1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአፍሪቃ/ኤርትራ ስደተኞች አበሳ

ሰኞ፣ ጥቅምት 25 2006

ሮም የታተመ የኢጣሊያ ጋዜጣ እንደዘገበዉ የሶሪያ ስደተኞችን እንረዳለን የሚሉ ሐይላት ከዘጠና አምስት ስደተኞች ላይ መቶ ሺሕ ዩሮ የሚያወጣ ወርቅ፥ሌላ ጌጣ ጌጥና ገንዘብ ዘርፈዋል።ዶን ሙሴ ዘርዓይ እንዳሉት ደግሞ አዉሮጳ የሚገቡ ስደተኞችን እንረዳለን የሚሉ፥ በተለይ የሚያስተረጉሙ ኤርትራዉን የስደተኞቹን ሚስጥር ለኤርትራ መንግሥት አሳልፈዉ ይሰጣሉ

https://p.dw.com/p/1ABTX
Photo title Scrap Hundreds of Africans of different nationalities from Chad, Sudan, Niger, Mali, Eritrea, Somalia and walk to the infidels at 250 to 300 people a day Place and, Date : Kufra – Libya 9-3 -2012 Copy Right/Photographer: Esam Mohamed ezzobair zugeliefert von: Abderrahmane Ammar
የአፍሪቃ ስደተኞች-ሊቢያምስል DW

አፍሪቃዊዉ ስደተኛ በረሐ ላይ በዉሐ ጥም ይሞታል፥ በረሐዉን ሲያቋርጥ በአጋቶች ይሰቃያል፥ ይገደላልም።ባሕር ላይ ደግሞ በዉሐ ይበላል።ሐይማኖተኛዉ ለሟች፥ ተሰቃዮች ይፀልያል። ፖለቲከኛዉ-በተለይ ከላምፔዱዛዉ መዳራሻ እልቂት በኋላ እልቂት፥ሞት፥ስቃዩ እንዳይደገም ወይም እንዲቀንስ በየስብሰባ-መድረኩ ቃል-ይገባል።የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች አስከሬን፥ ጉዳተኛ ይቆጥራሉ፥ ሁነኛ መፍትሔ እንዲገኝ ይጮሐሉ።በዚሁ መሐል ሌላዉ አፍሪቃዊዉ ወጣት የዘመድ፥ ወዳጅ፥ ብጤዎቹን እልቂት እየሰማ፥ የሞት ኬላዎቹን አቋርጦ ለማለፍ መሰደድ መሞቱን እንደቀጠለ ነዉ። በቅርቡ ዘመን አብዛኛዉ ኤርትራዊ ነዉ።እንደገና ለምን እና እስከ መቼ? እንበል፥ ላፍታ አብራችሁን ቆዩ።


የላፔዱዛ ደሴት መዳራሻ ባሕር በአስከሬን፥ በስደተኞች አስከሬን መሞላቱ እንደተሰማ፥የአብያተ ክርስቲያናት ደወል አቃጨለ፥የመሳጂዶች አዛን ተንቆረቆረ።ቄስ፥ ሼክ፥ ምዕመኑ ለሟቾች ሊፀልይ፥ ሊሰግድ ታደመ።

«ላምፔዱዛ መዳረሻ ላይ በደረሰዉ የጀልባ አደጋ ያለቁትን በርካታ ሰዎች (ሳስታዉስ) ታላቅ ቅሬታዬን አለመግለፅ አልችልም።በዕምሮዬ የሚመጣዉ ቃል ሐፍረት ነዉ።አሳፋሪ ነዉ።

«ሕወታቸዉን ላጡት ወንዶች፥ ሴቶች፥ ሕፃናት እና ለወዳጅ ዘመዶቻቸዉ፥ ለሁሉም ስደተኞች አብረን እንፀልይ።»

ታላቅ ጥፋት።ዜጎቻቸዉን ማኖር፥ ስደተኞቹን ማዳን፥ መቀበል፥ መርዳት ላልፈለጉ፥ ላልቻሉ፥ ሐይላት ደግሞ በርዕሠ-ሊቀነ ጳጳሳት ፍራንሲስ ቋንቋ ታላቅ ሐፍረት።ወይም ጥልቅ ፀፀት።በተደጋጋሚ የተባለዉን ለመድገም ያሕል ባለፈዉ ጥቅምት ሰዎት (ዕለት ዘመኑ ሁሉ እንደ ጎርጎሮሳዉያኑ አቆጣጠር ነዉ) ባሕር ዉስጥ ሰምጠዉ ከሞቱት ሰወስት መቶ ሥልሳ ስደተኞች፥ አብዛኞቹ የኤርትራ ዜጎች ናቸዉ።

