1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የደቡብ አፍሪቃ የወደፊት ዕጣ ፈንታ

ቅዳሜ፣ ታኅሣሥ 5 2006

የቀድሞው የደቡብ አፍሪቃ ፕሬዚደንት እና ዋናው የፀረ አፓርታይድ ታጋይ ኔልሰን ማንዴላ ሞት የሀገሪቱን ጥቁሮች እና ነጮች ዜጎች አቀራርቦዋል። በሀዘኑ ሰበብ የተፈጠረው ይኸው የመቀራረብ መንፈሥ ባለፉት

https://p.dw.com/p/1AZWx
Nelson Mandela Abschied 13.12.2013
ምስል Reuters

ቀናት የኔልሰን ማንዴላ አስከሬን ለጊዜው እንዲቆይ በተደረገበት ቀድሞ በፕሬዚደንትነት ይሰሩ በነበሩበት በፕሪቶርያ ቤተ መንግሥት ሕዝቡ በተሰናበተበት ጊዜ በግልጽ ታይቶዋል። ለወትሮው ይህ ዓይነቱ መቀራረብ መጓደሉን፣ ለምሳሌ ወደብሩክሊን የገበያ መደብር ጎራ ያለ ሰው ወዲያው ሊያየው ይችላል። በዚያ ያሉት ቡና እና ምግብ ቤቶች በምሳ ሰዓት አንድም ባዶ ጠረጴዛ አይገኝም፤ ግን፣ ጥቁሮች እና ነጮች ባንድነት የተቀመጡባቸው አይታዩም፤ ብዙዎቹ ተመሳሳይ የቆዳ ቀለም ካለው የሀገሩ ዜጋ ጋ ነው የሚቀመጠው።

ሀዘኑ ዜጎችን በዚህ ደረጃ ያቀራርባል ብላ እንዳልጠበቀች የገለጸችው በአንድ የገበያ አዳራሹ ሱቅ ውስጥ የምትሰራው የ25 ዓመቷ ማንዲፓ ጉማኒ ።ያም ቢሆን ግን በደቡብ አፍሪቃ በጥቁሮች እና በነጮች መካከል ለብዙ ዓመታት የተሰራበት ተለያይቶ የመኖሩ ሁኔታ አሁን ቀስ በቀስ በመጥፋት ላይ መሆኑን ትናገራለች። ተወዳጁን ፕሬዚደንት ለመሰናበት ብዙ ሰዓታት ከተሰለፉት ደቡብ አፍሪቃውያን መካከል አንዱ የሆነው እና በሕይወት የሌሉት ወግ አጥባቂው አባቱ ይህንን ርምጃውን እንደማይደግፉለት የተናገረው በመምህርነት የሚያገለግለው ነጩ ዲዮን ፈርማክም የወደፊቱን የሀገሩን ሁኔታ በተመለከተ ብሩህ አመለካከት እንዳለው ነው አስታውቋል።

Nelson Mandela Abschied 13.12.2013
ምስል Reuters

« እንደማስበው፣ ብዙ ተግዳሮቶች አሉ። ግን ቀጣይ ትውልድ ስላለ የወደፊቱ ሁኔታ ብሩህ እንደሚሆን አምናለሁ። ሕዝቡ ይህንኑ የመቀራረብ ሁኔታ ዘላቂ የማድረግ ኃላፊነት የተሰማው ይመስለኛል። »

ይሁንና፣ ከማንዴላ በኋላ የደቡብ አፍሪቃ የወደፊት ዕጣ ፈንታ ልክ እንደ ብዙዎቹ ደቡብ አፍሪቃውያን ማንዲፓ ጉማኒንም ያሳስባታል። በሀገሪቱ የሕዝብ ኤኮኖሚያዊ እና ማህበራዊ ኑሮ ይዞታ ላይ ተልቅ ልዩነት ይታያል። በዓለም ባንክ ዘገባ መሠረት፣ ወደ አንድ አራተኛ የሚጠጋው የደቡብ አፍሪቃ ሕዝብ በድህነት አፋፍ ላይ ይገኛል። የውሁዳኑ ነጮች ዘረኛ አገዛዝ ካበቃ ዛሬ ከ19 ዓመታትም በኋላ የአንድ ነጭ ደቡብ አፍሪቃዊ ዓመታዊ አማካይ ገቢ ከጥቁሩ የሀገሪቱ ዜጋ በስድት እጥፍ ይበልጣል። በሀገሪቱ ካሉት ሕፃናት መካከልም ግማሹ በድህነት ነው የሚኖረው። ከደቡብ አፍሪቃ የተፈጥሮ ሀብት መካከል ወደ 50 ከመቶ የሚጠጋው እጅግ ሀብታም በሚባሉት ከጠቅላላ የሀገሪቱ ሕዝብ መካከል 10 ከመቶውን በሆኑት ግለሰቦች እጅ ነው የተያዘው።

