የኦባማና የአውሮፓ ግንኙነት
ማክሰኞ፣ ኅዳር 4 2005የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዝዳንት ባራክ ኦባማ ዳግም እንዲመረጡየአሜሪካውያን ደጋፊዎቻቸው ብቻ ሳይሆን የበርካታ አውሮፓውያንንም ምኞት ነበር ። ከተፎካካሪያቸው ከሪፐብሊካውያኑ እጩ ሚት ሮምኒ በበለጠ አብዛኛዎቹ የሃገር ውስጥም ሆነ የማህበራዊ ና የፖለቲካ መርሃቸው ከአውሮፓውያኑ መርህ ጋር ይበልጥ መቀራረቡ ኦባማን ተመራጭ አድርጓቸዋል ። ከጠንካራ ፉክክርና የምርጫ ዘመቻ በኋላ ሪፐብሊካኑን ሚት ሮምኒን በሰፊ ልዩነት አሸንፈው ለ2ተ ኛ የሥልጣን ዘመን የተመረጡት የኦባማ የአውሮፓ መርሃቸው ከበፊቱ እንደማይለወጥ ነው የፖለቲካ ተንታኞች የሚያስረዱት ። ይሁንና አንዳንድ ፖለቲከኞች ኦባማን ይህ ነው የሚባል የአውሮፓ ፖሊሲ የላቸውም ሲሉ ይተቻሉ ። ስለ ኦባማ የአውሮፓ ፖሊሲ አስተያየታቸውን የተጠየቁት የአውሮፓ ህብረት ፓርላማ አባል ጀርመናዊቷ ፍራንትሴስካ ብራንትነርጥያቄውን መመለስ የጀመሩት በጥያቄ ነው ።
« ጥያቄው ለመሆኑ ኦባማ የአውሮፓ ፖሊሲ አላቸው እንዴ ? እኔ እስከማውቀው ድረስ ባለፉት 4 አመታት አውሮጶች ከኦባማ ጋር ያን ያህል ተቀራርበው የሰሩበት መርህ አልታየም ። አልተጓዘችም ። እንድ እንደ ምሳሌ ልጠቅስ የምችለው የዩናይትድ ስቴትስ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትርና የአውሮፓ ህብረት የውጭ ጉዳዮች ሃላፊ ካትሪን አሽተን የጋራ ጥቅም እንዳላቸው ለማሳየት በባልካን ሃገራት በጋራ መገኘታቸውን ነው ። ከዚህ ውጭ እውነት ለመናገር ኦባማ በአውሮፓ እብዛም አልነበሩም ማለት ነው የሚቻለው ። »
የአውሮፓና የዩናይትድ ስቴትስን ግንኙነት የሚከታተሉ የፖለቲካ ተንታኞች እንደሚሉት የዩናይትድ ስቴትስ የውጭ ፖሊሲ ትኩረት ይብለጡን ወደ እስያ እያደላ ነው ።
ኦባማና ሮምኒ ባካሄዱት በውጭ ፖሊሲ ላይ ባተኮረው የቴሌቪዥን ክርክራቸው አውሮፓ ብዙም አልተነሳም ። በቴሌቪዥን ክርክሩም ሆነ በሌሎች እንቅስቃሴዎች በአሁኑ ጊዜ ዩናይትድ ስቴትስ ፊቷን ወደ እስያ ማዞሯ ጎልቶ ይታያል ። በዚህ የተነሳም ቻያናና የመሳሰሉት የእስያ አገራት የዩናይትድ ስቴትስን ቀልብ ስበው አውሮፓ ተረስታለች የሚል አይነት አስተሳሰብ ይንፀባረቃል ። የ ብራንትነር ም አስተያየት ከዚህ የተለየ አይደለም ።
« አውሮፓ አሁን አስተማማኝነቷ የማያወላውል በአንፃራዊነት የተረጋጋች አጋር ተደርጋ ነው የምትወሰደው ። ሆኖም አሁን በፋይናንሱ ቀውስ ሰበብ በርካታ አሜሪካውያን አውሮፓ ላይ አትኩረዋል ። አውሮፓ ከፊናንሱ ቀውስ ጋር በተያያዘ ትኩረት ሳቢነትዋ ይጨምር ይሆናል ። ከዚያ ውጭ ግን የኦባማ ትኩረት እስያ ነው ። »
