1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የዴሞክራቲክ አላያንስ እና የ«አኻንግ» ጥምረት መፍረስ

ቅዳሜ፣ የካቲት 1 2006

በደቡብ አፍሪቃ ባለፈው ዓመት የተቋቋመው የ«አኻንግ ኤስ ኤ» ፓርቲ ሊቀ መንበር የሆኑት ፀረ አፓርታይድ ታጋይ ዶክተር ማምፌሌ ራምፌሌ እአአ የፊታችን ግንቦት ሰባት በሚካሄደው ቀጣዩ ፕሬዚደንታዊ ምርጫ የዴሞክራቲክ ፓርቲ መሪ ሄለን ሲለ አስታወቁ።

https://p.dw.com/p/1B5Do
Südafrika PK Mamphela Ramphele
ምስል Alexander Joe/AFP/Getty Images

በእንግሊዝኛ ምሕፃሩ « ዲ ኤ» ፕሬዚደንታዊ ዕጩ ሆነው ለመወዳደር ደርሰውታል የተባለውን ስምምነት ማፍረሳቸውን የ« ዲ ኤ» መሪ ሄለን በዚህም ሄለን ሲለ ባለፈው ሳምንት በ« ዲ ኤ» እና በ«አኻንግ ኤስ ኤ» ፓርቲዎች መካከል ተመሥርቶ ነበር ያሉት ጥምረት ፈርሶዋል። የ« ዲ ኤ» ፓርቲ ከ31 ዓመታት በፊት በውሁዳኑ የነጮች መንግሥት ፖሊስ የተገደለው መብት ተሟጋቹ እና ፀረ አፓርታይድ ታጋይ ስቲቭ ቢኮ ባልተቤት የነበሩትን ማምፌሌ ራምፌሌን ፕሬዚደንታዊው ዕጩ አድርጎ ሊያቀርብ ባሰበበት ድርጊት በደቡብ አፍሪቃ ፕሬዚደንት ጄኮብ ዙማ አመራር እና በሀገሪቱ በሚታየው ከፍተኛው የድህነት ደረጃ ቅር የተሰኘውን የብዙኃኑን ደቡብ አፍሪቃውያን መራጮችን ድምፅ ለማግኘት ተስፋ አድርጎ ነበር። የ67 ዓመቷ ሀኪም ዶክተር ራምፌሌ የ « ዲ ኤ» ፕሬዚደንታዊ ዕጩ እንደሚሆኑ ካስታወቁበት ጊዜ አንስቶ የራሳቸው ፓርቲ ባለሥልጣናት እና አባላት ራምፌሌ ውሳኔውን ማንንም ሳያማክሩ ወስደዋል፣ በዚህም በብዛት ነጮች አባላት ላሉት የ«ዲ ኤ» ፓርቲ መሳሪያ ሆነዋል በሚል ከፍተኛ ወቀሳ አፈራርቀውባቸዋል። ይሁንና፣ ራምፌሌ ፕሬዚደንታዊ ዕጩ እንዲሆኑ የተደረሰው የ «ዲ ኤ» ፓርቲ ውሳኔ በሚገባ ያልተጤነ እና ካለርሳቸው ስምምነት እንደወሰደው በማስታወቅ ፕሬዚደንታዊ ዕጩ ሆነው እንደማይቀርቡ ገልጸዋል። እንደርሳቸው ገለጻ፣ የ « ዲ ኤ» ፓርቲ ከአኻንግ ፓርቲያቸው ጋ ባንድነት ጥምረቱን በሚመለከቱ ጉዳዮች ላይ እንዲመክር ሊያቋቁመው የነበረውን ኮሚቴ ስራ ገና ከጅምሩ ሊያሰናክሉ የሚችሉ በርካታ ማስታወቂያዎች ወጥተዋል።ማምፌሌ ገዢው የአፍሪቃውያኑ ብሔረተኞች ኮንግረስ ፣ «ኤ ኤን ሲ» በሚልዮን የሚቆጠሩ ደቡብ አፍሪቃውያን ድምፃቸውን እንደሚሰጡት በጭፍን የሚተማመንበትን ሁኔታ የሚያበቃ አዲስ የፖለቲካ ሥርዓት የመፍጠር ዓላማ ይዘው የተነሱት ማምፌሌ ከ«ዲ ኤ» ፓርቲ ጋ ይህን ዓላማቸውን ከግብ ለማድረስ እንደማይችሉ አስረድተዋል።

Südafrika PK Helen Zille
ምስል Marco Longari/AFP/Getty Images

« አሁን የ« ዲ ኤ» አባል መሆን ቢኖርብኝ እና ያ ያስቀመጥኩት ራዕዬ ገሀድ እንዲሆን ብፈልግ፣ « ዲ ኤ» ባቀረበለኝ ሀሳብ አማካኝነት ይህንን ፍላጎቴን ማሟላት አልችልም። ድምፃቸውን ለ« ዲ ኤ» የማይሰጡ በሚልዮን የሚቆጠሩ ደቡብ አፍሪቃውያን አሉ፤ እነዚህ ሰዎች የነሱን ጥቅም የሚያስጠብቅ ፓርቲ የው የሚፈልጉት። የ«አኻንግ» ፓርቲ ይህንን ፍላጎታቸውን ሊያሟላቸው ይችላል። »

