1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኢንተርኔት አገልግሎት መታሰቢያ

ዓርብ፣ የካቲት 2 2004

የኢንተርኔት ተጠቃሚዎች ፤ ኮምፒዩተራቸውን ከፍተው ከአንድ ድረ ገጽ ወደሌላው ያላንዳች ሳንክ መሸጋገር ፤ መቃኘት፣ ሐሳብ መለዋወጥ ፣ ማንበብ ፣መጻፍም ሆነ ሙዚቃ ወይም ሌላ ማድመጥ የሚችሉበት ፣ አስተማማኝ መላ የማግኘቱ

https://p.dw.com/p/13zeN

ሁኔታ ፤ ቀደም ባለው ጊዜ ፤ በይበልጥም በአሁኑ ዘመን ፤ በመረጃ ሥነ ቴክኒክ ረገድ፣ ትልቅ ግምት ሆኗል የሚሰጠው። ትናንት ማክሰኞ ፤ ጥር 29 ቀን 2004 ዓ ም፤ ኢንተርኔት፤ ከእኩይ ጥቃት ነጻ ሆኖ አገልግሎት መስጠት የሚችልበት መታሰቢያ ዕለት በመባል፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ ትኩረት ተሰጥቶት አልፎአል። Safer Internet Day! በአጭሩ ኢንተርኔትን እንዴት አስተማማኝ ማድረግ ይቻላል? በሚለው ጥያቄ ዙሪያ አጥጋቢ መልስ ለማግኘት መታሰቢያው ቀን ልዩ ትኩረት የተደረገበት ዕለት ነበረ ማለት ይቻል ይሆናል። ኮምፑዩተርን ማበላሸት፤ በ Online ወንጀል መሥራት፤ ከሩቅ ፣ አሰናካይ ፣ ጎጂ ነገር መላክ፣ ከአነአካቴው ሊገታ ያልቻለ ችግር ሆኖ ቢቀጥልም፤ ለዚህ መከላከያውንም ሆነ አብነቱን በመሻት የሚጥሩና በተሣካ ሁኔታ ተግባራቸውን የሚያከናውኑ ኩባንያዎች በዓለም ዙሪያ ይገኛሉ። ከአነዚህም አንዱ ፤ መቀመጫውን ጀርመን ውስጥ በድንጋይ ከሰል ማዕድንና በብረታ-ብረት ፋብሪካዎች በታወቀው ሩር አውራጃ ውስጥ፤ ቦኹም በተሰኘችው ከተማ የሚገኘው G Data SecurityLabs ነው።

G Data ትናንት ታስቦ የዋለውን፣ ለኢንተርኔት አጠቃቀም ይበልጥ አስተማማኝ ሁኔታን መፍጠር የሚለውን መፈክር አስፈላጊነት ሲጠቅስ፤ በ«ኦንላይን» ላይ የሚፈጸም ጥቃት ባላፉት ዓመታት ፣ ይበልጥ እየጨመረ መምጣቱን ጭምር በሰፊው ሳያወሳ አላለፈም። የ «ጂ ዳታ» የደህነነት ጉዳይ ኀላፊ፣ Ralf Benzmüller በዝርዝር እንዳስረዱት፤ የኦንላይን ወንጀለኞች፤ የሌላውን ሰው የ«ኢሜይል» ምሥጢር ቃልን ፤ ገንዘብ ከባንክ የማውጫ ካርድ መለያ ቁጥርን፣ ፈልፍለው ለማወቅ በመጣር፤ በቀጥታ ተቀማጭ ገንዘብን መዝረፍ ነው ዓላማቸው!ፈተናው ፣ አዛውንት፣ ጎልማሶችና ልጆችን የሚመለከት ቢሆንም ይበልጥ የዚህ እኩይ ተግባር ሰለባዎች የሚሆኑት ልጆች ናቸው። ልጆች በ «ኦንላይን» ፣ ከአኩዮቻቸው ጋር፤ ቪዲዮዎች ማየት፣ ጨዋታዎችን ማዘውተር አዳዲስ ወዳጆችን በኢንተርኔት በኩል መተዋወቅም ይሻሉ። ወጣቶችም ሆኑ ልጆች፤ ጎጂ ሁኔታ ያጋጥማል ብለው አያስቡም። ስለሆነም ወላጆች፤ ኮምፒዩተር ሊበላሽ ይችላል ብለው ሳይሆን ፣ በቅድሚያ ፣ ልጆቻችንን የሚጎዳ ሁኔታ ሊፈጠር ይችላል ብለው ነው ፣ ጥንቃቄ ማድረግ የሚጠበቅባቸው። «ሶፍትዌሩ» ፣ ወቅታዊ ደረጃውን የጠበቀ ስለመሆኑ መመርመርና የሚያውክ እኩይ ተግባርን መክላት የሚችል መከላከያ ማስገባትም ተፈላጊ ይሆናል።

ወጣቶች እጅግ ፈታኝና ላቅ ያለ ኮምፒዩተራቸውን የሚያሰናክል አደጋ የሚገጥማቸው፤ በኢንተርኔት ተኀዋሲ የተበከለ ድረ ገጽ ሲጎበኙ ነው። መሰናክል የሚፈጥሩት ወገኖች፤ ማለትም በኮምፒዩተር ተግባር መሪ አካል (Processor) ላይ ብልሽት እንዲያጋጥም የሚጠቀሙት፤ የ ኢ ሜይል መልእክት በመላክ፣ ወይም የሚያጓጓ ፊልም፣ እጅግ ተወዳጅ ተዋንያንና ተወንያት ያሉበት ነው በማለት ፣በሚያቀርቡት የውሸት የቪዲዮ ፊልም አማካኝነት ነው። የኅብረት ጨዋታ አለ የሚል ማስታወቂያ አቅርበው በማጓጓት ወይም በማሰኘትና ወይም በ«ፌስቡክ» ፣ በውድድር ያሸነፈ የገንዘብ ሽልማት ያገኛል በሚል አማላይ ዘዴም ነው ጎጂ ተግባር የሚፈጽሙት።

