1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኤርትራ የነፃነት በዓል፥የአፍሪቃ ቀንድና አመፅ

ሰኞ፣ መጋቢት 5 2003

የመብት ተሟጋቾች እንደሚሉት ደግሞ ጋዜጠኞች፥ ተቃዋሚ ፖለቲከኞች ታስረዋል።ብዙዎች ደግሞ የደረሱበት አይታወቅም።አቶ ዓሊ ከወቀሳ ዉንጀላዉ አንዱንም አይቀበሉትም።

https://p.dw.com/p/R95x
አስመራምስል picture-alliance/ dpa


አቶ ዓሊ አብዶ የኤርትራ ማስታወቂያ ሚኒስትር።የኤርትራ ሃኛ አመት የነፃነት በዓል፥ የኤርትራዉያን የነፃነት፥የአፍሪቃ ቀንድ ትርምስና የሕዝባዊ አመፅ ሥጋት ርዕሳችን፥ አቶ ዓሊ አብዶን አነጋግረናል ላፍታ አብራችሁን ቆዩ።

የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚንስትር አቶ መለስ ዜናዉ ቅዳሜ።የዚያኑ ዕልት የኤርትራ ማስታወቂያ ሚንስትር አቶ ዓሊ አብዶ የኢትዮጵያ መንግሥት ኤርትራን የሚወነጅለዉ በኢትዮጵያዉያን ላይ የሚያደርሰዉን በደል ለመሸፈን ነዉ ብለዉ ነበር።የዛሬ ሃያ አመት ግድም እንደ ጥብቅ ወዳጅ አዲስ አበባና አስመራ ላይ ሁለት መንግሥት ያቆሙት ሁለቱ ሐይላት ከጫካ ዉጊያ እስከ አብያተ-መንግሥታት ያደረሰቸዉን «ፍቅር ወዳጅነት» በደም አፋሳሽ ጠብ ለመለወጥ ሰባት አመት አልታገሱም።ዛሬም በየሰበብ አስባቡ እንደተጋጩ፥እንደተወዛገቡ፥ እንደተወነጃጀሉ ነዉ።

የሁለቱ ጠብ፥ ብዙ የፖለቲካ ተንታኞች እንደሚሉት የሶማሊያዉን ግጭት ዉጊያም አንሮታል።ሱዳን-ደቡብ ይባል፥ አቤይ ወይም ዳርፉር ሰላም የለም።ጂቡቲና ኤርትራ ጠብ-ግጭታቸዉን አስወገድን ቢሉም ሠላም ናቸዉ ማለት አይቻልም።የርስ በርስ ፥የድንበር፥ የፖለቲካ ግጭት፥ ዉዝግብ ያልተለየዉ የአፍሪቃ ቀንድ የሰሜን አፍሪቃን የዘመናት ፖለቲካዊ ሥርዓት የገለባበጠዉ ሕዝባዊ አብዮት አይቀርለትም ይባላል።እንዲያዉም ጅቢቲን በስሱም ቢሆን ደባብሷታል።አቶ ዓሊ አብዶ እንደሚሉት ግን የአፍሪቃ ቀንድ መሠረታዊ ችግር ሌላ ነዉ።

በዩናይትድ ስቴትሱ ፕሬዝዳት በጆርጅ ደብሊዉ ቡሽ መስተዳድር ዘመን ኤርትራ በአለም አቀፉ የፀረ-ሽብር ዘመቻ ተባባሪ፥ኢራቅን ለመዉረር ደግሞ «የፍቃደኞች ጥምረት» (Coalision of the Willing) አባል ነበረች።የያኔዉ መከላከያ ሚንስትር ዶናልድ ራምስ ፌልድ እንደ ቅርብ ወዳጅ የጎበኟት ተባባሪ ሐገር ነበረች።በ2008 (ዘመኑ በሙሉ እንደ ጎርጎሮሳዉያኑ አቆጣጠር ነዉ) ግን የቡሽ መስተዳድር የአፍሪቃ ጉዳይ ረዳት ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር የነበሩት ጄንዳይ ፍሬዘር ኤርትራን አሸባሪዎችን ትደግፋለች፥ታስታጥቃለችም በማለት ወነጀሏት።