ትንሽቱ ሐገር ካላት ትንሽ ሕዝብ ባንድ ቀን፥ ባንድ ጀልባ አደጋ፥ አንድ ስፍራ መቶዎችን በጣሙን ወጣቶችን በባሕር ዉሐ ስትነጠቅ ለሐገሪቱ ትልቅ ኪሳራ ነዉ።ለሟቾች ወላጅ፥ ወዳጅ፥ ዘመድ፥ ወገኖች ደግሞ ሐዘኑ በርግጥ መሪር ነዉ።ሪሊዝ ኤርትራ የተሰኘዉ የሠብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅት መሪ ወይዘሮ ሠላም ኪዳነ እንዳሉት ደግሞ ሐዘን የሚለዉ ቃል ዉስጣዊ ስሜትን መግለፅ አይችልም።

ሙዚቀኛዉም አንጎራጎረ።«ባሕሪ ላምፔዱዛ» እያለ።

የላምፔዱዛዉ ባሕር አደጋ በሟቾች ቁጥር ከፍተኛ ቢሆንም የመጀመሪያዉ አይደለም።የሚሰደዱ፥ ሲሰደዱ የሚሞቱት ሰዎችም የኤርትራ ዜጎች ብቻ አይደሉም።የሶማሊያ፥ የኢትዮጵያ፥ የሱዳን፥ የኮንጎ፥ የናጄሪያ፥ የኒጀር፥ የሌሎች የበርካታ የአፍሪቃ ሐገራት ዜጎች፥ አረብ ሐገራት ለመግባት ቀይ ባሕርን፥ የአደን ባሕረ ሠላጤን፥አዉሮጳ ለመድረስ የሜድትራኒያን ባሕርን ለማቋረጥ ሲሞክሩ ባሕር ዉስጥ ሰምጠዉ ይሞታሉ።

ደቡብ አፍሪቃ ለመግባት ኬንያ፥ ታንዛኒያ፥ ማላዊ፥ ሞዛምቢክ፥ ዚምባቡዌ ወዘተን ለሟቋረጥ ሲሞክሩ አንድም በየታጨቁበት የብረት ሰንዱቅ ዉስጥ ታፍነዉ፥ አለያም ሐይቅ ዉስጥ ሰምጠዉ ይሞታሉ። የሲና በረሐ፥ የሊቢያ ድንበር፥ የሱዳን-ግብፅ፣ የግብፅ-እስራኤል ድንበር የስደተኞች አስከሬን ይሰጣበታል።አካል እየተተለተለ ይቸበቸብበታል።

በየስፍራዉ የዱርና የባሕር አዉሬ የሚበላቸዉን። በየደረሰበት የሚደበደብ፥ የሚሰቃይ፥ የሚደፈር፥ የሚዘረፍ፥ ታስሮ የሚበደል ስደተኛን’ ቁጥር ለቆጣሪ አታካች ነዉ።በቅርብ ጊዜ ብዙ ጋ፥ ብዙዉ አይነት የስደተኞች ሞት፥ ስቃይ ሲወሳ ኤርትራ-ኤርትራዉያን ይነሳሉ።ኤርትራዊዉ የፖለቲካ አቀንቃኝና የመብት ተሟጋች አቶ አብዱረሕማን ሰዒድ «በተደጋጋሚዉ አደጋ ኤርትራዉያን ወጣት ስደተኞች መሞት መሰቃየታቸዉን በሰማሁ ቁጥር ሁለት ነገር ይሰማኛል አሉ።»


ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንሲስ የላምፔዱዛዉን አይነት አደጋ እንዳይደገም በጋራ እንስራ ብለዉ ነበር።

«እንዲሕ አይነት አደጋዎች እንዳይደገሙ ሐይላችንን እናስተባብር።አደጋዉ እንዳይደገም፥ጥረታችንን እናስተባብር።»

መደገሙ ግን አልቀረም።ባለፈዉ ሳምንት የኒጀርን በረሐ-አቋርጠዉ ወደ አልጄሪያ ለመግባት የሞከሩ ዘጠና አፍሪቃዉያን ስደተኞች በዉሐ ጥም አልቀዋል።የኒጀርና የአካባቢዉ ሐገራት ስደተኞች በዉሐ ጥም ሲያልቁ ከሁለት ሺሕ አንድ ወዲሕ ያለፈዉ ሳምንቱ የመጀመሪያዉ ነዉ።የላምፔዱዛዉ የባሕር አደጋ አይነት አደጋ ግን ሲፈጥን የየዕለት ሲዘገይ የየሳምንት ሰቀቀን ከሆነ ዉሎ አድሯል።

