1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

Merga Yonas Bula
ዓርብ፣ ጥር 12 2009

የሶማሊ ክልል የደንነት አካል የሆነዉ «ልዩ ፖሊስ» በመባል የሚታወቀዉ ኃይል በኦሮሚያ ክልል የሚገኙ አዋሳኝ ወረዳዎች ዉስጥ በነዋሪዎች ላይ ጥቃት መፈፀሙ ተሰምቷል።

https://p.dw.com/p/2W96h
Karte Äthiopien englisch

Border Clash between Oromia, Somalia - MP3-Stereo

በትናንትናዉ ዕለት የኦሮሚያ ክልል የኮሙዩኒኬሽን ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ አዲሱ አረጋ ለመንግሥት መገናኛ ብዙሃን በአጎራባች ወራዳዎች ግጭት መኖሩን በማረጋገጥ፤ በዚህም በሰው ህይወት እና ንብረት ላይ ጉዳት መድረሱን ጠቅሰዋል።

በኦሮሚያ ክልል በምሥራቅ ሐራርጌ ዉስጥ የሚገኙት አዋሳኝ ወረዳዎች በጥቃቱ ስር መዉደቃቸዉን ከሶማሊ ክልል ድንበር 40 ኪሎ ሜትር ባልበለጠ ርቀት ላይ የምትገኝ ስማቸዉ እንዲጠቀስ ያልፈለጉ የአማዩ ሙሉቄ ወረዳ ነዋሪ ለዶቼ ቬሌ ተናግረዋል። አማዩ ሙሉቄን ጨምሮ ጭናግሰን፣ ጉርሱም፣ ባብሌ፣ ምዳጋና ቁምቢ ወረዳዎች በልዩ ፖሊስ ቁጥጥር ሥር እንደሚገኙ በመግለፅም በምዕራብ ሐራርጌም ተመሳሳይ ነገር እንዳለም እኝህ የዓይን እማኝ ጠቅሰዋል። ለግጭቱ መንሴዎች ምንድን ናቸዉ፣ «በ1997 በሁለቱ ክልሎች መካከል ያሉት ወረዳዎች ላይ ምርጫ ተካሄዶ ነበር። ትንሽ ቆይቶ ከሶማሊ አካባቢ ባሉት ወረዳዎች ወረራ አወጁ። ከታወጀም በኋላ በ2006 ዓ/ም ብዙ ወረዳዎች በልዩ ፖሊስ ቁጥጥር ሥር ወድቀዋል። ከዚም የተነሳ በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ቀያቸዉን ትተዉ ሸሽተዋል፣ ንብረታቸዉ ተዘርፏል፣ ሴቶች ተደፍረዋል፣ ትምህርት ቤትና ጤና ኬላዎችም ተቃጥለዋል። ማኅበረሰቡ መሣርያ ባለመታጠቁ ብዙ ችግር ደርሶበታል። አማዩ ሙሉቄ ወረዳም በትናንትናዉ ዕለት በልዩ ፖሊስ ቁጥጥር ሥር ዉላለች።»

በአማዩ ሙሉቄ ወረዳ በግጭቱ ምክንያት የሰዉ ህይወት ማለፉን ተናግረዉም ግጭቱን ለማረጋጋት መከላከያ ሠራዊት በወረዳዋ ሰፍሮ እንደምገኝም ጠቅሰዋል። ግን ይላሉ፣ «መከላክያም ቢመጣ ርምጃ የሚወስደዉ በኦሮሞ ማኅበረሰብ ላይ ነዉ እንጂ በሶማሊ ደህንነት ላይ አይደለም። ስለዚህ እነሱ መፍትሄ ያመጣሉ ወይም የማኅበረሰቡን ደህንነት ያስጠብቃሉ የሚል ተስፋ የለንም።»

ይህም ሆኖ ከኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት በኩል ምንም ምላሽ አለማየታቸዉንም እኝሁ የአማዩ ሙሉቄ ነዋር ይናገራሉ።

በፊት የሶማሊ ክልል አካል መሆኑ የሚነገረዉ የጭናግሰን ወረዳ ግን ምርጫዉን ተከትሎ በኦሮሚያ ክልል ስር እንዲተዳደር ተደርጓል። በዚህ ወረዳም ግጭት እንደነበረ የሚናገሩት የዓይን እማኝ  የሰዉ ህወት ማለፉን ለዶቼ ቬሌ ገልጸዋል።

መርጋ ዮናስ

ሸዋዬ ለገሠ