የጀርመን ፌደራል ሪፓብሊክ የቤተሰብ ጉዳይ ሚንስትር ወ/ሮ Kristina Schröder

በ«ዲጂታል» የመገናኛ ዘዴዎች አጠቃቀም ላይ ይበልጥ ኀላፊነት ሊሰማን ይገባል፤ በማለት ከማስገንዘባቸውም፤ ልጆች፤ በኢንተርኔት መጠቀም ያለውን ሰፊ ዕድልና ሊያጋጥም ስለሚችለው አደጋም ሆነ መሰናክል ጭምር ተገቢው ትምህርት ሊሰጣቸው እንደሚገባ አስረድተዋል። በዚህ ረገድ፤ የፖለቲካ ሰዎች፤ ትምህርት ቤቶች፤ ወላጆችና እያንዳንዱ ግለሰብ ፤ ሁሉም፤ ኀላፊነት ያለባቸው መሆኑንም ሚንስትርዋ ገልጸዋል።

Safer Internet Day አውሮፓ ውስጥ፤ በአውሮፓው ኅብረት ተነሳሽነት፤ Klicksafe በተሰኘው መርኀ-ግብር ሥር፤ በጀርመን የራይንላድፋልትዝና ኖርድ ራይን ቬስትፋለን ፈደራል ክፍላተ ሀገር የተቀናጀ ዘመቻ ያካሄዱ መሆናቸው ነው የተገለጠው። የዘንድሮው መሪ መፈክርም፤ «በኢንተርኔት መረብ አጠቃቀም ላይ ኀላፊነት ይኑር! » የሚል ነው። ባለፈው ዓመት፤ «የጾታን ልዩነት አጉልተው በሚያሳዩ ዓለማት ማደግ፤» ሃቻምና ፤ «የግል የምሥጢር ሰነዶች ጥበቃ፣» ከዚያም፤ እ ጎ አ በ 2009 ዓ ም፤ («ሳይበርሞቢንግ»)የተባለው ነበር።

Expedition Heimat DW Internet
ምስል expedition-heimat.dw.de

የሸማቾችም ሆነ የዕቃ ገዥዎች መብት ተመላካቹ ሚንስቴር ፣ ሚንስትር ወ/ሮ ኢልዘ አይግነር ፣ ዘመናዊዎቹ የአጅ ስልኮች፤ እንደ ኮምፒዩተርና እንደማስታወሻ ንዑስ ኮምፒዩተር መሣሪያ ከጥቃት ለመከላከል አስተማማኝ የመከላከያ አቅምም ሆነ ዘዴ የላቸውም በማለት በርሊን ላይ ታስቦ በዋለው ኢንተርኔትን ይበልጥ አስተማማኝ ለማድረግ ትኩረት በተሰጠበት መታሰቢያ ዕለት ላይ ጥንቃቄ እንደሚያሻ ምክራቸውን ለግሠዋል።

ሚንስትር ወ/ሮ ኢልሰ አይግነር ከሞላ ጎደል 60% ዕድሜአቸው ከ 30 በታች የሆነ ሰዎች በየዕለቱ በኢንተርኔት እንደሚገለገሉ ጠቅሰው፤ በተለይ ዘመናዊዎቹ የአጅ ስልኮች፤ ከኢንተርኔት የመረጃ ቀማኞች አደጋ ያን ያህል ነጻ አለመሆናቸው የሚያሳስብ ነው ብለዋል። በጀርመን ሀገር ሩቡ የአገሪቱ ተወላጆች በዘመናዊ የእጅ ስልክ አማካኝነት፤ በኢንተርኔት እንደሚገለገሉ ይታወቃል። ሚንስትር አይግነር ያቀረቡትን ማሳሳቢያ መንስዔ በማድረግ ሲያብራሩ----

1,« ለዚህ አባባላሌ ምክንያት የሆነኝ፤ ዘመናዊው የእጅ ስልክ፤ ከአንድ የኢንተርኔት ገጽ ጋር ያላንዳች መረጃ ግንኙነት ቢፈጥር፤ መሣሪያውን ለይቶ በማወቅ፤ የተቆለለ የስልክ ወጪ ተሸካሚ እንዲሆን ሊያደርገው ይችላል። »

ይህም ሊሆን በመቻሉ፤ ዘመናዊዎቹ የእጅ ስልኮች (እስማርትፎንስ)፤ በመላ አውሮፓ፣ ለጥቃት ላለመጋለጥ አስተማማኙን መከላከያ ሊያጠናክሩ ይገባቸዋል በማለት ነው ኢልዘ አይግነር ያሳሰቡት።

2,«ወደፊት ፤ የአውሮፓው የግል ምስጢራዊ ሰነድ የሚጠበቅበት መብት፤ ፊታቸውን ወደ አውሮፓው ገበያ ላዞሩ፣ በአውሮፓው ኅብረት መቀመጫ ለሌላቸውና በሦስተኛ አገር መረጃ ለሚቀምሩም ኩባንያዎች ሁሉ የሚያገልግል መሆን ይኖርበታል። በኢንተርኔት የማኅበራዊ ትሥሥር ላላቸውና በአውሮፓው ኅብረት ውስጥ ሆነው ለሚጠቀሙም ደንቡ ይሠራል። »

ተክሌ የኋላ

ነጋሽ መሐመድ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