ሐበሻ ኤጀንሲ የተባለዉ የአፍሪቃ ቀንድ የስደተኞች መርጃ ድርጅት መሪ ዶን (አባ) ሙሴ ዘርዓይ ባለፈዉ አርብ እንዳሉት ከሁለት ሺሕ አስር እስካሁን በተቆጠረዉ ሰወስት ዓመት ባልሞላ ጊዜ ዉስጥ ሜድትራንያን ባሕር ብቻ ሰምጠዉ የሞቱት ኤርትራዉያን ሁለት ሺሕ አምስት መቶ ይደርሳል።


በጥቅምት ሰወስቱ አደጋ ሰበብ የሐይማኖት መሪዎች ፀሎት፥ ስግደት፥ ምሕላ ምልጃ፥ ከቫቲካን እስከ መካሕ ሲንቆረቆር፥ አደጋዉ ሊደገም አይገባም የሚሉት የአዉሮጳ ፖለቲከኞች ቃልም ከብራስልስ፥ ከሽትራስ ቡርግ፥ ከሉክስምቡርግ፥ ከሮም ይጎርፍ ነበር።በፀሎት፥ ምልጃ፥ በፖለቲከኞቹ ቃል፥ ውይይት መሐል በአደጋዉ ያለቁት ሰዎች አስከሬን ፍላጋዉ ማዉጣት፥ቆጠራዉም እንደቀጠለ ነበር።

የልጅ፥ ዉላጅ፥ ዘመድ ወዳጃቸዉን ሞት አስቀድመዉ የሰሙት ለሟቾች ሰባት ለማዉጣት ሲዘጋጁ ከሞልታ ሌላ ዜና ተሰማ።አዲስ አይደለም።በአብዛኛዉ የአፍሪቃ ስደተኞችን ያሳፈረች አንዲት ጀልባ ሞልታ አጠገብ ሠጥማ ካሳፈረቻቸዉ ስደተኞች መካካል ሰላሳ ስምንቱ ሞቱ።ጥቅምት አስራ-አንድ ነበር።አሁንም የኤርትራዉን ስም አለ።ለኤርትራዉያን ሌላ መርዶ።

ያኔ ነዉ፥ የአዉሮጳ ሕብረት ምክር ቤት ፕሬዝዳንት ጀርመናዊዉ ፖለቲከኛ ማርቲን ሹልትስ ሰዎችን የሚያሰድደዉን መሠረታዊ ምክንያት ማዉቅ አለብን ያሉት።

«ከዚሁ ጋር ለስደተኝነት የሚዳርገዉን መሠረታዊ ፖለቲካዊ ምክንያት መመርመር አለብን።ስደተኞች ወደ አዉሮጳ በሕጋዊ መንገድ የሚገቡበትን ሥልት መቀየስም ይገባናል።አለበለዚያ ይሕን ችግር መቆጣጠር አንችልም።»

ሰዎች ለመሰደዳቸዉ ምክንያታቸዉ ብዙ ነዉ።ጦርነት፥ ጭቆና፥ ረሐብ፥ ምጣኔ ሐብታዊ ችግር፥ ማሕበረ-ሐይማኖታዊ ነፃነት ወዘተ-ብሎ መደርደር አይገድም።የተለመደ-እና ቀላልም ነዉ።ከችግሮቹ ሁሉ ሽልትስ እንዳሉት መሠረታዊ የሚባለዉን አንጥሮ ማዉጣት ለብዙዎች በርግጥ ከባድ ነዉ።ኤርትራዉ የፖለቲካ አቀንቃኝ እና የመብት ተሟጋች አቶ አብዱረሐማን ሠኢድ እንደሚሉት በተለይ ለኤርትራ ወጣቶች መሠደድ መሠረታዊ የሚባለዉ ችግር በሥልጣን ላይ ያለዉ መንግሥት ጨቋኝ መርሕ ነዉ።

