1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኢትዮጵያ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ

ሰኞ፣ መስከረም 30 2009

አዋጁ ከሚከለክላቸው መካከል መንግሥት ግጭቶችን ሊያስነሱ ይችላሉ የሚላቸውን ፅሁፎች ማዘጋጀት እና ማሰራጨት ይገኝበታል ። የአገር ሠላም እና ደህንነትን አደጋ ላይ ይጥላሉ የሚላቸውን የመገናኛ ዘዴዎች መንግሥት መዝጋት እንደሚችልም ተጠቅሷል ።

https://p.dw.com/p/2R5kv
Infografik Karte Proteste und Ausschreitungen in Äthiopien 2016

Rxn on State of emergency in Ethiopia - MP3-Stereo


የኢትዮጵያ መንግሥት ትናንት በሀገሪቱ የደነገገው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ሃገሪቱን ለገባችበት ችግር  መፍትሄ ሊያመጣ እንደማይችል ተነገረ ። የህግ ምሁራን እና ተቃዋሚዎች ስለ አዋጁ ለዶቼቬለ በሰጡት አስተያየት ኢትዮጵያ በአሁኑ ሰዓት ፣ አስቸኳይ አዋጅ ሳይሆን ፖለቲካዊ መፍትሄ ነው የሚያስፈልጋት ብለዋል ። ዝርዝሩን ኂሩት መለሰ አዘጋጅታዋለች ።
የኢትዮጵያ መንግሥት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን መደንገግ ያስፈለገው የአገሪቱን ህልውና ለማስጠበቅ የህዝብን ሰላም እና ጸጥታ እንዲሁም ደህንነት ለማረጋገጥ መሆኑን አስታውቋል ። የመንግሥት እና ለመንግሥት ቅርበት ያላቸው መገናኛ ዘዴዎች አዋጁ የወጣው «በሀገሪቱ የሚካሄደው ሁከት በመሣሪያ የሚታገዝ በመሆኑ ምክንያት እንደሆነ  የኢትዮጵያ ፌደራል ጠቅላይ አቃቤ ህግን ጠቅሰው ዘግበዋል ። ዶቼቬለ ስለ አስቸኳይ አዋጁ ፋይዳ እና አንድምታው ካነጋገራቸው አንዱ እዚህ ጀርመን የተማሩት የህግ ፣በተለይም የአስተዳደር ህግ ባለሞያ እና የፖለቲካ ሳይንስ ምሁር ዶክተር ለማይፍራሸዋ ናቸው ። ዶክተር ለማ የኢትዮጵያን ህገመንግሥት አንቀፅ 93ን  መሠረት አድርጎ የወጣው ይህ አዋጅ በሌላውም የዓለም ክፍል እንደሚሰራበት  ገልጸው የሚያሰጋው እና የሚያጠያይቀው አተገባበር መሆኑን አስረድተዋል ።መንግሥት ሃላፊዎች በሰጡት ማብራሪያ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ከሚከለክላቸው  መካከል መንግሥት ግጭቶችን ሊያስነሱ ይችላሉ የሚላቸውን ፅሁፎች ማዘጋጀት እና ማሰራጨት ይገኝበታል ።  በአዋጁ የአገር ሠላም እና ደህንነትን አደጋ ላይ ይጥላሉ የሚላቸውን የመገናኛ ዘዴዎች መንግሥት መዝጋት እንደሚችልም ተጠቅሷል ።የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት መድረክ በአጭሩ መድረክ እንዲሁም የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ ገብሩ ገብረ ማርያም አዋጅን የነበረውን እጅግ የተገደበ ነጻነት ጭርሱኑ የሚያዳፍን ነው ብለዋል ።የአዋጁ አስፈጻሚዎች በሁከትና ብጥብጥ የተጠረጠሩ እና የተካፈሉ ያለ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ በቁጥጥር ስር ማዋል እንደሚችሉ ተገልጿል። በቁጥጥር ስር የሚውሉ ዜጎች ተምረው እንደሚለቀቁም ተዘግቧል  ። ዶክተር ለማ ይህ በህገ መንግስቱ ከሰፈሩት መሠረታዊ መብቶች ጋር የሚጻረር ነው ሲሉ ተችተዋል
ዶክተር ለማም ሆኑ አቶ ገብሩ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ የሃገሪቱን ችግር ሊፈታ አይችልም ነው የሚሉት ። እንደ አቶ ገብሩ መፍትሄ ሊያመጣ የሚችለው ሁሉን አሳታፊ ውይይት ብቻ ነው ።
ዶክተር ለማም ለኢትዮጵያ አሁን ያስፈልጋል ያሏቸውን ፖለቲካዊ መፍትሄዎች ዘርዝረዋል ።ትናንት የተደነገገው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የሰዓት እላፊ ገደብ አልጣለም ።

ኂሩት መለሰ

ነጋሽ መሀመድ