1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኡሁሩ ኬንያታ በ«አይ ሲ ሲ» መቅረብ

ረቡዕ፣ መስከረም 28 2007

የኬንያ ፕሬዚደንት ኡሁሩ ኬንያታ በዛሬው ዕለት ዘ ሄግ በሚገኘው ዓለም አቀፉ ወንጀል ተመልካች ፍርድ ቤት፣ «አይ ሲ ሲ» ቀረቡ። «አይ ሲ ሲ» ከሰባት ዓመት በፊት በኬንያ ከተካሄደው ፕሬዚደንታዊ ምርጫ በኋላ በሀገሪቱ የተካሄደውን የጎሳ ግጭት አቀነባብረዋል በሚል በጠረጠራቸው ኬንያታ ላይ ክስ መመሥረቱ የሚታወስ ነው።

https://p.dw.com/p/1DSCb
Uhuru Kenyatta Kenia Präsident
ምስል Reuters/Peter Dejong

አንድ በሥልጣን ላይ ያለ መሪ ሄግ ፍርድ ቤት ሲቀርብ ኬንያታ የመጀመሪያው ሲሆኑ፣ ይህ አነጋጋሪ ጉዳይ ብዙ ማከራከሩ አልቀረም። የኬንያው ፕሬዚዳንት ኡሑሩ ኬንያታ ጠበቃ በሰብአዊነት ላይ ወንጀል መፈጸም የሚለው ክስ እንዲሠረዝላቸው ፍርድ ቤቱን ጠይቀዋል። ኬንያ ውስጥ ከምርጫ ማግሥት ታኅሳስ 2007 እስከ ጥር 2008 ም፤ በተለይ በሁለት ብሔሮች መካከል የጎሣ አምባጓሮ ተፈጥሮ ብዙ ሰዎች እንዲገደሉ የጠነሰሱት ዑሑሩ ኬንያታ ናቸው በሚል ጥርጣሬ ነው በሀገሪቱ የመጀመሪያው ፕሬዚዳንት ጆሞ ኬንያታ ልጅ ላይ ክሱ የተመሠረተው። በያኔው ሁከት 1,200 ሰዎች መገደላቸውና 600,000 ሰዎች ከቀየአቸው መፈናቀላቸው ታውቋል። 52 ዓመቱ ጎልማሳ ዑሑሩ ኬንያታ፣ ሥልጣናቸውን ለምክትላቸው ዊልያም ሩቶ አስረክበው ደን ሐኽ ከገቡ በኋላ፣ ዓለም አቀፉ ፍርድ ቤት ደረጃ ላይ ለተሰበሰቡ ደጋፊዎቻቸው፤

«ዛሬ እነርሱ በፈለጉት መሠረት እዚህ ድረስ መጥተንላቸዋል። አሁንም ቢሆን ታዲያ ምንም ነገር የለም » ሲሉ ተደምጠዋል። ኬንያታ ይህን ያሉት በወንጀል ለመከሰስ ጭብጥ ማስረጃ እንዳልተገኘ ለመጠቆም ነው ተብሏል።

የዚያው ዘመን የኃይል ርምጃ ሰለባዎች ጠበቃ የሆኑት ፌርጋል ጌይነር ይህን ብለዋል።

«ተከሳሽ በእውነት ስማቸውን ከመጎደፍ ለማዳን ቢፈልጉ ኖሮ በተቻላቸው መጠን ያኔ ከምርጫ በኋላ ሁከት በተቀሰቀሰበት ወቅት፤ በእርሳቸውና በረዳቶቻቸው መካከል የተደረጉ የእጅ ስልክ ንግግሮችን በተቻለ ፍጥነት ለማስረጃነት ማቅረብ በቻሉ ነበር። ስማቸው ከጉድፍ እንዲጸዳ፣ እጅግ ፈጣኑ ርምጃ ይህ ነበር የሚበጀው፤ አሁንም ቢሆን ዘግይቷል አንልም።»

ሂልከ ፊሸር/ይልማ ኃይለሚካኤል

አርያም ተክሌ

ሸዋዬ ለገሠ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