1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኢንቴርኔት መቆራረጥ በአማራ ክልል

Merga Yonas Bulaማክሰኞ፣ ነሐሴ 10 2008

ሰሞኑን በአማራ እና በኦሮሚያ ክልል የተለያዩ ቦታዎች የተቃዉሞ እንቅስቃሴ መኖሩ ይታወቃል። መንግሥት የተቃዉሞዉ ምንጭ ከዉጭ በማኅበራዊ መገናኝ ብዙሃን የሚሰራጭ ፀረ ሰላም ቅስቀሳ ነዉ ባይ ነዉ።

https://p.dw.com/p/1JjEC
Karte Äthiopien Amhara, Tigray, Oromia Deutsch

[No title]

የተቃዉሞ እንቅስቃሴዉን ለመቆጣጠርም በርካታ የፀጥታ ኃይል በማሰማራት ሰልፎች እንዳይካሄዱ እያደረገ መሆኑን እማኞች ይገልጻሉ። ከዚህም አልፎ ለተቃዉሞ የቅስቀሳ መልክቶች እንዳያስራጩ በአንዳንድ ቦታዎች የኢንተርኔት አገልግሎት መስተጓጎሉ፤ ማህበራዊ መገናኛ መድረኮቹም መዘጋታቸዉ ይሰማል። ለዚህም ማህበራዊ መድረኩን የሚጠቀሙ አንዳንድ ሰዎች ሃሰት እየፈበረኩ ህዝቡ የፀጥታዉ አካል ላይ እንዲነሳሳ፣ ወንድም ወንድሙን እንዲጎዳ ስለሚጥሩ መንግሥት ርምጃዉን ለመዉሰድ መገደዱን የመንግሥት የኮሙኒኬሼን ጉዳዮች ሚኒስትር አቶ ጌታቸዉ ርዳ ሰሞኑን ከአልጃዚራ ጋር ባደረጉት ቃለ መጠይቅ ጠቅሰዋል።


ስማቸዉ እንዳይጠቀስ የጠየቁት የባህር ዳር ነዋሪ ከተማዋ ከእሁድ ዕለት ጀምሮ እስከ ዛሬ ከፍተኛ ዉጥረት ላይ እንደምትገኝ ይጠቅሳሉ። ሌላዉ ስማቸዉን ያልገለጹት የጎንደር ነዋሪ ደግሞ የዛሬዉን ርግጠኛ ባይሆኑም በከተማዋ ሙሉ በሙሉ እሁድና ሰኞ ዕለት መጓጓዣ እንዳልነበረ፣ የመንግስት መስርያ ቤቶችና ሱቆችም እንደተዘጉ ይናገራሉ።


በሰሜን ወሎ ወልድያ አካባቢ ተቃዉሞ ለማካሄድ ቢታቀድም በፀጥታ ኃይል ታፍኗል ይላሉ እኝህ የጎንደር ነዋሪ። የወሎ ዩንቨርሲቲ ተማሪ መሆናቸዉን የገለፁልን ደግሞ ኮምቦልቻና አካባቢዋ በፌዴራል ፖሊስና መከላክያ ሠራዊት ተሞልታለች ካሉ በኋላ የተማሪዉ እንቅስቃሴ መገደደቡን አመልክተዋል።


የኢንቴርኔት አገልግሎቱ መቆራረጡን በተመለከተ ከክልሉም ሆነ ከፌዴራል መንግሥት ማብራርያ እንዲሰጡን ለመጠየቅ ያደረግነዉ ሙከራ ለዛሬ ሊሳካልን አልቻልም።


በዶቼ ቬለ የፌስ ቡክ ገጽ ስለኢንተርኔት አገልግሎቱ ይዞታ እና ስለጎንደር ዉሎ የተከታዮቻችንን አስተያየት ጠይቀን ነበር። «ከቤት ባይወጡ ምንቸገረው መንግሥት፣ ያው አረፈ፤ ሲርባቸው ይወጣሉ.» የሚሉ ሲኖሩ ሌሎች ደግሞ «የሚገርመው ለማኝ እንኳን ለምኖ እንዳይበላ? መንግሥት ምን ቸገረው ጥቁር ወንበር ቁጭ ብሎ፤ እኛን ጥቁር የሀዘን ልብስ ያለብሰናል።» «አዲስ አበባ ላይ ይህ የተቃውሞ ስልት ተግባራዊ ሲሆን ያኔ ወያኔ ኧረ ባካችሁ ሰልፍ ውጡ የሚል ይመስለኛል።» እና ሌሎችንም ተያያዥ አስተያየታቸዉን ጽፈዉልናል።

መርጋ ዮናስ

ሸዋዬ ለገሰ