1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአፍቃኒስታን ሠላምና የኔቶ ጉባኤ

ዓርብ፣ ግንቦት 10 2004

የአፍቃኒስታኑ ሥልት ገቢራዊነት እንዳጠያየቀ ነዉ።የዓለምን ምርጥ መሳሪያ የታጠቀዉ-ምርጥ ጦር አስራ-አንድ አመት ያልሆነለትን ዉጊያ ገና የሚሰለጥነዉ፥የአፍቃኒስታን ጦር ብቻዉን ይሳከለታል-ማለት ለብዙዎች ግራ-አጋቢ ነዉ የሆነዉ።

https://p.dw.com/p/14x9M
epa03147619 President Obama's image is reflected on the fuselage of Air Force One as he waves when boarding en route to fundraising events in Chicago, at Andrews Air Force Base in Maryland, USA, 16 March 2012. EPA/JIM LO SCALZO
የጉባኤዉ አስተናጋጅምስል picture-alliance/dpa

17 05 12

የሠሜን አትላንቲክ ጦር ቃል ኪዳን ድርጅት (ኔቶ) አባል ሐገራት መሪዎች በመጪዉ ሳምንት ቺካጎ-ዩናይትድ ስቴትስ ዉስጥ የሚያደርጉት ጉባኤ አብይ ትኩረት የአፍቃኒስታን ሠላምና ፀጥታ ነዉ።እንደ ጎሮግሮሳዉያኑ አቆጣጠር ከ2001 ጀምሮ አፍቃኒስታንና ፓኪስታን ዉስጥ ከአል-ቃኢዳና- ከታሊባን ደፈጣ ተዋጊዎች ጋር የተዋጋዉ የኔቶ ጦር እስከ 2014 ድረስ ለቅቆ ይወጣል።የቺካጎ ጉባኤተኞች ጦራቸዉ ከአፍቃኒስታን ከወጣ በሕዋላ ጦሩ ሲወጋቸዉ የነበሩት ሐይላት ተጠናክረዉ አፍቃኒስታንን ዳግም ተቆጣጥረዉ ምዕራቡን ዓለም እንዳይፈታተኑ የሚከላከሉበትን ሥልት ይቀይሳሉ ተብሎ ይጠበቃል።ነጋሽ መሐመድ ዝር ዝር ዘገባ አለዉ።



ኒዮርክና ዋሽንግተን በተሸበሩ ማግሥት የዘመተዉ የምዕራባዉያኑ የጦር ተሻራኪ  ድርጅት ጦር በአብዛኛዉ የአል-ቃኢዳና የታሊባን አሸባሪ፥ አክራሪ፥ ፅንፈኛ፥ እና ሌላም ከሚባሉ ደፈጣ ተዋጊዎች ጋር አፍቃኒስታንና ፓኪስታን ጠረፍ እስካሁን ያደረገዉ ዉጊያ ድል-ሽንፈት እንደተመልካቹ እይታ የሚለያይ-አንዳዴም የሚቃረን ነዉ።


አሜሪካ መራሹ ጦር አስራ-አንድ አመት ያደረገዉ ዉጊያ ዉጤት በተቃርኖ ጎራ ያቆማቸዉ ወገኖች በአንድ ነገር ግን አንድ ናቸዉ።አፍቃኒስታን ዛሬም ሠላም የለም-በሚለዉ።ሐያሉ ጦር  በርካታ ጓዶቹን የሰዋባት፥ ሐያላኑ መንግሥታት ቢሊዮነ-ቢሊዮናት ዶላር የከሰከሱባት፥ ሩቅ ምሥራቃዊቱ ሐገር ጠንካራዉ ጦር ድንኳኑን በሚነቅል፥ ጓዙን በሚጠቀልላበት ወቅት አሁንም  በርግጥ እንደተመሰቃቀለች ነዉ።

በአፍቃኒስታን የቀድሞዉ የአዉሮጳ ሕብረት ምክትል አማካሪ ባርባራ ስታፕለት አፍቃኒስታንን «ከጦርነት አረንቋ የተዘፈቀች» ይሏታል፥ የኔቶ ጦር እንዲወጣ መወሰኑን ደግሞ «ሽሽት»።የጦር ድርጅቱ አባል ሐገራት መሪዎች ግን አፍቃኒስታንን ብቻዋን አንተዋትም ይላሉ። የድርጅቱ  ዋና ፀሐፊ አድርስ ራስሙሥን  ፎግሕ ከሁለት ሺሕ አስራ-አራት በሕዋላም ኔቶ እዚያዉ ነዉ-ባይ ናቸዉ።
               
