1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኦጋዴን የሠላም ድርድር

ረቡዕ፣ ነሐሴ 1 2005

ዓለም አቀፉ አጥኚ ተቋም ICG እንደሚለዉ ልዩነቱን ለማስወገድ መሠረታዊዉ ነገር የሁለቱ ፖለቲካዊ ራዕይ ነዉ።አርቆ ማስተዋሉ ካለ ዉክልና ወይም ሥልጣን መጋራት፥በጋራ ጉዳዮች በጋራ መወሰን አካባቢዉን ማልማት፥የሕዝቡን ኑሮ ማሻሻሉም አይገድም።

https://p.dw.com/p/19LST
12.06.2013 DW Online Karten Basis Äthiopien Englisch

የኢትዮጵያ መንግሥትና የኦጋዴን ብሔራዊ ነፃ አዉጪ ግንባር (ኦብነግ) በቅርቡ ሊያደርጉት ያቀዱት ድርድር ለዉጤት እንዲበቃ ሁለቱም ወገኖች አበክረዉ መጣር እንደሚባገባቸዉ ዓለም አቀፉ የግጭት መፍትሔ አፈላላጊ ጥናት ተቋም መከረ።ICG በሚል ምሕፃረ-ቃል የሚጠራዉ ተቋም እንደሚለዉ በኦጋዴን ዘላቂ ሠላም ለመማምጣት ሁለቱም ወገኖች በትዕግሥትና ባርቆ አስተዋይነት መደራደር፥ መመተማመን ማስፈን እና ለአካባቢዉ ልማትና ለሕዝብ ጥቅም ትኩረት መስጠት አለባቸዉ።የአፍሪቃ ቀንድ የፖለቲካ ተንታኝ ረሺድ አብዲም ሁለቱ ወገኖች ወታደራዊ እርምጃ መፍትሔ እንደማይሆን አዉቀዉ መግባቢያ ነጥቦችን ለማግኘት ከልብ መጣር አለባቸዉ።ነጋሽ መሐመድ አጭር ዘገባ አለዉ።

የሁለቱ ወገኖች ተወካዮች ባለፈዉ ጥቅምት ናይሮቢ-ኬንያ ዉስጥ በኬንያዎች ሸምጋይነት ሁለት ዙር ድርድር አድርገዉ ነበር።ወዲያዉ ግን ሁለቱም ከሃያ-ዓመታት በላይ እንደኖሩበት ወደ ግጭት፥ ጦርነት፥ ወደ መወቃቀስ መወጋገዝ ገቡ።አሁን ካመት ዕረፍት በኋላ ይጀመራል የተባለዉም ድርድር የአፍሪቃ ቀንድ የፖለቲካ አጥኚ ረሺድ አብዲ እንደሚሉት ለሁለቱም «ፈታኝ» ነዉ የሚሆን።

«እንደሚመስለኝ በጣም ከባድ ድርድር ነዉ-የሚሆነዉ።ሊቆም፥ ሊቋረጥም ይችላል።ይሁንና እንደሚመስለኝ ሁለቱም፥ የኢትዮጵያ መንግሥትም፥ የኦጋዴን ብሔራዊ ነፃ አዉጪ ግንባርም በድርድሩ መጀመር ማመናቸዉ ራሱ ጥሩ እርምጃ ነዉ።»

ያለፈዉ ድርድር ለመቋረጡ እንደ ዋና ምክንያት የተጠቀሰዉ ኦብነግ የኢትዮጵያን ሕገ-መንግሥት እንዳለ አልቀበልም በማለቱ ነበር።ይሕ ልዩነት ረሺድ አብዲ እንደሚሉት አሁንም አልተወገደም። ዋናዉ ግን በፖለቲካ አጥኚዉ እምነት ሁለቱ ወገኖች መጀመሪያ ላይ ከማያግባባቸዉ ይልቅ በሚያግባቧቸዉ ነጥቦች ላይ ማተኮር፥ እና መተማመንን መመሥረት ነዉ።

«በሕገ-መንግሥቱ ላይ የተፈጠረዉ አለመግባባት መቀጠሉ አይቀርም።ይሁንና ሁለቱ ወገኖች ከልብ ካሰቡበት ሌሎች የመግባቢያ ነጥቦች ያገኛሉ።በቀላሉ የሚግባቡባቸዉ ጉዳዮች አሉ።ከዚሕም በተጨማሪ እርስ በርስ መተማመን የሚያስፍኑባቸዉን ሥልቶች መከተል አለባቸዉ።ለምሳሌ እስረኞችን መልቀቅ፥ ግጭትን፥ ፕሮፓጋንዳን ማቆም አለባቸዉ።በተከታታይ መገናኛት እና መወያየት ይገባቸዋል።በድርድሩ የመጀመሪያ ደረጃ እነዚሕን ማድረግ አለባቸዉ።»

