1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የየመን ምስቅልቅል

ሐሙስ፣ የካቲት 5 2007

የየመን የፀጥታ ይዞታ እየተባባሰ መሄዱ እየተነገረ ነዉ። የሀገሪቱ የታጠቁ ኃይሎች እንቅስቃሴ ያሰጋቸዉ የዉጭ ዲፕሎማትና ኤምባሲዎችም መዘጋታቸዉ ተዘግቧል። እንደዘገባዎቹ ትናንት የዩናይትድ ስቴትስ፣ ብሪታንያና ፈረንሳይ ኤምባሲዎች ሙሉ በሙሉ ተዘግተዉ ሠራተኞቻቸዉም ከየመን ወጥተዋል።

https://p.dw.com/p/1Ea3r
Jemen - Huthi-Rebellen
ምስል Reuters

አሜሪካ ከዲፕሎማቶቿ በተጨማሪ የመን የሚገኙ የባህር ኃይል አባላቷንም ማስወጣት ጀምራለች። የሁቲ አማፅያን በበኩላቸዉ ኤምባሲዎቹ በጥድፊያ መዘጋታቸዉና ሠራተኞቹ እንዲወጡ መደረጉ ተቀባይነት የለዉም ሲል ተችቷል።

የየመን የፀጥታ ሁኔታ ከድጥ ወደማጡ ሆኖ ሕዝቡ በፍርሃት ቆፈን መቀፍደዱን ነዉ እዚያ የሚገኘዉ ጋዜጠኛ ግሩም ተክለሃይማኖት የሚገልፀዉ። የቀድሞ የሀገሪቱ ፕሬዝደንት አሊ አብደላ ሳልህ የሚመሩትን ጨምሮ የሀገሪቱ የተለያዩ ፓርቲዎች ተሰባስበዉ ጊዜያዊ የሽግግር መንግሥት ስለማዋቀር ተወያይተዉ አለመስማማታቸዉ፤ የሁቲ አማፅያኑም ቀጭን ትዕዛዝ ማስተላለፋቸዉ ዉጥረት ማንገሱን ያመለክታል።

Jemen Huthi-Rebellen verkünden Übergangsverfassung
የሁቲ አማፅያን ጉባኤምስል picture-alliance/dpa/Str

ዩናይትድ ስቴትስ፣ ብሪታንያና ፈረንሳይ የመን የሚገኙ ኤምባሲዎቻቸዉን በመዝጋት ሠራተኞችና ዜጎቻቸዉን ለማዉጣት መንቀሳቀሳቸዉ በየመን የቀዉሱን መባባስ በግልፅ አመላካች ነዉ። በትናንትናዉ ዕለትም የተጠቀሱት ሀገራት ኤምባሲዎች ጥንቃቄ የሚያስፈልጋቸዉ ያሏቸዉን ዶሴዎች፣ ኮምፕዩተሮች፣ ስልኮች እና ሌሎች መገልገያ መሣሪያዎቻቸዉን መሰባበርና ማዉደማቸዉ ተዘግቧል። ኤምባሲዎቹን ለዚህ ርምጃ የገፋፋቸዉ እንደጋዜጠኛ ግሩም አገላለፅ የሁቲ አማፅያኑ የዲፕሎማቲክ መብቶችን ያላገናዘበ እርምጃ ሳይሆን አይቀርም።

በዛሬዉ ዕለት የመን ዉስጥ የሚንቀሳቀሰዉ የአልቃይዳ ክንፍ ደቡባዊ የመን ዉስጥ የወታደራዊ ጦር ሠፈርን መቆጣጠሩን በትዊተር ገልጿል። በአካባቢ የሚገኙ የመንግሥት ባለስልጣን በሻብዋ ክፍለሀገር ባይሃን ያለዉ የ19ኛዉ ብርጌድ የጦር ሰፈር በታጣቂዎች መያዙንና በተኩስ ልዉዉጥም 3 ወታደሮችን ጨምሮ 7 ሰዉ መገደሉን ማረጋገጣቸዉን የፈረንሳይ የዜና ወኪል አመልክቷል።

በዓረቡ ዓለም ሕዝባዊ አብዮት በተቀጣጠለ ማግስት በጎርጎሪዮሳዊዉ 2011ዓ,ም ነበር የመንን ነዉጡ የጎበኛት። በቀጣዩ ዓመት መባቻም ለረዥም ዓመታት ስልጣን ላይ የቆዩት ፕሬዝደንት አሊ አብደላ ሳልህ መንበራቸዉን ለቀቁ። ያም ሆኖ የተፈጠረዉን የስልጣን ክፍተት የሚሞላ ጠንካራ ማዕከላዊ መንግሥት እስካሁን አላገኘችም። የሁቲ አማፅያን የምዕራቡን ዓለም ይሁንታ ያገኙት ፕሬዝደንት አብዲራቦ ማንሱር ሀዲን ቤተ-መንግሥት ከተቆጣጠሩ ወዲህ ፕሬዝደንቱን በቤታቸዉ በቁም እስር አኑረዉ የራሳቸዉን የአገዛዝ ስልት ለመትከል ቢሞክሩም በሁሉም ሕዝብ ዘንድ ተቀባይነት አላገኙም።

US Botschaft in Sanaa 27.01.2015
ሰንዓ የሚገኘዉ የዩናይትድ ስቴትስ ኤምባሲምስል Reuters/M. al-Sayaghi

የመን ለዚህ ቀዉስ የበቃችበት ዋነኛ መንስኤ እንደጋዜጠኛ ግሩም እንደሚለዉ ከመነሻዉ ለረዥም ዓመታት ሀገሪቱ የተከተለችዉ ማዕከላዊነትን ያልተከተለዉ የመንግሥት አስተዳደር ሳይሆን አይቀርም።

አሁን ሰንዓን የተቆጣጠሩት የሁቲ ሚሊሺያዎች ወደዚህ ደረጃ የደረሱትም ይህንኑ የአስተዳደር ክፍተት ተጠቅመዉ መሆኑንም ነዉ ጋዜጠኛ ግሩም የሚገልፀዉ። በአስጊ ሁኔታ ላይ እንደምትገኝ የገለፃትን የየመንን ቀጣይ ሁኔታ ከወዲሁ ለመገመትም አዳጋች መሆኑን ሳይጠቁም አላላለፈም።

ሸዋዬ ለገሠ

ተክሌ የኋላ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