1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ሰኞ፣ ኅዳር 26 2009

የኢትዮጵያ መንግስት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅን ካወጀ ከሁለት ወር በፊት ጀምሮ በእጅ ስልክ፣ የቀጥታ የኢንቴርኔት አገልግሎት ወይም «mobile data» ን ዘግቶ እንደነበረ ዘገባዎች ያመለክታሉ። መንግስት ይህን አገልግሎት ባለፈዉ ዓርብ መልሶ ከፍቶታል።

https://p.dw.com/p/2Tlp4
Äthiopien Addis Abeba Universität Kommunikation Internetsperre
ምስል DW/J. Jeffrey

Internet Service in Ethiopia - MP3-Stereo

እንደ ዘገባዎቹ ከሆነ ግን፣ አሁንም የማህበራዊ መገናኛ ዘዴዎች ፣ ማለትም የዋትስአፕ፣ የቫይበር፣ የፌስቦክና ኢንስታግራም አገልግሎት እንደተዘጉ ይገኛሉ። መንግስት ለዚሁ ርምጃው በኦሮምያና በአማራ ክልል ተከስቶ የነበረዉን ተቃዉሞ ለማርገብ መሆኑን እንደ ምክንያት መጥቀሱ ይታወሳል።

በተለያዩ የኦሮምያና የአማራ ክልል ነዋሪዎች በአካባቢዎች አሁን ያለዉ የኢንቴርኔት አገልግሎት ምን እንደሚመስል ጠይቀናቸዋል። ብዙዎቹ ስማቸው እና ያሉበት ቦታ እንዲጠቀስ ባይፈልጉም አስተያየት ለመስጠት ዝግጁ ነበሩ። አንዱ የአማራ ክልል ነዋሪ፣ ባለፈው ዓርብ  ኢንቴርኔት መከፈቱን ቢያረጋግጡም፣ እሳቸው Psiphon በተሰኘዉ የፀረ/ሳንሱር አፕሊልኬሼን እንደሚጠቀሙ ተናግረዋል።

ሌላው የምዕራብ ሃራርጌ የቆቦ ነዋሪ መምህር  የኢንቴርኔት ላለፉት ሁለት ወራት መዘጋት በሙያቸዉ ላይ ተፅዕኖ እንደፈጠረባቸው ገልጸዋል። ኢንቴርኔት መልሶ ተከፈተ ቢባልም፣ አገልግሎቱ በትክክክል ይሰራል ማለት አይደለም ይላሉ። «እኔ በፌስቡክ ነዉ የምጠቀመዉ። ባለፉት ጊዚያት ሙሉ በሙሉ አልነበረም።  ትላንት ነበረ። እኔ ያለሁበት ቦታ ግን አሁን  አይሰራም።»

የአባት ስማቸዉን ለመጥቀስ ያልፈለጉ አቶ አብዲ የተባሉ የአዲስ አበባ ነዋሪ ደግሞ የኢንቴርኔት አገልግሎት በከፊል ተከፈተ ቢባልም ፣ «አዝጋሚ» መሆኑን ነው ያስታወቁት።

የአዳማው ነዋሪ ደግሞ የኢንቴርኔት አገልግሎትን ላለፉት ወራቶች በPsiphon ሲጠቀሙ እንደነበሩ ተናግረው በወቅቱ ከድሮው የተለወጠ ነገር እንዳላዩ አስረድተዋል።  መልሶ ተከፈተ የተባለበት አካባቢ በግልፅ አይታወቅም ይላሉ።


በዚሁ ጉዳይ ላይ ከኢትዮጵያ የመንግስት ኮሙኒኬሼን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት  መረጃ ለማግኘት ብንሞክርም አልተሳካልንም።  መቀመጫዉን በዋሽንግቶን ዲ ሲ  ያደረገዉ የአሜሪካውያኑ የብሩክሊን ተቋም ከጥቂት ጊዜ በፊት ያወጣው ጥናት እንዳሳየው፣ የኢትዮጵያ  መንግሥት ኢንቴርኔት በመዝጋቱ ወደ ዘጠኝ ሚሊዮን ዶላር አጥቶዋል።

መርጋ ዮናስ

አረያም ተክሌ