«ፀጥታ የማስከበሩን ዋነኛ ሐላፊነት ቀስ በቀስ ለአፍቃኖች እንሰጣለን።ይሕ ሒደት በሁለት ሺሕ አስራ-አራት ማብቂያ ይጠናቀቃል።ከዚያ በሕዋላ አፍቃኖች ሙሉ ሐላፊነቱን ይወስዳሉ።ይሁንና ከሁለት ሺሕ አስራ-አራት በሕዋላም እዚያዉ እንቆያለን።ግን በአዲስ ተልዕኮ።»

አዲሱ ተልዕኮ ፎግሕ እንደሚሉት ለአፍቃኒስታን ጦር ድጋፍ መስጠትና ማሰልጠን ነዉ።ቀደም ሲል ሰወስት መቶ ሐምሳ ሺሕ የአፍቃኒስታን ፀጥታ አስከባሪዎችን ለማሰልጠን ታቅዶ ነበር።አሁን ግን የዩናይትድ ስቴትስ ባለሥልጣናት እንደሚሉት ያንን ሁሉ ሠራዊት ማሰልጠን አይቻልም።ምክንያት ገንዘብ።ከእንግዲሕ ይሰለጥናል የተባለዉ ሁለት መቶ ሐምሳ ሺሕ ሠራዊት ነዉ።

የዚሕም ወጪ ቢሆን ምጣኔ ሐብታቸዉ ለከሰረዉ ምዕራባዉያን የሚቻል አይደለም።የኔቶ ዋና ፀሐፊ መፍትሔ አለ ነዉ-የሚሉት።                     

              
«እርግጥ ነዉ የመከላከያ በጀት በቀነሰበት ባሁኑ ወቅት ይሕን ማድረግ ከባድ ፈተና ነዉ። መቀጠል የምንችለዉ ያለንን ሐብት አብቃቅተን በመጠቀም ነዉ።አንዱ ብልሐት ደግሞ ሕብረ-ብሔራዊ ትብብርን ማጠናከር ነዉ።»

የኦቦማ መስተዳድርም «ሕብረ-ብሔራዊ ትብብር» የምትለዋን ሐሳብ አልዘነጋትም።በአመት ወደ ሰባት ቢሊዮን ዶላር የሚደርሰዉን የኔቶን ወጪ እንዲጋሩ ከጦር ተሻራኪዉ ድርጅት ጋር ምንም ግንኙነት የሌላቸዉ የጃፓንን የመሰሳሰሉ ሐገራት መሪዎች ሳይቀሩ ለቺካጎዉ ጉባኤ ላይ ተጋብዘዋል።

እንዲያዉም በቺካጎዉ ጉባኤ ከኔቶ አባል ሐገራት መሪዎች ይልቅ-የኔቶ አባል ያልሆኑት ተሳታፊዎች ቁጥር ይበልጣል።የኔቶ አባላት ሃያ-ስምንት ናቸዉ።ጉባኤተኞች ግን ሥልሳ።ዉሳኔዉ ግን ያዉ የኔቶ ነዉ-የሚባለዉ።
            
«በቺካጎዉ (ጉባኤ) የመከላከያ ማዕቀፍ እናፀድቃለን።«ቀልጣፋ» ያልነዉን የመከላከያ ፅንሰ-ሐሳብ እናፀድቃለን።ፀንሠ ሐሳቡ ያለንን ሐብትን በማብቃቃት፥ ሐብትን፥ ወታደራዊ መሳሪያና አቅምን ማዋጣትና መጋራትን ያጠቃልላል።በዚሕ ሁኔታ የምጣኔ ሐብት ችግር ቢኖርም አስፈላጊዉን ወታደራዊ አቅማችን መጠበቅ እንችላለን።»

የአፍቃኒስታኑ ሥልት ገቢራዊነት ግን እንደ እስካሁኑ የዉጊያ ዉጤት ሁሉ እንዳጠያየቀ ነዉ።የዓለምን ምርጥ መሳሪያ የታጠቀዉ-ምርጥ ጦር አስራ-አንድ አመት ያልሆነለትን ዉጊያ ገና የሚሰለጥነዉ፥የአፍቃኒስታን ጦር ብቻዉን ይሳከለታል-ማለት ለብዙዎች ግራ-አጋቢ ነዉ የሆነዉ።

Afghan President Hamid Karzai gestures while giving his opening address to dignitaries attending the peace jirga, in Kabul, Afghanistan, Wednesday, June 2, 2010. Security forces battled insurgents including at least one suicide bomber outside the national peace conference just as Karzai opened the three-day meeting Wednesday in the Afghan capital. (AP Photo/Musadeq Sadeq)
ካርዛይምስል AP
US soldiers inspect the site of suicide attack in Kandahar, Afghanistan, Saturday, Dec. 18, 2010. A suicide bomber attacked an armored car carrying a district chief in the southern Afghan city of Kandahar, killing himself and one civilian bystander, Afghan authorities said. (AP Photo/Allauddin Khan)
ኔቶ ወታደሮች በጥቃት መሐልምስል AP

ነጋሽ መሐመድ

አርያም ተክሌ










 

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