1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኮንሶ ጥያቄ ግጭት እና መፍትሄው

እሑድ፣ መስከረም 15 2009

መንግሥት ኮንሶ በሰገን ዞን የተጠቃለለው ህዝቡን የልማት ተጠቃሚ ለማድረግ ነው ይላል ። ጥያቄውን የሚያቀርቡትንም የግል ጥቅማቸውን ለማስፈጸም የሚሯሯጡ ሲል ይከሳል ። ኮሚቴው በበኩሉ በዚህ ውሳኔ ህዝቡ ማህበራዊ ኤኮኖሚያዊ እና ፖለቲካዊ ጥቅሞቹን ተነፍጓል ሲል ይከራከራል ።

https://p.dw.com/p/1K7TN
Karte Äthiopien englisch

በኢትዮጵያ የደቡብ ብሔር ብሄረሰቦች ክልላዊ መንግሥት ሥር የሚገኘው የኮንሶ ወረዳ ነዋሪዎች ባነሱት የአስተዳደር ጥያቄ ሰበብ በተቀሰቀሰ ግጭት ፣ የሰዎች ህይወት መጥፋቱ ፤ ቤት ንብረት መውደሙ፤ እና ነዋሪዎችም መፈናቀላቸው በተደጋጋሚ ተዘግቧል ። ባለፈው ሳምንትም ግጭቱ ተባብሶ ተጨማሪ ህይወት እና ንብረት ጠፍቷል ።የጥያቄው መነሻ ልዩ ወረዳ የነበረው ኮንሶ በ2004 ዓም ከ5 ሌሎች ልዩ ወረዳዎች ጋር በሰገን ህዝቦች ዞን ስር መጠቃለሉ ሲሆን ጥያቄውን የሚያስተባብረው ኮሚቴ አባላት ይህ የተደረገው ህዝቡ ሳይጠየቅ በክልሉ አመራሮች ውሳኔ መሆኑን ይናገራሉ ። የክልሉ መንግሥት ኮንሶ በሰገን ዞን የተጠቃለለው ነዋሪውን የልማት ተጠቃሚ ለማድረግ ነው ይላል ። ጥያቄውን የሚያቀርቡትንም የግል ጥቅማቸውን ለማስፈጸም የሚሯሯጡ ሲል ይከሳል ። ኮሚቴው በበኩሉ በዚህ ውሳኔ ህዝቡ ማህበራዊ ኤኮኖሚያዊ እና ፖለቲካዊ ጥቅሞቹን ተነፍጓል ሲል ይከራከራል ። በዚህ ውዝግብ መነሻነት በተለይ ካለፈው ዓመት አንስቶ የክልሉ ኃይል በወረዳው በወሰደው የኃይል እርምጃ ቀደም ሲል እንደተገለፀው ሰዎች መገደላቸው መታሰራቸውን እና መፈናቀላቸው ይነገራል ። የክልሉ መንግሥት በበኩሉ ሰዎችን በማጥቃት በማፈናቀል እና ቤቶችን በማቃጠል የኮሚቴውን አባላት ተጠያቂ ያደርጋል ። የኮንሶዎች ጥያቄ ግጭቱ እና መፍትሄው የዛሬው እንወያይ ትኩረት ነው ።

ኂሩት መለሰ

ልደት አበበ