ዩናይትድ ስቴትስ አውሮፓን በመተው ከአትላንቲክ ማዶ ለማዶው ግንኙነት አሁን ፊቷን ወደ እስያ ፓስፊክ አዙራለች ፤ ግንኙነታቸው ቀዝቅዟል ፤ ወይም ተራርቀዋል የሚለውን አባባል ብዙዎች አይቀበሉትም ። በነርሱ አስተያየት አውሮፓ እንደ ቀድሞው የዩናይትድ ስቴትስ እጅግ አስፈላጊና አስተማማኝ አጋር ሆና መቀጠሏ አይቀርም ። የአሜሪካን የውጭና የደህንነት ፖሊሲ ሚዛን ከአውሮፓ ወደ እስያና ወደ መካከለኛው ምሥራቅ ማዘንበሉ አውሮፓ ላይ ምን ተፅዕኖ ያሳድር ይሆን ተብለው የተጠየቁት የቀድሞው የ ጀርመን መራሄ መንግሥት የሄልሙት ኮል የፀጥታ ጉዳዮች አማካሪ ፕሮፌሰር ኽርስት ቴልትሺክጥቅሙ የጋራ ነው አይነት አስተያየት ነው የሰጡት ።
« ድምዳሚዮ በጣም ቀላል ነው ። ዩናይትድ ስቴትስ እንደ ልዕለ ኃያል ሃገር ይበልጡን በእስያ ላይ ማተኮሯን ትቀጥላለች ። ምክንያቱም የቻይናና የዩናይትድ ስቴትስ ግንኙነት ለአካባቢው ደህንነትና ሰላም መሠረታዊ ጉዳይ ነው ። ይህም ለአውሮፓውያን ትልቅ ጠቀሜታ አለው ። ለዚህም ነው የቻይናና የዩናይትድ ስቴትስ ግንኙነት ሃላፊነት በተሞላው መንገድ ይበልጥ ሲዳብር የማየት ከፍተኛ ፍላጎት ያለን ። ያም ማለት አሜሪካውያን እዚህ ላለው ሁኔታ በኛ እምነታቸውን ጥለዋል ። እኛ ባልተረጋጋው በባልካን ሃገራት ና በነበሩበት በቆሙ ሌሎች ግጭቶች ላይ እንድንጠመድ ትተውናል ። »
በአንዳንድ ተንታኞች አባባል የአውሮፓንና የዩናይትድ ስቴትስን ግንኙነት የቀዘቀዘ ያስመሰለው አሜሪካን በሌላው አለም በሚከሰቱ እጅግ አንገብጋቢ ጉዳዮች ላይ መጠመዷ ነው ። በአውሮፓ ግን ከቅርብ አመታት ወዲህ ከተከሰተው የኢኮኖሚ ቀውስ ውጭ ሌላ አንገንጋቢ የሚባል ችግር አልታየም ። ይህ ሲባል ግን ዩናይትድ ስቴትስ ከአውሮፓ የምትጠብቀው ነገር አይኖርም ማለት አይደለም ። ኦባማ በ 4 ት አመት ተጨማሪ የሥልጣን ዘመናቸው አውሮፓውያን ኤኮኖሚያቸውን እንዲያሻሽሉ ይጠብቃሉ ። ምክንያቱም የተዳከመው የአሜሪካን ኤኮኖሚ ማንሰራራት ከአውሮፓ ኤኮኖሚ ማገገም ጋር በእጅጉ የተያያዘ ነውና ። የኦባማ አስተዳደር ባለፉት አመታት የአውሮፓን የዩሮ ቀውስ አያያዝ በተደጋጋሚ ሲተች ነበር ። በመጪዎቹ ጊዜያትም ማሳሰቢያውን መቀጠሉ እንደማይቀር ነው ብራንትነር የሚገምቱት ።
« በአጠቃላይ በአውሮፓ የገንዘብ ቀውሱ አያያዝ ላይ የአለም አቀፉ ማህበረሰብ ትዕግሥት እየተሟጠጠ ነው ። እስከማናውቀው ድረስ ኦባማ ብቻ ሳይሆኑ ሌሎች በርካታ ባለሥልጣኖቻቸውም አውሮፓውያን ትንሽቷን ሃገር ግሪክን ከውድቀት ማዳን ባለመቻላቸው ተሰላችተዋል ። ከኛም በበለጠ ለአሜሪካውያን ግሪክ ትንሽ ሆና ነው የምታታያቸው ግሪክ ከአውሮፓ የኤኮኖሚ ጥንካሬ 2 በመቶውን ነው የምትወክለው ። ከ 2 አመት ተኩል በላይ በወሰደ ጊዜ ችግሩን መፍታት አለመቻሉ አይገባቸውም ። ቀውሱ ወደ ስፓኝ ኢጣልያ ና ሌሎችም ትላልቅ አገራት እንዳይዛመት ግፊቱ ይጠናከራል ብዮ እገምታለሁ ። »
