1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኢትዮጵያ ፖለቲካዊ ቀዉስና መፍትሔዉ

ነጋሽ መሐመድ Negash Mohammed
እሑድ፣ ጥቅምት 6 2009

ባለፉት ተከታታይ ሳምንታት ከደቡብ ዲላ እስከ ሰሜን አርማ ጮኾ የሚደርሱን መረጃዎች እንደሚጠቁሙት ኢትዮጵያዉያን በየዕለቱ በየሥፍራዉ እየተገደሉ፤ አካላቸዉ እየጎደለ፤ እየተደበደቡ እየታሰሩ ነዉ።የመንግሥት እና የባለሐብት መኪኖች፤ ፋብሪካዎች፤ የእርሻ ማሳዎች፤ ሌላዉ ቀርቶ ቤተ-እምነቶች እየጋዩ ነዉ።

https://p.dw.com/p/2RG2w
Äthiopien Trauer für gestorbenen Demonstranten
ምስል picture-alliance/AP Photo/K. Prinsloo

የኢትዮጵያ ፖለቲካዊ

 

አምና ሕዳር ለጀመረዉ ሕዝባዊ ጥያቄና ሰላማዊ ተቃዉሞ የኢትዮጵያ መንግሥት አስቸካይ እና ተገቢዉን መልስ እንዲሰጥ የተለያዩ ወገኖች በተደጋጋሚ አሳስበዋል።መክረዋልም።እስካሁን የተሰጠዉ መልስ ግን ሰብአዊ፤ ዲሞክራሲያዊ መብቱ፤ ማንነቱ፤ ሰዉ የመሆን ክብሩ እንዲጠበቅ በመጠየቅ አደባባይ የወጣዉን ሕዝብ አንዳንድ እያሉ ማሳነስ፤ ጥያቄያዉን ከአሸባሪ ወይም ከአጎራባች ሐገራት ጋር ማያያዝ እና ማዉገዝ ፤አልፎ ተርፎም የሐይል እርምጃ ነዉ።

ባለፉት ተከታታይ ሳምንታት ከደቡብ ዲላ እስከ ሰሜን አርማ ጮኾ የሚደርሱን መረጃዎች እንደሚጠቁሙት ኢትዮጵያዉያን በየዕለቱ በየሥፍራዉ እየተገደሉ፤ አካላቸዉ እየጎደለ፤ እየተደበደቡ እየታሰሩ ነዉ።የመንግሥት እና የባለሐብት መኪኖች፤ ፋብሪካዎች፤ የእርሻ ማሳዎች፤ ሌላዉ ቀርቶ ቤተ-እምነቶች እየጋዩ ነዉ።

ታዛቢዎች እንደተከታተሉት የኢትዮጵያ መንግስት ተቃዉሞዉን ለማቆም እስካሁን ከወሰዳቸዉ እርምጃዎች በተጨማሪ በነፃነት የሚዘግቡ መገናኛ ዘዴዎችን ማፈን ወይም ጃም ማድረግ፤ የኢተርኔትና የስልክ አገልግሎቶችን መዝጋትን እንደ ጥሩ መፍትሔ ቀጥሎበታል።ባለፈዉ ሳምንት ማብቂያ ደግሞ ለስድስት ወራት የሚፀና የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ደንግጓሉ። በዚሕ መሐል የተሐድሶ ለዉጥ እንደሚያደርግ አስታዉቋልም። ለዉጡ ወይም ዕቅዱ ግን በዝርዝር አልተገለጠም።

በቅርቡ ኢትዮጵያን የጎበኙት የጀርመንዋ መራሂተ መንግሥት አንጌላ ሜርክልን ጨምሮ የአዉሮጳ ሕብረት፤ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ፤ ዩናይትድ ስቴትስን የመሳሰሉ የኢትዮጵያ ወዳጅ የሚባሉ መንግሥታት፤ ማሕበራትና ባለሥልጣናት የኢትዮጵያ መንግስት ለሕዝቡ ጥያቄ ተገቢዉን መልስ እንዲሰጥ፤ የደረሰዉ ጥፋት በገለልተኛ ወገን እንዲጣራ አሁንም እያሳሰቡ ነዉ።የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ወትሮም ያልፀናዉን የመናገር፤ የመሰብሰብና የመደራጀት ነፃነትን ጨርሶ እንዳያዳፍነዉ ያሳስባሉ። እስካሁን ግን ተቀባይነት ያገኙ አይመስልም።ፖለቲዊ ቀዉሱም እንደቀጠለ ነዉ።የዛሬ ዉይይታችን የኢትዮጵያን  ፖለቲካዊ ቀዉስና  መፍትሔዉን ለመቃኘት ይሞክራል።

ነጋሽ መሐመድ

ልደት አበበ