1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የጎርጎሮሳዉያኑ 2009 ና ጋዜጠኝነት

ሐሙስ፣ ታኅሣሥ 22 2002

አሜሪካ ዉስጥ ባጠቃላይ ስድስት ጋዜጠኞች ተገድለዋል።አደገኛዉ ክፍለ-አለም ግን እስያ ነበር።አርባ-አራት ጋዜጠኞች ተገደለዋል።ብዙ ዘጋቢዎች የተገደሉባት ደግም ሶማሊያ ናት።ዘጠኝ።

https://p.dw.com/p/LHrl

31 12 09

ዛሬ እኩለ ሌት የሚያበቃዉ የጎርጎሮሳዉያኑ ሁለት ሺሕ ዘጠኝ ለጋዜጠኝነትና ለጋዜጠኞች መጥፎ የሚባል አመት እንደሆነ አለም አቀፉ የጋዜጠኞች መብት ተሟጋች ድርጅት አስታወቀ።መንበሩን ፓሪስ-ፈረንሳይ ያደረገዉ ድንበር የለሽ ዘጋቢዎች እንደሚለዉ በተሰናባቹ አመት በርካታ ጋዜጠኞች ተገድለዋል።ታስረዋል፥ ተመርምረዋል።እስራትና ግድያን ፍራቻ ተሰደዋል፥ሥራቸዉን ለቀዋል።ሐይነር ኪይዘል የዘገበዉን ነጋሽ መሐመድ አጠናቅሮታል።

እርግጥ ነዉ-ዘመኑን በጎርጎሮሳዉያኑ ቀመር-የሚያሰላዉ አሮጌ-ዘመን-ባዲስ ሊለወጥ-የሰአታት እድሜ ቀረዉ።ድንበር የለሽ ዘጋቢዎች እንደዘገበዉ ግን ዛሬ እኩለ ሌት አሮጌ የሚሆነዉ 2009 ለፕረስ ነፃነት መጥፎ ነበር።

በተሰናባቹ አመት ሙያዊ ግዴታቸዉን በመወጣት ላይ እንዳሉ በመንግሥታትና በታጣቂ ቡድናት የተገደሉ፥የተደበደቡ፥ቁጥጥር (ሳንሱር) የተደረጉ ጋዜጠኞችን ይዘረዝራል።የጀርመንኛዉን ዘገባ ያጠናቀሩት የድንበር የለሽ ዘጋቢዎች ባልደረባ አንያ ፊዮል እንደሚሉት የመጥፎ-መጥፎዉ ቁጥር ጨምሯል።
«ባብዛኛዉ መጥፎ አዝማሚያ ነዉ ያየነዉ።በብዙዎቹ መስክ ያሉት ቁጥሮች አሻቅበዋል።የተገደሉት ጋዜጠኞች ቁጥር፥ በመገናኛ ዘዴዎች ላይ የሚደረገዉ ቁጥጥር (ሳንሱር) ጨምሯል።ትንሽ ያሽቆለቆለዉ የታሰሩ ጋዜጠኞች ቁጥር ነዉ።»

ለሰአታት ዘንድሮ-እንደተባለ በሚቆየዉ ሁለት ሺ ዘጠኝ ሰባ-ስድስት ጋዜጠኞች ተገድለዋል።አምና ከተገደሉት ጋዜጠኞች በሃያ-አምስት ከመቶ ይበልጣል ማለት ነዉ።ከተገደሉት ጋዜጠኞች አብዛኞቹ የፊሊፒንስ ዜጎች ናቸዉ።እንደገና ፊዮል

«አብዛኞቹ ፊሊፒንስ ዉስጥ ነዉ-የተገደሉት።ባለፈዉ ሕዳር ሚንዳዎ ደሴት ዉስጥ ነዉ የተገደሉት።እዚያ ባንድ ቀን ሰላሳ-ጋዜጠኞች ናቸዉ የተገደሉት።በሙሉ የዚያዉ ሐገር ዜጎች ናቸዉ።በዚሕ አመት ከተገደሉት ጋዜጤኞች ካንዱ በስተቀር በሙሉ የተገደሉት በየሐገራቸዉ ነዉ።»

ከሐገሩ ዉጪ የተገደለዉ ብቸኛዉ ጋዜጠኛ-የስጳኝና የፈረንሳይ ዜግነት የነበረዉ የዘገቢ ፊልም አዘጋጅ ክርቲያን ፖቬዳ ነዉ።መስከረም መጀመሪያ ላይ ኤልሳልቫዶር ዉስጥ በጥይት ተገደለ።አሜሪካ ዉስጥ ባጠቃላይ ስድስት ጋዜጠኞች ተገድለዋል።አደገኛዉ ክፍለ-አለም ግን እስያ ነበር።አርባ-አራት ጋዜጠኞች ተገደለዋል።ብዙ ዘጋቢዎች የተገደሉባት ደግም ሶማሊያ ናት።ዘጠኝ።

