1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የግብፅ መንግሥት እርምጃና መገናኛ ዘዴዎች

ማክሰኞ፣ ነሐሴ 28 2005

የግብጽ የጦር ፍርድ ቤት በ52 የሙስሊም ወንድማማቾች አባላትና ደጋፊዎች ላይ ከአምስት ዓመት እስከ እድሜ ልክ እስራትን በየነ። ከተከሰሱት መካከል አንዱ የእድሜ ልክ እስራት ተፈርዶባቸዋል።

https://p.dw.com/p/19baq
ምስል picture-alliance/dpa

ፍርድ ቤቱ ከስልጣን የወረዱት ሞሐመድ ሙርሲ ሶስት ደጋፊዎች የ15ዓመት እስራት መበየኑም ተገልጿል። አል-ሐራም ጋዜጣን የጠቀሰዉ የጀርመን የዜና ወኪል ዘገባ እንዳመለከተዉ ሰዎቹ የተከሰሱት ጦር ኃይሉ ላይ ጥቃት በመሰንዘር እና ቤተ ክርስቲያናትን በማቃጠል ወንጀል ነዉ። ሌሎች 48 ተከሳሾችም በያዝነዉ ወር ካይሮ ላይ የጸጥታ ኃይሎች የሙርሲ ደጋፊዎችን ከየአደባባዩ ለማንሳት ሲሞክሩ በተነሳዉ ግጭት ለነበራቸዉ ሚና ከአምስት እስከ አስር ዓመት እስራት ተፈርዶባቸዋል። ከዚህም ሌላ የካይሮ ፍርድ ቤት በዛሬዉ ዕለት አልጃዚራን ጨምሮ አራት የቴሌቪዥን ስርጭቶች በሀገሪቱ እንዳይታዩ ትዕዛዝ አስተላልፏል። ንብረትነቱ የሙስሊም ወንድማማቾች ትስስር የሆነዉ አህራር 25፤ እንዲሁም አል ያርሙክ እና አል ቁዱስ የተሰኙት ጣቢያዎች እንዲዘጉ ተወስኗል። እንደዘገባዉ አህራር 25 ቴሌቪዥን ሙርሲ ከስልጣን እንደወረዱ ስርጭቱ ተቋርጧል። አልጃዚራ እንዲታገድ የተወሰነዉ መቀመጫዉ ዶሃ ለሚገኘዉ ቴሌቪዥን የሚሰሩ ሁለት የዉጭ ሀገር ጋዜጠኞችን ባለስልጣናት ከሀገር ካባረሩ በኋላ ነዉ። ይህ በእንዲህ እንዳለም የሀገሪቱ የዳኞች መድረክ መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት የሚለዉ የሙስሊም ወንድማማቾች ይዞታ እንዲሰረዝ ጊዜያዉን መንግስት ጠይቋል። በግብጽ ህግ መሠረት መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት የፖለቲካ ፓርቲን መደገፍ አይችልም። የመንግስት አቃቤ ሕግ በበኩሉ ተቃዋሚዎቻቸዉ የተገደሉበትን አመጽ በማነሳሳት ሙርሲ ላይ ክስ እንዲመሠረት ሃሳብ አቅርበዋል።
የግብፅ ጦር ሐይል የመሠረተዉ የሐገሪቱ ጊዚያዊ መንግሥት፥ ጦር ሐይሉ ያደረገዉን መፈንቅለ መንግሥትና መፈንቅለ መንግሥቱን በሚቃወሙ ወገኖች ላይ የሚወስደዉን የሐይል እርምጃ በሚዘግቡ ጋዜጠኞችና መገናኛ ዘዴዎች ላይ የከፈተዉን የመዝጋት ዘመቻ እንደቀጠለ ነዉ። ጊዚያዊዉ መንግሥቱ ለተለያዩ ዓለም አቀፍና አካባቢያዊ ቴሌቪዥን ጣቢያዎች የሚዘግቡ ጋዜጠኞችን አድም ከሐገር አባርሯል፥ አለያም የሥራ ፈቃድ ከልክሏል። አራት ቴሌቪዥን ጣቢያዎችን ዘግተዋልም። የተለያዩ የጋዜጠኞች መብት ተሟጋች ድርጅቶች እርምጃዉን ተቃዉመዉታል። የግብፅ ጦር በሕዝብ የተመረጡትን ፕሬዝዳት መሐመድ ሙርሲን በሐይል ከሥልጣን ካስወገደ ወዲሕ የዓረብ ዓለም መገናኛ ዘዴዎች ለሁለት ተከፍለዉ እየተኮቱ። የጂዳዉ ወኪላችን ነቢዩ ሲራክ ዝር ዝር ዘገባ ልኮልናል።

Ägypten Mohammed Mursi
ምስል Reuters

ነብዩ ሲራክ

ነጋሽ መሐመድ