የዴሞክራሲ ጥያቄን በኤኮኖሚ አብዮት መመለስ ይቻላል?
እሑድ፣ ሚያዝያ 1 2009አመፁን ተከትሎ መንግሥት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ቢደነግግም፣ በአንጻራዊነት ሰላም ከመስፈኑ ባሻገር ለአመፁ መቀስቀስ ምክንያት የሆኑ ችግሮች አለመፈታታቸዉ ይነገራል። መንግስት በበኩሉ በተለይ በኦሮሚያና በአማራ ክልል የሥራ አጥነት ችግርን ይፈታል ያለዉን «የኢኮኖሚ አብዮት»በሚል የተለያዩ እቅዶችን ነድፎ ወደ እንቅስቃሴ ገብቶአል። ግዙፍ ኩባንያዎችን የመመሥረትና በዓመት ለአንድ ሚሊዮን ለሚጠጉ ወጣቶች የሥራ እድልን መፍጠር ያስችላል የተባለዉ የኤኮኖሚ አብዮት የተለያዩ ጥያቄዎች አስነስቶዋል። « የኤኮኖሚ አብዮት ስንል ምን ማለታችን ነዉ?» በርግጥ ይህ የኤኮኖሚ አብዮት ለወጣቱ ጥያቄ መልስ ይሆናል? በመጪው እሁድ የሚተላለፈው እንወያይ የመነጋገሪያ ርዕስ ነው ። በውይይቱ የተሳተፉት እንግዶች፤ አቶ አበባዉ መሃሪ የቀድሞ የመኢአድ ፕሬዚደንትና ተባበሩት መንግሥታትን ጨምሮ በተለያዩ የአፍሪቃ ሃገራት በአማካሪነት የሰሩ የኤኮኖሚ ምሁር ናቸዉ። አቶ ጌትነት አልማዉ በባህርዳር ዩንቨርስቲ የማኔጅመንት ትምህርት ክፍል መምህርና የፖለቲካ ሳይንስ የሁለተኛ ዲግሪ ተማሪ እንዲሁም ዶክተር ደረጀ ገረፉ ቱሉ፤ የሰቢ ንግድ ማኅበር መስራችና የዉጭ ንግድ ባለሞያ ናቸዉ። ተወያዮች በዉይይቱ ላይ በመካፈላቸዉ እያመሰገንን ፤ ሙሉዉን ዉይይት የድምፅ ማድመጫ ማዕቀፉን በመጫን እንዲከታተሉ እንጋብዛለን።
አዜብ ታደሰ
ልደት አበበ