Textilfabrik in Asmara Eritrea
የጨርቃጨርቅ ፋብሪካምስል africa-photo

ወይዘሮ ሒላሪ ክሊንተን እንደ ጎሮጎሮሳዉያኑ አቆጣጠር1990 ዎቹ አጋማሽ እንደ ቀዳማዊት እመቤት አስመራን ሲጎበኙ ያቺ ወጣት ሐገር የሠላም ተምሳሌት፥ የልማት፥ ዲሞክራሲም ተስፋ አይነት ተብላ ነበር በዋሽንግተኞች አይን።ክሊንተን በ2009 እንደ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር የአፍሪቃ ቀንድን ሁኔታ ሲቃኙ ግን ኤርትራ የሶማሊያዉን አሽባሪ ቡድን አ-ሸባብን ታስታጥቃለች በማለት ወነጀሏት።

ከዩናይትድ ስቴትስ እና ከኢትዮጵያ ሌላ ሌሎች መንግሥታትና ድርጅቶችም ኤርትራ ከኦጋዴን-እስከ ሶማሊያ፥ ከጅቡቲ እስከ ዳርፉር የአፍሪቃ ቀንድን በሚያብጠዉ ግጭት ዉዝግብ እጇን አስገብታለች በማለት ይወነጅሏታል።የተባበሩት መንግሥታት ድርጅትም ማዕቀብ ጥሎባታል።የኤርትራዉ ማስታወቂያ ሚንስትር ግን ዉንጀላ-ወቀሳዉን አይቀበሉትም።

ያም ሆኖ የአስመራ መንግሥት ከመገለል የሚድንበትን መንገድ ማፈላለጉ አልቀረም።ኤርትራ ለአመታት አቋርጠዉ ወደ ነበረዉ የአፍሪቃ ሕብረት አባልነት ባለፈዉ ጥር ተመልሳ አምባሳደሯን ወደ ሕብረቱ መቀመጫ አዲስ አበባ ልካለች።ማስታወቂያ ሚንስትር ዓሊ አብዶ እንደሚሉት ግን የአፍሪቃ ሕብረት የሚይዛቸዉን ብዙ አቋሞች መንግሥታቸዉ አይቀበለዉም።


የኤርትራ መንግሥት ባለፉት ሃያ አመታት በብዙ ኪሎ ሜትር የሚቆጠሩ መንገዶችን፥ በረጅሙ ጦርነት የወደሙ ተቋማትን መልሶ መገንባቱን ሐገሪቱን ያዩ ይመሰክራሉ።የዚያኑ ያክል ግን ኤርትራ ምርጫ የሚባል ነገር አታዉቅም።መንበሩን ፓሪስ ያደረገዉ ድንበር የለሽ ዘጋቢዎች የተሰኘዉ የጋዜጠኞች መብት ተሟጋች ድርጅት ባለፈዉ አመት ባወጣዉ ዘገባዉ ኤርትራ በፕረስ ነፃነት ከነ ሰሜን ኮሪያ በልጣ ከአለም የመጨረሻዉን ደረጃ ይዛለች።ሰሞኑን ባወጣዉ ሌላ መግለጫዉ ደግሞ የኢንተርነት ጠላት ብሏታል።

Eritrea Äthiopien Soldaten Flash-Galerie
ወታደሮችምስል AP

ሌሎች የመብት ተሟጋቾች እንደሚሉት ደግሞ ጋዜጠኞች፥ ተቃዋሚ ፖለቲከኞች ታስረዋል።ብዙዎች ደግሞ የደረሱበት አይታወቅም።አቶ ዓሊ ከወቀሳ ዉንጀላዉ አንዱንም አይቀበሉትም።
፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧፧
የአስመራ ባለሥልጣናት «የሠላም ደሴት» ቢሏትም ኤርትራ አካባቢዉን በሚያተራምሰዉ ግጭት ጦርነት እጇን ማስገባቷን ብዙዎች ይናገራሉ።የሰሜን አፍሪቃዉና የመካከለኛዉ ምሥራቅ ሕዝባዊ አመፅ አይመለከታትም ማለት አይቻልም።የመጪዉ ዘመን ሒደቷ እንደ እስከዛሬዉ ሁሉ ነገም ማጠያየቋም።ለዛሬዉ ነጋሽ መሐመድ ቸር ያሰማን።