሆነ ነዉ የዓለም የጤና ድርጅት የሚያመለክተዉ። በጎርጎሪዮሳዊዉ 1990ዓ,ም 1,7 ሚሊዮን ሰዎች በዓለም ዙሪያ የዳሌ አጥንት መሰንጠቅ እንዳጋጠማቸዉ ተመዝግቧል። የዓለም የጤና ድርጅት እንደሚለዉም በመጪዉ 2050ዓ,ም ከህዝብ ብዛትና የአኗኗር ሁኔታ አኳያ ቁጥሩ ከፍ ብሎ 6 ሚሊዮን ሊደርስ እንደሚችል ይገመታል።

ሸዋዬ ለገሠ

ኂሩት መለሰ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