1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአፍሪቃ ስደተኞች በኢጣልያዋ አፑልያ

ማክሰኞ፣ ነሐሴ 7 2005

ከማልታና ከግሪክ ቀጥሎ በርካታ አፍሪቃውያን ስደተኞች የሚጎርፉባት አውሮፓዊት ሃገር ኢጣልያ ናት።በአንዳንድ የኢጣልያ ግዛቶች መንግሥት ህገ ወጥ የሚላቸው አፍሪቃውያን ስደተኞች ደግሞ በኢጣልያ ጎስቋላ ህይወት ነው የሚገፉት።

https://p.dw.com/p/19Oti
ምስል picture-alliance/dpa/dpaweb

በሺህዎች የሚቆጠሩ መንግሥት ህገ ወጥ የሚላቸው አፍሪቃውያን ስደተኞች በየዓመቱ ኢጣልያ ይገባሉ ። እነዚህ ስደተኞች ሥራ የማግኘት ፣ የተሻለ ህይወት የመምራት ወደ ቤተሰቦቻቸውም ገንዘብ የመላክ ተስፋ ሰንቀው በአስቸጋሪው የባህር ላይ ጉዞ ከሞት አምልጠው በተለያዩ የሃገሪቱ የባህር ጠረፎች በኩል ኢጣልያ ቢደርሱም የሚያልሙትን ሁሉ የማግኘት ዕድላቸው የመነመነ ነው ። ጥገኝነት ያላገኙት ደግሞ በአሰዛን ሁኔታ የወንጀለኛ ቡድኖች ሰለባ ሆነው ይሰቃያሉ ። የዶቼቬለዎቹ አሱምፕታ ላቱስ ና ዩልያ ሃን ጥሩ ተስፋ ሰንቆ ወደ ኢጣልያ የሄደ አንድ በደቡብ ምሥራቅ ኢጣልያው የአፑልያ ግዛት የሚገኝ አፍሪቃዊ ስደተኛ ያለበትን ሁኔታ ተመልክተዋል ። ከካርቶንና ከፕላስቲክ ከተቀለሰው ሊወድቅ ከተቃረበው ደሳሳ ጎጆ ውጭ ዝንቦች ያንዣብባሉ ፤ ሽታው ከሩቅ የሚተነፍገው ሳምንታት ያስቆጠረው ቆሻሻ ተከሞሯል ። በስፍራው ይህን መሰል ብዙ ጎጆዎች ይገኛሉ ። ንጹህ የመጠጥ ውሐ ኤሌክትሪክም ሆነ የመፀዳጃ ቤት የለም ። ነዋሪዎቹ አፑልያ ኢጣልያ ውስጥ የሚገኘውን ይህን አካባቢ የጎስቋሎች መንደር ወይም ጌቶ ነው የሚሉት ።

Symbolbild afrikanische Flüchtlinge im Mittelmeer
ምስል picture-alliance/Milestone Media

በአንደኛው ጎጆ ውስጥ አንድ ፍራሽ ላይ 5 ሰዎች ተኝተዋል ። በጥቂት ሴንቲሜትሮች ርቀት የሚገኙ ሌሎች 10 ባዶ ፍራሾችም በዚሁ ጎጆ ውስጥ አሉ ። ከላይ የሚንጠለጠሉ ገመዶች እንደ ልብስ መስቀያ ያገለግላሉ ። ወለሉ ላይ ጫማዎች ተደርድረዋል ። በፕላስቲክ ሳህኖች ምግብ ተቀምጧል ። አትሞ

ጎጆዋ የኢብራ ምባኬ ፋልና በአመዛኙ ከምዕራብ አፍሪቃ የመጡ የሌሎች 20 ስደተኞች መኖሪያ ናት ። ጎጆዋ ጠባብና ብዙ ሰዎች የሚኖርባት በመሆኗ አየር የታፈገና መጥፎ ጠረንም ያለው ነው ። ኢብራ ድህነትን ሸሽቶ ህይወቱን ለሞት አጋልጦ በአደገኛው የባህር ላይ ጉዞ ከሴኔጋል ትልቅ ተስፋ ይዞ ወደ ደቡብ ኢጣልያዋ የባህር ዳርቻ የመጣው የዛሬ 12 ዓመት ነው ።

«እዚህ የመጣሁት የራሴን ህይወት ለማሻሻል የሚረዳኝ ጥሩ ሥራ ማግኘት እችላለሁ ፤ ሴኔጋል የሚገኙትንም ቤተሰቦቼን ለመርዳት የሚያስችለኝ ጥሩ ገንዘብ አገኛለሁ ብዬ ነበር ። »

