1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኤቦላ ዳግም መከሰት

ሐሙስ፣ መጋቢት 29 2008

የዓለም ጤና ድርጅት በሶስት የምዕራብ አፍሪቃ ሀገራት፣ ሲየራ ልዮን፣ ላይቤሪያ እና ጊኔ የኤቦላ ስርጭት አብቅቷል ሲል ከአንድ ሳምንት በፊት ማወጁ ይታወሳል። ድርጅቱ እንዳመለከተው፣ ይኸው ተላላፊ በሽታ ለዚሁ አካባቢ ስጋት አይደቅንም። ግን አሁን የተኅዋሲዉ ስርጭት እንደ አዲስ መታየት ጀምሮአል።

https://p.dw.com/p/1IRVo
Liberia Schild Ebola ist real
ምስል picture-alliance/dpa/A. Jallanzo

[No title]

በምዕራብ አፍሪቃ ባለፉት ሁለት ዓመታት 29,000 ሰዎችን የያዘው እና ከ11,000 የሚበልጡ ሰዎችን ሕይወት ያጠፋው የኤቦላ አስተላላፊ ተኀዋሲ ስርጭት፣ በዓለም ጤና ድርጅት ዘገባ መሰረት፣ በጣም ዝቅተኛ ደረጃ ላይ ደርሶዋል። ይህም ቢባል ግን የተኀዋሲው ስርጭትም ሆነ ሰዉ በበሽታው እንዳይያዝ ያደረበት ስጋት አልተወገደም። በዚህም የተነሳ በትናንቱ ዕለት በመቶዎች የሚቆጠሩ የሲየራ ልዮን ዜጎች ለራሳቸው እና ለልጆቻቸው ተጨማሪ ድጋፍ፣ የሕክምና ርዳታ እና ለትምህርት ቤት መክፈያ ገንዘብ እንዲሰጣቸው በመጠየቅ በመዲናይቱ ፍሪታውን አደባባይ ወጥተው ውለዋል።

