1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የየመን ውጥንቅጥና የጸጥታ ስጋት

ሰኞ፣ መጋቢት 14 2007

የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤት ትናንት መጋቢት 13 ባደረገው አስቸኳይ ስብሰባ አገሪቱ የርስ በርስ ጦርነት ውስጥ ልትገባ ትችላለች ሲል በድጋሚ አስጠንቅቋል። የሑቲ አማጽያን በበኩላቸው ወደ ደቡብ የመን የሚያደርጉትን ግስጋሴ ቀጥለዋል።

https://p.dw.com/p/1EvlH
Jemen Demonstration der Anhänger vom Ex-Präsidenten Saleh
ምስል Reuters/K. Abdullah

በየመን የሑቲ አማጽያን ፕሬዚደንትአብዱራባህማንሱርሃዲ ከሰንዓ ሸሽተዉ ወደ ተሸሸጉባት ኤደን እየገሰገሱ ነው። በየመን ሶስተኛ ትልቅ ከተማ በሆነችው ታዒዝ የሚገኘውን የአዉሮፕላን ማረፊያ እሁድ መጋቢት 13/2007 የተቆጣጠሩት ሰሜናውያኑ የሺዓ አማጽያን ዛሬ ደግሞ በሺዎች የሚቆጠሩ ታጣቂዎችን በመላክ ከሱኒዎች ጋር ውጊያ ላይ መሆናቸውን አዣንስ ፍራንስ ፕሬስ የዜና ወኪል ዘግቧል። ባለፈው ሳምንት ለተፈጸመውና 29 ወታደሮች ለሞቱበት ጥቃት ራሱን እስላማዊ መንግስት ከሚለዉ ፅንፈኛ ታጣቂ ቡድን ጋር ግንኙነት አለኝ የሚለው በየመን የአልቃኢዳ ክንፍ ሃላፊነት መውሰዱን አሶሲየትድ ፕረስ የዜና ወኪል ዘግቧል። የፖለቲካ ተንታኙ ዩሱፍ ያሲን በየመን የታጣቂዎች እና የውጭ ሃይሎች መበራከት የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤት እንዳለው ሃገሪቱን ወደ እርስ በርስ ጦርነት ሊከታት ይችላል የሚል ስጋት አላቸው።

22.03.2015 DW Journal Jemen eng

«በየመን የሑቲ አማጽያን፤የቀድሞው ፕሬዝዳንት አሊ አብደላ ሳልህ ወታደሮች እና የጎሳ ሚሊሺያዎች አሉ።የደቡብ ንቅናቄም አለ።የሳዑዲ አረቢያ እና የገልፍ አገሮች ትብብር አቋም አለ።የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ይኸ ጉዳይ የየመንን አንድነት ብቻ ሳይሆን ያካባቢው ሰላምና ጸጥታን ያደፈርሳል በሚል ጣልቃ እንዲገቡ እየተማጸኑ ናቸው። ግን ጣልቃ ከመግባታቸው በፊት እነሱ(የሑቲ አማጽያን) እስከ ኤደን ድረስ ሄደው ለመቆጣጠር እየሞከሩ ስለሆነ ይኸ ነገር ወደ ርስ በርስ ጦርነት ያመራል የሚለው ስጋት እንዳለ ነው።»

የመን በአልቃኢዳ ላይ ይደረግ በነበረው ዘመቻ አጋር የነበረች ቢሆንም አሁን ግን በኢራን እና ሳዑዲ አረቢያ የእጅ አዙር ጦርነት፤ በሺዓ እና ሱኒ ፍጥጫ ታምሳለች። ዩናይትድ ስቴትስ የመን ዉስጥ የነበራትን የመጨረሻ ኃይል ዛሬ ማስወጣቷ ተዘግቧል። የየመን መታመስ ግን በዚያው በየመን የሚያበቃ አይመስልም። ዩሱፍ ያሲን የውክልናው ጦርነትም ይሁን የታጣቂዎቹ እና የጦር ጄኔራሎቹ ፍጥጫ ሙሉ ቀጠናውን እንደሚያተራምሰው ይናገራሉ።

Jemen Bombenanschlag in einer Moschee in Sanaa
ምስል Reuters/Khaled Abdullah

የሑቲ አማጽያን የሚዋጉት ከፕሬዚደንትአብዱራባህማንሱርሃዲ ሃይሎች ጋር ብቻ ሳይሆን ከእስላማዊ መንግስት ግንኙነት አለኝ ከሚለው የየመን የአልቃኢዳ ክንፍ ጋር ጭምር ነው። አማጽያኑ የየመን ዋና ከተማ ሰንዓን ከመንግስታዊ ጽሕፈት ቤቶች ጋር ቢቆጣጠሩም እስካሁን መንግስት ለመመስረት ያደረጉት ሙከራ አልተሳካም። ከቀድሞው መሪ አሊ አብደላ ሳልህ በኋላ የፕሬዝዳንትነት መንበሩን የተረከቡት እና ሰንዓ ዉስጥ ከቆዩበት የቁም እስር አምልጠዉ ኤደን ላይ የከተሙት ማንሱር ሃዲ ደግሞ ሀገሪቱን ሙሉ ለሙሉ ተቆጣጥሮ የሚያረጋጋ ሃይል እንደሌላቸዉ እየታየ ነዉ። እናም የየመን እጣ ፈንታ በድቅድቅ ጨለማ ውስጥ ከመዳከር ጋር ተመሳስሏል። ይህን ክፍተት በሀገሪቱ የሚገኘው አልቃኢዳ እና ኢራቅ እና ሶርያን የሚያምሰው እስላማዊ መንግስት ሊጠቀሙበት ይችላሉ የሚለው ስጋት አይሏል።

እሸቴ በቀለ

ሸዋዬ ለገሠ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