እስካሁን ግን ኢብራ በኢጣልያ የሚመኘውን ህይወት አላገኘም ። ኑሮ በኢጣልያዋ የባህር ዳርቻ አፑልያ ከድጡ ወደ ማጡ ሆኖበታል ። የ32 ዓመቱ ኢብራ በአገሩ የኮራ አናፂ ነበር ። ኢጣልያ እንደሄደ በሙያው መሥራት ባይችልም መጀመሪያ ላይ ጣልያኖች መሥራት የማይፈልጉትን ሥራ ማግኘት ችሎ ነበር ። ጥሩ ክፍያ ባያገኝበትም ከእርሻ ቦታ አትክልትና ፍራፍሬ ይለቅም ነበር ። ያኔ ጣሊያኖች ንቀው የማይሰሩት ይህ ሥራ ዛሬ የሰማይ ያህል ርቋል ። አሁን እንደ ቀድሞው በቀላሉ የሚገኝ ሥራ አልሆነም ። በዚህ የተነሳም አሁን የሚሰራው አጥቶ ሥራ ፍለጋ ሲዋትት ነው የሚውለው ። ኢብራን ለዕለት ቀለቡ ብቻ ሳይሆን አገሩ ሴኔጋል ለሚገኙት ዘመዶቹም ነው የሚያስበው ። ሥራ በነበረው ጊዜ ከሚያገኘው ገንዘብ ቆጥቦ ይልክላቸው ነበር ። አሁን ግን ያን ማድረግ አልቻለም ።

Destination Europe – Kapitel-Nr. 4
ምስል LAIF

«ወደ አገር ቤት ገንዘብ መላክ ካቆምኩ 3 ወር ሆነኝ ። ሥራም ሆነ ገንዘብ እንደሌለኝ ልገልፅላቸው ብሞክርም የሚያምነኝ አላገኘሁም ። እነርሱን ዘንግቼ አውሮፓ የምንፈላሰስ ነው የሚመስላቸው »

ኢብራ ሥራ ከማጣቱ በፊት በሰዓት 3 ዩሮ ለሚከፍሉት ካፖላሪ ለሚባሉት ለኢጣልያና ለአፍሪቃ ማፍያዎች ይሰራ ነበር ። የስራ ውል ወይም ኮንትራት እንዲሰጠው ጠይቆ ስላልተሳካለት አቋርጦታል ። ኢብራ የኮንትራት ሥራ ይዞ ከሥራ ቢባረር እንኳን ከመግሥት ጥቂትም ቢሆን ገንዘብ ሊያገኝ እንደሚችል ያውቃል ። ይሁናና ለኢብራ ስራ የሚያመቻቹት እነዚህ ማፍያዎች ለመብቶቹ ደንታም የላቸውም ። ማፍያዎቹ ኢብራና መሰሎቹ ሊያገኙት ከሚገባው ገንዘብ 50 በመቶውን ወደራሳቸው ኪስ ያስገባሉ ። እነ ኢብራን በአነስተኛ ገንዘብ ቀጥረው የሚያሠሩት የአካባቢው ገበሬዎች ብዙ ያተርፉባቸዋል ። ኑሮ በኢጣልያ ያልተሳካለት ኢብራ አሁን ወደ ሃገሩ ወደ ሴኔጋል መመለስን እንደ ሽንፈት ነው የሚቆጥረው ። ወደ ሃገሩ ለመመለስ ቢወስን እንኳን ቲኬት መግዣ ገንዘብ የለውም ። ለክፉ ቀን ብሎ ያጠራቀመው ገንዘብም ቢሆን ተሟጧል ። አሁን ምናልባት ሥራ የሚሰጥ ባገኝ ብሎ በአትክልት እርሻዎች አካባቢ ይዘዋወራል ። ኑሮው ከቀድሞው አሁን ከብዶታል ። በአካባቢው እርዳታ የሚለግስ ደግሞ አንድ ድርጅት ብቻ ነው ።

Einwanderer in Spanien
ምስል AP

« እዚህ ሲመጣ የምናየው ብቸኛው ድርጅት የካቶሊካውያን የበጎ አድራጎት ድርጅት ካሪታስ ነው ። ባለፉት ሁለት ወራት ሶስት ጊዜ ያህል ብቻ ነው የመጣው ። ሩዝ ፓስታ እና ቲማቲም ያከፋፍለናል ።»

በኢጣልያዋ የአፑልያ ግዛት በ10 ሺህዎች የሚቆጠሩ አፍሪቃውያን ስደተኞች ይኖራሉ ። አብዛናዎቹም መንግሥት ህገ ወጥ የሚላቸው ስደተኞች ናቸው ። የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት እንዳስታወቀው በጎርጎሮሳውያኑ 2013 የመጀመሪያዎቹ 6 ወራት ከጥር እስከ እስካለፈው ሰኔ ወር ድረስ ፣ 8 ሺህ አፍሪቃውያን ስደተኞች ደቡብ ኢጣልያዋ ደሴት ላምፔዱዛ ገብተዋል ። የሚመጡትም በአውሮፓ ህብረት አባል ሃገራት ውስጥ ሥራ ፍለጋ ነው ። እናም ከቀናቸው አብዛኛዎቹ ኢጣልያ ላይቆዩም ይችላሉ ። ያልሆነላቸው ደግሞ ኮፖራሊ በተባለው የወንጀለኞች ቡድን ስር እዚያው ኢጣልያ ውስጥ በሚገኙት የአትክልት እርሻዎች መስራት ይሆናል ዕጣቸው ። የአካባቢው ነዋሪዎች አፍሪቃውያኑ ስለሚገፉት ጎስቋላ ህይወት ያውቃሉ ። አንዳንዶቹ በአካባቢው አሁን ለነርሱ የሚሆን ስራ አንደሌለ ሲናገሩ ፤ አንዳንዶቹ ደግሞ ስደተኞቹ አመፅ እንዳያስነሱ ስጋት አላቸው ።