Südafrika - Helen Zille und Mamphela Ramphele
ምስል Getty Images

ዶክተር ራምፌሌ ማምፌሌ ትክክለኛዋ ፕሬዚደንታዊ ዕጩም ነበሩ ብለው የሚያምኑት እና ማምፌሌ ዕጩነታቸውን በመሳባቸው ቅር የተሰኙት የ« ዲ ኤ» መሪ ሄለን ሲለ ማምፌሌ በሁለቱ ፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል ጥምረት እንዲፈጠር ጠንክረው እንደሰሩ በማስታወቅ የማምፌሌን አባባል አስተባብለዋል።

« ባለፉት ሦስት ዓመታት ተኩል በተደጋጋሚ ተወያይተናል። እና የጥምረቱ ምሥረታ በጋዜጣዊ መግለጫ ይፋ እንዲሆን የጠየቁት ራሳቸው ማምፌሌ ናቸው። »

ዶክተር ማምፌሌ የ « ዲ ኤ» ፕሬዚደንታዊ ዕጩነታቸውን የሰረዙበት ውሳኔ ተጣምረው የነበሩትን ሁለቱን ፓርቲዎች፣ ማለትም፣ « ዲ ኤ» ን እና «አኻንግ» ን የፊታችን ሚያዝያ ወይም ግንቦት ለሚካሄደው ምርጫ የሚያደርጉትን ዝግጅት አብዝቶ እንደሚጎዳ የፖለቲካ ተንታኞች ይገምታሉ። ፕሮፌሰር ሶማዶዳ ፊኬኒ እንደሚሉት፣ በተለይ ዶክተር ሄለን ሲለ በገዛ የ «ዲ ኤ » ፓርቲያቸው ውስጥ ያሉትን ጥቁሮቹን ደቡብ አፍሪቃውያን መሪዎችን ችላ በማለት የሌላውን ፓርቲ፣ የ«አኻንግ»ን መሪ ዶክተር ማምፌሌን ፕሬዚደንታዊ ዕጩ አድርገው መምረጣቸው ትልቅ ችግር ያጋጥማቸዋል።« አንድ ነጭ ተወዳዳሪ ወይም በፓርቲያቸው ካሉት ጥቁር ደቡብ አፍሪቃዊ መሪዎች አንዱን ፕሬዚደንታዊ ዕጩ አድርገው ቢሠይሙም እንኳን፣ ቀደም ሲል ችላ ያሉበት ውሳኔአቸው አዳጋች ሁኔታ ሊፈጥርባቸው እና በሚቀጥሉት ጊዚያት ምናልባት ከዚያው ከፓርቲያቸው ከባድ ፈተና እንዲጠብቃቸው ሊያደርግ ይችል ይሆናል። »

Mandela Trauerfeier Johannesburg 10.12.2013
ምስል Reuters

በዚያም ሆነ በዚህ በ «ዲ ኤ» እና በ«አኻንግ» መካከል አሁን የተፈጠረው ልዩነት ደቡብ አፍሪቃ ውስጥ አንድ የተባባረ የተቃዋሚ ቡድን የቆዳ ቀለም ሳይገድበው የሚመሠረትበት ጊዜ ገና መሆኑን አሳይቷል። ይህም የኔልሰን ማንዴላ ፓርቲ-ገዢው የአፍሪቃውያኑ ብሔረተኞች ኮንግረስ ፣ «ኤ ኤን ሲ » አሁንም ካለጠንካራ ተፎካካሪ እንዲቆይ አድርጓል። ምንም እንኳን ብዙ ደቡብ አፍሪቃውያን በሙስና ቅሌት በሚወቀሰው ገዢው ፓርቲ ከፍተኛ ቅሬታ ቢኖራቸውም። የውሁዳኑ ነጮች የዘር አድልዋ አገዛዝ ካበቃ ዛሬ ከ20 ዓመታት በኋላም በሀገሪቱ ድሆች እና ሀብታሞች መካከል ልዩነቱ እጅግ የሰፋ ነው። የወጣት ስራ አጥ ቁጥርም በጣም ከፍ ነው። በዚህም የተነሳ ብዙዎች ገዢውን ፓርቲ እየጣሉ በመውጣት ላይ ናቸው። ምክንያቱም ባለፉት ዓመታት ሀገሪቱ አስመዘገበችው ከተባለው የኤኮኖሚ ዕድገት ተጠቃሚዎች አልሆኑም።

አርያም ተክሌ

ሸዋዬ ለገሠ