የኢትዮ-ኬንያ ኤሌክትሪክ፥ የዓለም ባንክና ሠብአዊ መብት
ሐሙስ፣ ሐምሌ 5 2004
የዓለም ባንክ የኢትዮጵያና የኬንያን የኤሌክቲክ ፕሮጄክት በገንዘብ እንዳይደግፍ ዓለም አቀፉ የመብት ተሟጋች ድርጅት Human Rights Watch ጠየቀ።የዓለም ባንክ ከኢትዮጵያዉ የግልገል ጊቤ የሐይል ማመንጫ ግድብ ወደ ኬንያ የኤሌክትሪክ ሐይል ለሚተላለፍበትን መስመር መዘርጊያ 1.3 ቢሊዮን ዶላር ያሕል ለመርዳት አቅዷል።የመብት ተሟጋቹ ድርጅት እንደሚለዉ ግድቡና መሥመሩ በአካባቢዉ የሚኖረዉን ሕዝብና የተፈጥሮ ሐብትን የሚጎዳ ነዉ።በዚሕም ምክንያት ባንኩ ለፕሮጅክቱ ማስፈፀሚያ ገንዘብ ማበደር የለበትም።ነጋሽ መሐመድ አጭር ዘገባ አለዉ።
ደቡባዊ ኢትዮጵያ የሚገነባዉ የግልገል ግቤ ቁጥር ሰወስት የኤሌክትሪክ ሐይል ማመንጫ ግድብ ሑዩማን ራይትስ ዋች እና ሌሎች የመብት ተሟጋች ተቋማት እንደሚሉት በኦሞ ወንዝና በወንዙ ተፋሰስ አካባቢ የሚኖረዉን ሕዝብ ያፈናቅላል፥ አኗኗር አሠራር ባሕሉን ያዉካል፥ የተፈጥሮ ሐብትንም ይጎዳል።
የዓለም ባንክም የሕዝብን ፍላጎት፥ ኑሮና ጤና፥ የተፈጥሮ ሐብትን ደሕንነት ለአደጋ ያጋልጣሉ የሚባሉ መርሐ-ግብሮችን አይረዳም።ግዙፉ አበዳሪ ድርጅት ለግልገል ጊቤ ቁጥር ሰወስት የግድብ ገንባታ ገንዘብ ላለመስጠት ያቅማማዉም ከመብት ተሟጋቾቹ ጩኸት እኩል ግድቡ የራሱንም መርሕ ይቃረናል በሚል ሰበብ ነበር።
ከግድቡ ከሚነጨዉ ሐይል ወደ ኬንያ ለሚተላለፍዉ ሐይል አንድ ሺሕ ኪሎ ሜትር የሚረዝም መሥመር ለመዘርጋት ግን ባንኩ ገንዘብ ለማበደር አቅዷል።ይሕ ነዉ የሒዩማን ራይትስ ዋች ተቋዉሞ።በድርጅቱ የአፍሪቃ ጉዳይ አጥኚ ቤን ሮዉሌንስ የባንኩን ዕቅድ እሳት ካየዉ ምንለየዉ አይነት ይላሉ።
«የዓለም ባንክ ራሱ የግልገል ግጌ ሰወስት ግድብ የነዋሪዎችን መብትን የሚጋፋና የተፈጥሮ ሐብትን የሚጎዳ መሆኑ አሳስቦት ነበር።ለዚሕም ነበር ለግድቡ ለራሱ ከገንዘብ መስጠት የታቀበዉ።አሁን ግን ከዚያዉ ግድብ ወደ ኬንያ፥ ኋላ ደግሞ ወደ ደቡብ ሱዳን ሐይል የሚተላለፍበትን መስመር መዝርጊያ ገንዘብ ለመስጠት እያሰበ ነዉ።እኛ እንደምናስበዉ በግድቡ ላይ የተወሰደዉ እርምጃ ለሐይል መስመሩም መስራት አለበት።ምክያንቱም ማስተላለፊያዉ የግድቡ አካል ነዉና።»
ከሰማኒያ-እስከ ዘጠና ከመቶ የሚሆነዉ የኢትዮጵያና የኬንያ ሕዝብ ኤሌክትሪክ የለዉም።ኤሌክትሪክ የሚፈልገዉ የደቡብ ሱዳን ሕዝብ ቁጥር ደጎሞ ከሁለቱ ሐገራትም ይበልጣል።የደሐዉን ሐዝብ ኑሮ ለማሻሻል፥ የድሆቹ ሐገራትን ምጣኔ ሐብት ለማሳደግ የኤሌክትሪክ ሐይል ወሳኝ ነዉ።ድሆቹ ሐገራት ወሳኙን ሐይል ለማግኘት ያላቸዉ ርካሽ አማራጭ ደግሞ ዉሐ ነዉ።ዉሐዉ ተገድቦ።
ዉሐ እንዳይገደብ መቃወም፥ የሕዝብ ኑሮ አይሻሻል፥ የድሐ-ሐገራት አቅም አይደግ ማለት-አይደለም-ጠየቅዃቸዉ፥ ሮዉሌንስን-መለስሙም። አይደለም እያሉ።
«አይደለም በጭራሽ አይደለም።ማለቴ ኬንያ ኤሌክትሪክ ትፈልጋለች።ኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ትፈልጋለች።ኤሌክትሪክ አይኖራቸዉ የሚባልበት ምክንያት የለም።ኤሌክትሪኩ ከነፁሕ ምንጭ፥ በተገቢዉ መንገድ ከተገነባ፥ በቅጡ ተመክሮበት ከተሠራ ግድብ ማግኘት ይቻላል። ሰዎችን ሳያፈናቅሉ፥ በተፈጥሮ ሐብት ላይ ጉዳት ሳያደርሱ ግድብ መሥራት ይቻላል።ሰዎች የሚፈናቀሉም ከሆነ እነሱን በማማካርና ተገቢዉን ካሳ በመክፈል መገደብ ይቻላል።»
የኢትዮጵያ መንግሥት በተደጋጋሚ እንደሚለዉ ግድቡ ከማንም በላይ ለአካባቢዉ ሕዝብ የሚጠቅም፥ በሕዝቡ ፍቃድና ፍላጎት ነዉ የሚነገነባዉ።የሁዩማን ራትስ ዋቹ አጥኚ ግን ይሕን አይቀበሉትም።እንዲያ ቢሆን ኖሮማ-አሉ አጥኚዉ አበዳሪዎች ለግንባታዉ ገንዘብ ባልነፈጉ ነበር።
«የአፍሪቃ ልማት ባንክ፥የአዉሮጳ ኢንቨስትመንት ባንክ፥ የአለም ባንክ እነዚሕ በሙሉ ርቀዋል። ምክንያቱም ይሕ ፕሮጀክት ከተገቢዉ አሠራር ዉጪ የቀጠለ ነዉ-ብለዉ ሥለሚያምኑ።»
ግድቡ ግን እየተገነባ ነዉ።በዕቅዱ መሠረት ከሁለት ዓመት በሕዋላ አገልግሎት ይሰጣል ተብሎ ይጠበቃል።የዓለም ባንክ የገዢዎች ቦርድ ለመስመር መዘርጊያ የሚያስፈልገዉን ከ1.3 ቢሊዮን ዶላር በላይ ብድር መስጠት አለመስጡቱን ማምሻቸዉን ይወስናል ተብሎ ይጠብቃል።
ነጋሸ መሐመድ
ሸዋዬ ለገሠ