ወይዘሮ ሠላምም በዚሕ ይስማማሉ።

የኤርትራ መንግሥት ባለሥልጣናትን ለማነጋገር አስመራ እና ሮም (ኤርትራ ኤምባሲ) በተከታታይ ሥልክ ደዉለን ነበር።ገሚሶቹ ሥልካቸዉን አያነሱም።ያነሱት ሌሎቹን ጠይቁ አሉን።ሌሎች የተባሉትን ስንጠይቅ መልሰን እንደዉልላችኋለን አሉን።ይሕን ዝግጅት እስካጠናቀርኩበት ጊዜ የደወለ የለም።

እና እስካሁን የአፍሪቃ ሕብረት ላምፔዱዛም፥ ሞልታ አጠገብም ባሕር ዉስጥ ሰጥመዉ ያለቁትን፥ ኒጀር በረሐም በዉሐ-ጥም የሞቱትን ጠቅለል አድርጎ ትናንት በሐዘን ዘክሯል።ርዕሠ-ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንሲስ የላምፔዱዛዉ አይነት ጥፋት እንዳይደገም ባሉት ሐሳብ ላይ የመከረ ስብሰባ በሳምንቱ ማብቂያ የሮማ ካቶሊካዊት ቤተ-ክርስቲያን አስተናግዳለች።

በዚሑ ሳምንት ማብቂያ፥ እዚያዉ ሮም የታተመ የኢጣሊያ ጋዜጣ እንደዘገበዉ የሶሪያ ስደተኞችን እንረዳለን የሚሉ ሐይላት ከባሕር አደጋ ካዳኗቸዉ ዘጠና አምስት ስደተኞች ላይ መቶ ሺሕ ዩሮ የሚያወጣ ወርቅ፥ሌላ ጌጣ ጌጥና ገንዘብ ዘርፈዋል።ዶን ሙሴ ዘርዓይ እንዳሉት ደግሞ ሞት፥ ዘረፋ፥ ዱላ፥ ስቃይን አልፈዉ አዉሮጳ የሚገቡ ስደተኞችን እንረዳለን የሚሉ፥ በተለይ የሚያስተረጉሙ ኤርትራዉን ስደተኞቹን ይሰልላሉ፥ ሚስጥራቸዉን ለኤርትራ መንግሥት አሳልፈዉ ይሰጣሉ።

ከሞት ዱላ፥ መደፈር ካመለጡ በሕዋላም መከራዉ ብዙ፥ ተደጋጋሚም ነዉ።መፍትሔዉም እንደ ችግሩ ምክንያት ሁሉ ዉስብስብ፥ እንደየተመልካቹም የተለያየ ነዉ።የወይዘሮ ሠላምን እናስቀድም።

የአቶ አብዱረሕማን እናስከትል።

በዚሑ እናብቃ።ሥለዝግጅታችን ያላችሁን አስተያየት በተለመደዉ አድራሽን ላኩልን።ማሕደረ-ዜና ቢቃኘዉ ጥሩ ነዉ ብላችሁ የምታስቡትን ወቅታዊ ሐገራዊ፥ አካባቢያዊ፥ ዓለም አቀፋዊ ጉዳዮችን ብትጠቁሙን ለማስተናገድ እንሞክራለን።ነጋሽ መሐመድ ነኝ ቸር ያሰማን።

Eritreas-Flüchtlinge in Nord-Äthiopien, 2013; Copyright: DW/Getachew Tedla Hailegeorgis
የኤርትራ ስደተኞች-ኢትዮጵያምስል DW/Getachew Tedla Hailegeorgis
epa03893732 A row of dead bodies are covered with sheets at the port of Lampedusa, Italy, 03 October 2013. According to Italian port authorities, at least 82 bodies have been recovered off the Italian coast after a ship carrying migrants sank near the southern island of Lampedusa. The ship, which was believed to be carrying hundreds of migrants from Somalia and Eritrea, suffered extensive damage as it approached the smaller island of Conigli. EPA/NINO RANDAZZO BEST QUALITY AVAILABLE. +++(c) dpa - Bildfunk+++
ምስል picture-alliance/dpa
A coastguard vessel manoeuvres after unloading body bags containing African migrants, who drowned trying to reach Italian shores, in the harbour of Lampedusa October 3, 2013. At least 94 people died and scores were missing after a boat carrying migrants from Africa sank off the Sicilian island of Lampedusa on Thursday, officials and rescuers said. The coastguard said it appeared that there were between 400 and 500 migrants on the boat when it sank, and 150 had been saved so far. REUTERS/Enza Billeci (ITALY - Tags: SOCIETY IMMIGRATION DISASTER POLITICS)
ስደተኞች-በጉዞምስል Reuters

ነጋሽ መሐመድ

ሸዋዬ ለገሠ












ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