የዶይቸ ቬለ የዓ/አቀፍ የመ/ብዙኀን መድረክ
ሰኞ፣ ሰኔ 18 2004ርእሶች፤ ባህል፣ትምህርት እና የመገናኛ ብዙኀን ናቸው።
« ትምህርት ለአጥናፋዊ ትስስር አንዱ መሰረታዊ ነገር ነው» ነው ያሉት የዶቸ ቬለ ዋና ስራ አስኪያጅ ኤሪክ ቤተርማን ስለዚኛው ዓመት የውይይት መድረክ አላማ ሲጠየቁ። መላው ህዝብ እንዴት አደርጎ ትምህርት ሊያገኝ እንደሚችል የመገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎች፣ ፖለቲከኞች እና በተለያዩ ሙያ የተሰማሩ ግለሰቦች ለሶስት ቀናት ዶቸ ቬለ ባዘጋጀው 5ኛ አመታዊ «የአለም አቀፍ የመገናኛ ብዙኀን መድረክ» ላይ ይመክራሉ።
« የበለጸገም ይሁን አዳጊ አገር፤ በምዕራብም ያለ ይሁን በምስራቅ፤ ትምህርት ባህል እና የሙያ ስልጠና ለሰላማዊ አኗኗር ፣ለዘላቂ እድገት እና በባህሎች መካከል ለሚኖረው ውይይት ወሳኝ ነገሮች ናቸው። » የመክፈቻውን ንግግር ያደረጉት የዶቸ ቬለ ምክትል ስራ አስኪያጅ ዶክተር ራይንሀርድ ሀርትእሽታይን ናቸው። ቤተርማን በስራ ምክንያት ወደ ሰሜን ጀርመን ስለተጓዙ ዛሬ በመድረኩ ላይ አልተካፈሉም። ይሁንና ቤተርማን አስቀድመው በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ እንደገለፁት፤እንደ ተባበሩት መንግስታት የህጻናት መርጃ ድርጅት (UNICEF)መዘርዝር በአለም ዙሪያ 101 ሚሊየን ማንበብ እና መፃፍ የማይችሉ ህፃናት አሉ። ይህም የሆነበት በርካታ ምክንያቶች አሉ። ወይ ወላጆች በድህነት የተነሳ ልጆቻቸውን ወደ ት/ቤት መላክ አይችሉም። ትምህርት ቤቱ በተማሪዎች ተጨናንቋል አልያም በእግር የሚደረስበት አይደለም። «በዚህም የተነሳ የመገናኛ ብዙኃን ትልቅ ኃላፊነት አለባቸው፤ ስለሆነም ማህበረሰቡን ለማስገንዘብ እንደ መሳሪያ ሊያገለግሉ ይገባል።» ነው ያሉት የዶቸ ቬለ ምክትል ስራ አስኪያጅ ሀርትእሽታይን።
« የመገናኛ ብዙኃን በሁለት መንገድ ወሳኝ ናቸው። ይፋ ማድረግ ያስፈልጋል። ችግሮቹ ምኑጋ እንደሆኑ ግልፅ ማድረግ ይኖርባቸዋል። በትምህርት ረገድ ያለው ልዩነቱ የት ድረስ እንደሆነ እና ለምን ይህንን መቅረፍ እንደሚገባ ማሳየት መቻል ይኖርባቸዋል።»
የሀርትእሽታይን ሀሳብ ሮላንድ በርኔከር፤ የጀርመን የተባበሩት መንግስታት የትምህርት የሳይንስና የባህል ድርጅት (UNESCO)ኮሚሽን ዋና ጸሐፊ ይጋራሉ። የፕረስ ነፃነት፣ የትምህርት ጥራት እና የተለያዩ ባህሎች ለነፃ ሲቪል ማህበረሰብ መሠረታዊ ነገሮች ናቸው።
ሶስት ቀናት በሚቆየው የዶቸ ቬለ «የአለም አቀፍ የመገናኛ ብዙኀን መድረክ» ላይ የቀድሞው የኢንዶኜዢያ ፕሬዚዳንት ዩሱፍ ሀቢቢ ፣ የጀርመኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጊዶ ቬስተርቬለ፤ እንዲሁም ሌሎች ታዋቂ ፖለቲከኞች ይገኛሉ። ከዋናው መድረክ ጎን 50 የተለያዩ የውይይት መድረኮች ተከፍተው የብሔራዊ እና አለም አቀፍ እንግዶች ተሰብስበው። ውይይታቸውን ጀምረዋል። የዶይቸ ቬለ «የአለም አቀፍ የመገናኛ ብዙኀን መድረክ» ኃላፊ ራልፍ ኖርቲንግ የውይይት መድረኩ ለምን አስፈላጊ እንደሆነ እንደሚከተለው ገልፀውታል።
« ምክንያቶቹ ፤ መድረኩ ፍፁም የመገናኛ ጉባኤ፣ የፖለቲካም ሆነ የማህበራዊ ሳይንስ አይደለም እንደዚህ ዓይነት ጉባዔዎች በአለም ላይ በርካታ ይገኛሉ። ይልቁንስ እኛ በዚህ አጋጣሚ ሰዎችን በጠረቤዛ ዙሪያ አሰባስበን፣ ለአለም አቀፉ ችግር ምን አይነት መፍትሄ ማግኘት እንደሚቻል እንዲያስቡበት መንገድ መፍጠር ነው። »
ባህል፣ትምህርት እና የመገናኛ ብዙኃንን ዋና ርዕሱ ያደረገው 5ኛው የዶይቸ ቬለ «የአለም አቀፍ የመገናኛ ብዙኸን መድረክ» እስከ ረቡዕ ድረስ ይዘልቃል።
ልደት አበበ
ተክሎ የኋላ