በደቡብ አፍሪቃ የሚታየው ድህነት ጊዚያዊ የሕዝብ ድጋፍ ለሚፈልጉ ከአፍሪቃውያኑ ብሔረተኞች ኮንግረስ፣ በምሕፃሩ ኤ ኤን ሲ ከተባረሩ በኋላ በእንግሊዝኛ ምሕፃሩ « ኤ ኤፍ ኤፍ» የተባለውን የኤኮኖሚ ነፃ አውጪ ታጋዮች ፓርቲ ላቋቋሙት ጁልየስ ማሌማን ለመሳሰሉ ግለሰቦች ጥሩ ሕዝብ መቀስቀሻ ምክንያት ፈጥሮላቸዋል። የሀገሪቱ ነጮች የያዙት መሬት እንዲወረስ እና ለጥቁሮች መከፋፈል አለበት ብለው የሚያምኑት የኤ ኤን ሲ የወጣቶች ቡድን መሪ የነበሩት ማሌማ በመስበክ እአአ የፊታችን ሚያዝያ 2014 ዓም በሚካሄደው ምክር ቤታዊ እና ፕሬዚደንታዊ ምርጫ ላይ በተወዳዳሪነት በመቅረብ የብዙ መራጭ ድምፅ ዕቅድ አላቸው። ይህ ዓይነቱ ፖለቲካ የኃይል ተግባር እንዳያስከትል መስጋቷን ወጣቷን ማንዲፓ ጉማኒ ገልጻለች።

Südafrika Pretoria Mandipha Gumani
ምስል DW/D. Pelz

« ትንሽ ግራ ተጋብቻለሁ። እነዚህ ሰዎች አሁን ማዲባ ከኛ ጋ ባለመኖራቸው ውጊያ እንዳይጀምሩ እናበሀገሪቱ ሁኔታዎች እንዳይቀያየሩ እሰጋለሁ። «ኢ ኤፍ ኤፍ »ንም ሆነ « ኤ ኤን ሲ» ን አናምናቸውም። ውጊያ የሚጀምሩ ይመስለኛል። »

የማህበራዊውን የኑሮ ዘርፍ ልዩነት ማጥፋት እና በሀቅ አንድ የሆነች ደቡብ አፍሪቃን መገነባት ከተፈለገ ብዙ መሰራት እንደሚኖርበት ሌላው ወጣት ትቺያቲ ንኳኔ አመልክቶዋል። ይህን በተመለከተ ኔልሰን ማንዴላ ድርሻቸውን አበርክተዋል፣ አሁን ደግሞ ሀገሪቱን የማሻሻሉ ተግባር የሌሎቹ ፈንት ነው ይላል። በተለይ የደቡብ አፍሪቃ ፕሬዚደንt ጄኮብ ዙማ የሚመሩት መንግሥት ብዙ ይጠበቅበታል። እስካሁን ስማቸው የሚነሳው ሕዝብን መቀስቀስ በተጠቀሙበት አነጋገራቸው እና የግል መኖሪያ ቤታቸውን በመንግሥት ንብረት አሰሩ በተባለበት ቅሌት ብቻ ነው።

መንግሥት ጥቁሮችን በሀገሪቱ ልማት ሂደት ውስጥ ይበልጥ ተሳታፊ ለማድረግ፣ ማለትም፣ ጥቁሮች ደቡብ አፍሪቃውያንን በመንግሥት መሥሪያ ቤቶች እና በትላልቆቹ ተቋማት ቦርዶች ውስጥ ቦታ ለማስያዝ የተነደፈውን መርሀግብር ማስፋፋት፣ እንዲሁም፣ ብዙ ወጣት ደቡብ አፍሪቃውያን የስራ ዕድል ለመፍጠር ይቻል ዘንድ የትምህርቱን ሥርዓት ማሻሻል እንዳለበት ትቺያቲ ንኳኔ አመልክቶዋል።

አርያም ተክሌ

ልደት አበበ

------

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