« በርካታ አፍሪቃውያን እዚህ እየመጡ ሥራ እንዳለ ይጠይቃሉ ። ሆኖም እዚህ ሥራ የለም ። በአንድ ወቅት ከመካከላቸው አንዱን ቀጥሬው ነበር ። ይሁንና አሁን ለርሱ የሚሆን ሥራ የለኝም ። »

«ወደ ተጎሳቆለው መንደር አልሄድኩም ። ሆኖም በአስከፊ ሁኔታ ውስጥ እንደሚኖሩ ሰምቻለሁ ። ሁኔታውንም ካሉበት ችግር ለማምለጥ እንደ አመፅ ማስነሻ አድርገው ሊጠቀሙበትም ይችላሉ ። ይህም መንግሥት ምንም እንደማያደርግ ያሳያል ። »

አስተያየት ሰጭዎቹ ይህን ቢሉም በካፖላሪዎች ወይም በማፍያዎች ጉዳይ ውስጥ ገብተው መናገር ግን ይፈራሉ ። ኢብራ እንደሚለው መንግሥትም ቢሆን ስደተኞቹን ዞር ብሎ አያይም ።

Afrikanische Migranten Almeria Behausung
ምስል DW

« ባለሥልጣናቱ በምንም ዓይነት መንገድ አይረዱንም ። »

የአፑልዪ ከንቲባ ጅያንፍራንኮ ሳቪኖ በአፑሊያ የሚኖሩትን አፍሪቃውያን ስደተኞች ለመርዳት ምንም አለማድረጋቸውን ያምናሉ ። ምክንያት የሚያደርጉትም ሃገሪቱ አህን ያለባትን ችግር ነው ።

«የኤኮኖሚ ቀውስ ውስጥ ነው ያለነው ። ያም ማለት እኛም ጎስቋላው መንደር እንደሚኖሩት ሰዎች ሁሉ ሥራ የሚያሻቸው ብዙ ሰዎች አሉን ። ኢጣልያ ውስጥ ከመንግሥት ተቋማት አንስቶ እስከ አካባቢ ባለሥልጣናት ድረስ እጅግ ከፍተኛ የኤኮኖሚ ችግር አለ ። በዚያ ላይ ደግሞ የስደተኞች ጉዳይም ሌላው ተጨማሪ ችግር ነው ። »

በአሁኑ ጊዜ ከግሪክ ቀጥሎ አውሮፓውያንን የሚያስጨንቀው የኢጣልያ ችግር ሆኗል ። ሃገሪቱ ከገጠማት የኢኮኖሚ ቀውስ ሌላ በየጊዜው በስደተኞች መጥለቅለቋ አሳሳቢ ነው ። አርካንጄሎ ስደተኞችን በተቻላቸው መጠን የሚረዱ የካቶሊክ ቄስ ናቸው ።

አፍሪቃውያኑን በየጊዜው ይጎበኟቸዋል ። ጣሊያንኛ እንዲማሩ የቋንቋ ኮርሶችን በማዘጋጀት እንዲሁም በተቻለ ሁሉ ስደተኞቹን ለማፅናናት ይሞክራሉ ። በእርሳቸው አስተያየት መንግሥት ስደተኞችን ላለመርዳት ችግሩን ሰበብ አድርጎ ማቅረቡ ተቀባይነት የለውም

«የኢጣልያ ተቋማት የሆኑት የፖሊስ ና የኢሚግሬሽን ቢሮዎች ማከናወን የሚገባቸውን እየሰሩ አይደለም ። ከዚህ ችግር በስተጀርባ ያሉት እነርሱ ናቸው ። ሁኔታው እንዲቀጥል ይፈልጋሉ ብዮም አስባለሁ ። ያ ካልሆነ ግን ባለቸው ሥልጣንና በስራቸው ያለውን አማራጭ ሁሉ ተጠቅመው ችግሩን ለምን አያስወግዱም ? »

ይሁንና ቄስ አርካንጄሎ ከኢጣልያ ቢሮክራሲ ጋር የተያያዘውን ይህን ችግር የመፍታት አቅም እንደሌላቸው ነው የሚያስረዱት ። አሁን ለኢብራ በአውሮፓ የተሻለ ህይወት የመምራት ተስፋው ወደ ቅዠት ተለውጧል ። አሁን ያለው አማራጭ አዲሱ መኖሪያው በሆነው በጎስቋላው መንደር እየኖረ ሥራ ፍለጋውን መቀጠል ብቻ ነው ።

ሂሩት መለሰ

ተክሌ የኋላ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