የከአትላንቲክ ማዶ ለማዶው ግንኙነት በኢኮኖሚው ማገገም ላይ ብቻ የሚወሰን አይሆንም ። ከኤኮኖሚው ሌላ አውሮፓ በአለም ዓቀፍ ጉዳዮች ላይ ንቁ ተሳታፊ እንድትሆንም የኦባማ አስተዳደር ተጫማሪ ጥሪ ሊያደርግ እንደሚችል ይጠበቃል ። ከነዚህም መካከል የአለምን ትኩረት ለሳበው ለሶሪያው የርስ በርስ ጦርነት የጋራ መፍትሄ ፍለጋ እንዲሁም የኢራን የኒዩክልየር መርሃ ግብር ያስነሳውን ውዝግብ መፍታት ሊሆኑ ይችላሉ ። በተለይ ወደ ግጭት ሊያመራ እንደሚችል በሚያሰጋው በኢራን ጉዳይ መፍትሄ ፍለጋ በአውሮፓ ግዙፍ ኤኮኖሚ የምታንቀሳቅሰው የጀርመን ድርሻ ምን ይሆናል ፕሮፌሰር ቴልትሺክ
« ወደ ኢራን ስንመጣ ሁኔታዎች ይለያሉ ። በዚህ ረገድ ኦባማ በማሸነፋቸው ተደስቻለሁ ። ምክንያቱም ርሳቸው ቅድሚያ የሚሰጡት ለዲፕሎማሲያዊ መፍትሄ ነው ። እኛም በርግጥ ከ 5 ቱ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት አባላት ጋር ጉዳዩን እንከታተላለን ። እዚያም ቢሆን ከአሜሪካን ጋር በቅርብ ትብብር ነው ልንንቀሳቀስ የምንችለው ። ግቡ ግጭት መሆን አይችልም ። ከተመክሮአችንና ከቀዝቃዛው ጦርነት ታሪካችን በመነሳት ከኢራን ጋር ማድረግ ያለብን ውይይትና ትብብር እንጂ ግጭት አይደለም »
። ጀርመንም ሆነች በአጠቃላይ አውሮፓ በአለም የፖለቲካ መድረክ የቀድሞውን ቦታቸውን እንዲይዙ ምን ማድረግ ይገባቸዋል ? ፕሮፌሰር ቴልትሺክ
« ጀርመን አሁን በተዘበራረቀ ሁኔታ ውስጥ ነው ያለችው ። በአንድ በኩል በአውሮፓ የመሪነቱን ሚና ይዘናል በሌላ በኩል ደግሞ በግሪክ የሚካሄዱትን ተቃውሞዎች በቅርበት ስናይ የተዘበራረቀ ስሜት ይፈጥራል ። ስለዚህ ለጀርመን አንድ መልስ ብቻ ነው ሊኖር የሚችለው ። ግልፅና አሳማኝ የውጭ ፖሊሲ ይዘን መቅረብ ይኖርብናል ። ምንድነው የምንፈልገው ? ይህ ጉዳይ ከዩናይትድ ስቴትስም ቁልፍ ጥያቄ ጋርም ይያያዛል ። »
ይህ በተለይ የቀድሞው የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዝዳንት የጆርጅ W ቡሽ መስተዳድር አውሮጳ ውስጥ ሊተክል ካቀደው የሚሣይል መከላከያ ጋር የተገናኘ ነው እንደሚታወቀው ፕሬዝዳንት ኦባማ ሥልጣን ከያዙ ወዲህ የምሣይል መርሐ ግብሩን ለመቀየር እንደሚሹ አስታውቀዋል እንዲያውም ሚሣይል መተከሉን አጥብቃ ለተቃወመችው ለሩስያ የቀድሞ ፕሬዝዳንት ዲሚትሪ ሜድቬዴብ ሚሣይል ተከላው የቡሽ መስተዳድር ባቀረበው መንገድ እንደማይቀጥል ቃል ተገብቶላቸዋል ።
አንዳንድ አውሮፓውያን ፖለቲከኞች ሮምኒ ፕሬዝዳንት ቢሆኑ በጆርጅ W ቡሽ እንደሆነው አውሮፓ እንደገና ትከፋፈል ነበር ይላሉ ። የሮምኒ የቻይና የሩስያ እና የመካከለኛው ምሥራቅ መርህ አውሮፓን በመከፋፈል ለጥፋት ይዳርግ ነበር ባይ ናቸው እነዚህ ወገኖች ። በነርሱ አባባል የኦባማ መመረጥ ለአውሮፓ በጣም ጥሩ ውሳኔ ነው ።
ሂሩት መለሰ
ነጋሽ መሐመድ