ከጥቂት ቀናት በፊት አንድ አምቡላንስ ላይቤርያ ውስጥ አንድ ሕይወቷ ያለፈች ሴት ይዞ ወደ ክሊኒክ ሲጣደፍ ታይቶ ነበር። ሴትዮዋ መሞቷ እየታወቀ ይኸ ሁሉ ጥድፊያ ለምን በሚል ከአንዳንዶች ለተነሳው ጥያቄ የላይቤርያ ምክትል የጤና ጥበቃ ሚንስትር ቶልበርት ኒዬንስዋህ እንዲህ ሲሉ ነበር የመለሱት።
« የ30 ዓመት ሴት ክሊኒኩ ስትደርስ መሞቷ ተረጋግጦዋል፣ ኤቦላ እንደነበረባት በምርመራ ታውቋል። ከመዲናይቱ ሞንሮቪያ ወጣ ብሎ በሚገኝ አካባቢ ነው የምትኖረው። እንደምታውቁት፣ የዓለም ጤና ድርጅት ላይቤሪያን ባለፈው እጎአ ጥር 14፣ 2016 ከኤቦላ ነፃ ብሎታል። ይህን ካለ ከሶስትወራት በኋላ አሁን እንደገና አንድ ሰው በኤቦላ ተኀዋሲ ተይዞዋል። »
አንዷ የሟች ሴት ልጅም በኤቦላ ተኀዋሲ ተይዛለች፣ እናትና ልጅ፣ ምንም እንኳን ድንበሩ ቢዘጋም፣ ከጎረቤት ጊኒ ነው ወደ ላይቤርያ የሄዱት። እርግጥ፣ እስካሁን ጥቂት ሰዎች ላይ ብቻ ነው የታየው። የዓለም ጤና ድርጅት በምዕራብ አፍሪቃ በኤቦላ ሰበብ ያወጀውን አስቸኳይ ሁኔታ ያበቃው ከአንድ ሳምንት በፊት ነበር። በኤቦላ የተጎዱት ሀገራት አዲስ ስርጭት ለመከላከል የሚያስችል አቅም እንዳላቸው በማስታወቅ፣ በጉዞ ላይ አርፎ የነበረው ገደብም ሊነሳ እንደሚችል ነው ምክትል ጤና ጥበቃ ሚንስትር ያስታወቁት።
« ሰው የሚረበሽበት አንድም ምክንያት የለም። አዲሱን ስርጭት ለመቆጣጠር የዓለም አቀፉ ድጋፍ አለን። »
በሽታውን ያስተላለፈውን ሰው እና ከሟች ጋር ግንኙነት የነበራቸውን ፣ ወደ መቶ ሊጠጉ ይችላሉ የተባሉትን ሰዎች በመፈለግ ላይ እንደሚገኝ ሚንስትሩ ገልጸዋል።
ምንም እንኳን ሚንስትሩ ስርጭቱን መቆጣጠር እንደሚቻል ቃል ቢገቡም፣ ሕዝቡ መስጋቱ አልቀረም። ሰዉ እጁን የሚታጠብበት ክሎሪን ያለበት ውኃ አሁንም በየቦታው በባሊ ተቀምጦለታል። መጨባበጥም ሆነ ተቃቅፎ ሰላምታ መስጠት ብዙ አይደፍርም። በመንግሥቱ የጤና ጥበቃ አውታርም ላይ እንደበፊቱ እምነት የለውም።
ድንበር የማይገድበው የሀኪሞች ድርጅት ባካሄደው አንድ መጠይቅ መሰረት፣ በሲየራ ልዮን ቢታመም ወደ ሀኪም ቤት ለመሄድ የሚፈልግ አንድም ሰው የለም። ትኩሳት ወይም ተቅማጥ የያዘው ሰው ፣ በተላላፊው ኤቦላ መያዙን ስለሚፈራ፣ ከሀኪም ቤት ይልቅ ወደ ፋርማሲ መሄዱን ይመርጣል። ይህ ግን ግለሰቡ በርግጥ በኤቦላ ተኀዋሲ መያዝ አለመያዙን ለይቶ የማወቁን ስራ ያጓትተዋል።
እንደሚታወሰው፣ ጊኒ ከኤቦላ ነፃ በተባለችበት በ2015 መጨረሻ ትልቅ ፈንጠዝያ አድርጎ ነበር ያከበረው። አሁን በመሀሉ ግን ሰባት ሰዎች በተኀዋሲው ባለፈው ወር ሞተዋል። ወደ 1000 የሚጠጉ ደግሞ ተጠርጥረዋል። ክትትል እየተደረገላቸው ነው ። ከነዚህ 800 በዓለም ጤና ድርጅት መሰረት፣ ፍቱን ሊሆን ይችላል በሚባል ለሙከራ ላይ ያለ ክትባት ሊሰጣቸው ታስቦዋል።
ይህ አዲስ ክስተት የጤና አውታራቸው አሁንም ደካማ ለሆኑት የኡ ኤቦላ የተጎዱት ሀገራት በገንዘብ ምክንያት ብቻ ሳይሆን ባጠቃላይ ትልቅ ምት ነው። የሲየራ ልዮን ጤና ጥበቃ ሚንስቴር ቃል አቀባይ ሲድያያ ቱኒስ ሀገራቸው ባለፈው ጥር ወር ከኤቦላ ነጻ ከተባለች ከአንድ ሳምንት በኋላ አስs ሰው መያዙን ይፋ ባደረጉበት ጊዜ፣ ይህ በሀገሪቱ የኤኮኖሚ ልማት ላይ ዘላቂ ጉዳት እንዳያስከትል አስጠንቅቀዋል።
« በጣም በጣም ቅር የሚያሰኝ ጉዳይ ነው፣ ኤቦላ በሲየራ ልዮን፣ ላይቤሪያ እና ጊኔ ላይ አሉታዊ ይህም ኤኮኖሚው ንተፅዕኖ አሳርፎዋል። ማህበራዊ ትብብራችንንም አዳክሞዋል። »
ሲየራ ልዮን እንደ ጎረቤቶችዋ የጤና መቆጣጠሪያ ኬላዎች እንደገና ተክላለች፣ ይህም፣ የዓለም ጤና ድርጅት ባልደረባ ስዊድናዊ ሀንስ ሮዝሊንግ ከአንድ ዓመት በፊት « ኤቦላ ተመልሶ ሊመጣ ይችላል፣ ጨርሶ እስኪጠፋ ድረስ ብዙ ዓመታት ሊወስዲ ይችላል» ያሉበትን አነጋጋር የሚያስታውስ ሆኖዋል።

Grenze Guinea Liberia Ebola
ምስል I. Sanogo/AFP/Getty Images
Genf WHO erklärt Ebola-Notstand für beendet
ምስል picture-alliance/dpa/S. di Nolfi
Liberia Händewaschen gegen Ebola
ምስል picture-alliance/dpa/A. Jallanzo

ሽቴፈን ኤልበርት/አርያም ተክሌ

አዜብ ታደሰ