ሌላዉ ቀስ በቀስ ይመጣል ባይ ናቸዉ ረሺድ አብዲ።

የቱርክ፥ የብሪታንያ፥ የኢጣሊያ ቅኝ ገዢዎች በየዘመናቸዉ በዘመቱ ቁጥር ያ ሠፊ በረሐማ ግዛት ጦርነት ተለይቶት አያዉቅም።ኢትዮጵያና ሶማሊያ በተጋጩ ቁጥር የመጀመሪያዉ አስከሬን የሚወደቅዉም እዚያ ነዉ።ኦጋዴን።

ኦብነግ አሁን የያዘዉን መልክና ባሕሪ ይዞ ከተደራጀበት ከ1976 ጀምሮ ከኢትዮጵያ ማዕከላዊ መንግሥት ጦር ጋር ባደረገዉ ዉጊያያም በብዙ ሺሕ የሚቆጠሩ ሰዎች ተገድለዋል።በመቶ ሺሕ የሚቆጠሩ ተሰደዋል፥ አለያም ተፈናቅለዋል።ጦርነቱ ከጥፋት ባለፍ ያመጣዉ ለዉጥ ግን የለም።ቢዘገዩ-አሁን፥-«ሁለቱም ይሕን መረዳት አለባቸዉ።» ይላሉ ረሺድ አብዲ።

«በኢትዮጵያ መንግሥትም፥ በኦብነግም በኩል የሥልት ለዉጥ ያደረጉ ይመስለኛል።ለዚሕ ግጭት ወታደራዊ እርምጃ መፍትሔ እንደማይሆን ማወቅ አለባቸዉ።በድርድር ፖለቲካዊ መፍትሔ መፈለግ አለባቸዉ።እንደሚመስለኝ ይሕንን ሁለቱም የተገነዘቡት ይመስለኛል።»

ሁለቱም የተገነዘቡትን ሐቅ ገቢር ለማድረግ ግን ብዙ እንቅፋት፥ ሰፊ ልዩነት መኖሩ እርግጥ ነዉ።ዓለም አቀፉ አጥኚ ተቋም ICG እንደሚለዉ ልዩነቱን ለማስወገድ መሠረታዊዉ ነገር የሁለቱ ፖለቲካዊ ራዕይ ነዉ።አርቆ ማስተዋሉ ካለ ዉክልና ወይም ሥልጣን መጋራት፥በጋራ ጉዳዮች በጋራ መወሰን አካባቢዉን ማልማት፥የሕዝቡን ኑሮ ማሻሻሉም አይገድም።ICG-እንደሚመክረዉ።

የኦጋዴን ችግር ረሺድ አብዲ እንደሚሉት የኦጋዴን ወይም የኢትዮጵያ ብቻ አይደለም።የአካባቢዉ ጭምርም እንጂ።በመፍትሔ ፍለጋዉም የአካባቢዉ መንግሥታት በተለይ የኬንያ መንግሥት እና የኢጋድ አስተዋፅኦም ቀላል አይደለም።

«በመሠረቱ ኬንያ ለግጭቱ መፍትሔ የመፈለግ ፍላጎት አላት።ምክንያቱም የኦጋዴን ጉዳይ በሶማሊያም ባጠቃላይ ባካባቢዉም ትልቅ ትርጉም አለዉ።ሥለዚሕ የኦጋዴን ችግር መፍትሔ እንዲያገኝ አካባቢያዊ በሙሉ ይፈልጋል።ምክንያቱም የኦጋዴን ችግር ከተወገደ የአካባቢዉ ሐገራት ሥለሶማሊያ ጉዳይ በቀላሉ መተባበር ይችላሉ።»

ዋንኞቹ ግን የአዲስ አበባና የኦብነግ ሹማምንታት ናቸዉ።

ነጋሽ መሐመድ

Zerstörte Schule in Hargeisa, Somalia
ጦርነት-ጥፋትምስል AP
Angriff auf chinesische Ölarbeiter in Äthiopien
ምስል AP

ሸዋዬ ለገሠ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