«ከዘጠኙ ስድስቱ የተገደሉት በአክራሪ እስላማዊ ቡድናት ነዉ።እዚያ (ሶማሊያ) ነፃ መገናኛ ዘዴ የሌለ-ያክል ነዉ።ለሕዝብ ነፃ መረጃ ለመስጠትና በዉጊያ ቀጠና ዉስጥ ደፍረዉ ገብተዉ ለመዘገብ የሚፍጨረጨሩ ጥቂት ራዲዮ-ጣቢያዎች አሉ።ሁኔታዉ እንደዚሕ በመሆኑም ዘንድሮ ላንድ ራዲዮ ጣቢያ የሚሰሩ ሰወስት ጋዜጠኞች ተገድለዋል።»

ሥለ ዉጊያ፥ ሥለ ምርጫ ዉዝግብ እና ፖለቲካዊ እሰጥ አገባ የሚዘግቡ ጋዜጠኞች ከመገደል ቢያመልጡ ይደበደባሉ፥ ይታሰራሉ።ወይም የዛቻና ማስፈራራ ሰለቦች ናቸዉ።እና ሞት እስራት ዱላን ፍራቻ ይሰደዳሉ።አለምን የመታዉ የምጣኔ ሐብት ቀዉስም ለጋዜጠኛዉ እንደ አብዛኛዉ ሰዉ ሥራ ከማጣቱ ሌላ ሥለ ቀዉሱ መዘዘገቡ ሌላ ፈተና ነዉ-ያስከተለበት።

Medienfreiheit Bosnien Werbeplakate der Journalistenvereinigung
ምስል Ljiljana Pirolic

አዲሱ የመገኛ ዘዴ ኢንተርኔትም-የድንበር የለሽ ዘጋቢዎች አመታዊ ዘገባ እንዳረጋገጠዉ የፀረ-ጋዜጠኛ ሐይላት ሰላባ ሆኗል።ዘንድሮ የታሰሩት የኢንተርኔት ጋዜጠኞች አምና ከታሰሩት በአንድ መቶ ሐምሳ-ከተሞ ጨምሯል።አምና ሰባ ስምንት ታስረዉ ነበር።ዘንድሮ-አንድ መቶ ሐምሳ-አንድ።

ኢንተርኔት በመዝጋትና የኢንተርኔት ዘጋቢዎችን በማሰር ኢራንና ቻይና አንደኞች ናቸዉ።አሁንም አንያ ፊዮል፣-

«የሆነ ነገር በፌስ ቡክ በመላካቸዉ፥ወይም ፎቷቸዉ በፌስ ቡክ ወይም ዩ-ቱዩብ በመታየቱ ብቻ ብዙ ሰዎች መታሰራቸዉን አረጋግጠናል።ይሕ ግን ትክክለኛ ዘጋቢዎች አስተያየት ሰጪዎች በመሆናቸዉ አይደለም።(በባለሥልጣናት) ላይ የተነሳዉን ተቃዉሞ የሚያመለክቱ መልዕክቶች በማስተላለፋቸዉና ወይም ያስተላልፋሉ ተብለዉ በባለሥልጣኑ በመጠርጠራቸዉ ነዉ።ለዚሕም ነዉ እኛ ዘንድሮ በዚሕ መሁኔታ ያለዉን ለብቻዉ የዘረዘር ነዉ።»

አመቱ-የተገበረለትን ያክል-የጋዜጠኛ ሕይወት፥ አካል፥ ነፃነት አስገብሮ-በርግጥ አለቀ።መጪዉም አመት ሌላ-የጋዜጠኛ ሕይወት፥ አካል፥ ነፃነትን መስዋዕት እንደሚጠይቅ መገመቱ ነዉ-ሰቀቀኑ።ከዘንድሮ ከቀጠሉት ግጭት፥ ጦርነት፥ ዉዝግቦች ሌላ-ዉዝግብ፥ ግጭት ያስከትላሉ የሚባሉ ኢትዮጵያ፥ኮትዲቮር፥ሺሪላንካ፥ ኢራቅ በርማ ምርጫ አለ።ለጋዜጠኛዉ-ድንበር የለሽ ዘጋቢዎች እንደሚገምተዉ ተጨማሪ አደጋ አለ።

Heiner Kiesel
Negash Mohammed