1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የጎርጎሮሳዊ 2013ዓ,ም የመሪዎች መልዕክት

ማክሰኞ፣ ታኅሣሥ 23 2005

የጎርጎሮሳዊዉ አዲስ ዓመት በየሀገራቸዉ የሰዓት አቆጣጠር ትናንት እኩለ ሌሊት የተቀበሉ ሀገሮች መንግስታት ለህዝባቸዉ ተስፋን ብቻ ሳይሆን ማሳሰቢያን ያዘሉ መልዕክቶች አስተላልፈዋል። የካቶሎካዊት ቤተክርስቲያን ሊቀጳጳሳት ቤኔዲክት 16ኛ በበኩላቸዉ አዲሱ ዓመት 2013 የሰላም ዓመት ይሆናል የሚል የተስፋቸዉን ገልፀዋል።

https://p.dw.com/p/17C2t
ምስል Getty Images

የጎርጎሮሳዊዉ አዲስ ዓመት 2013 እንደአዲስነቱ ተስፋን ብቻ ሳይሆን ስጋትንም ይዞ መምጣቱ እንደማይቀር የተለያዩ ሀገር መሪዎች ዕለቱን አስመልክተዉ ለሀገራቸዉ ህዝብ ባደረጉት ንግግር ጠቁመዋል። መንፈሳዊዉ መሪ የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ቤኔዲክት አስራ ስድስተኛ አዲሱ ዓመት በካፒታሊዝም በሽብርተኝነትና ወንጀለኝነት ስጋት የተጎዳዉ ዓለም ሰላምን የሚያገኝበት ዘመን እንደሚሆን ያላቸዉን ተስፋ ገልፀዋል።

Nordkorea Neujahrsansprache von Kim Jong Un
ኪም ዩንግ ዑንምስል dapd

ስለሰላም የሃይማኖቱ መሪ መስበካቸዉ ቢጠበቅም፤ በታጠቀችዉ የኒኩሊየር የጦር መሳሪያ፤ እንዲሁም በምታደርጋቸዉ የሚሳኤል ፍተሻዎች መሰል አቅም ያላቸዉ የዓለማችን ጉልበታም ሀገሮች በዓይነ ቁራኛ የሚከታተሏት ሰሜን ኮርያ መሪ በዚህ ዓመት ለሀገራቸዉና የደቡብ ኮርያን ሰላም ቆርጠዉ መነሳታቸዉን ያመላከተ ንግግር ነዉ ያደረጉት። በአባታቸዉ እግር የተተኩት የሰሜን ኮርያዉ ፕሬዝደንት ኪም ዮንግ ዑን በሰሜኑና በደቡብ ኮርያ መካከል ዘመን የተሻገረዉ ፍጥጫና ግጭት እልባት እንዲያገኝ ጥሪ አድርገዋል።

«ጠቃሚዉ ጉዳይ በሰሜንና ደቡብ መካከል ያለዉን ፍጥጫ በማስወገድ የተከፋፈለዉን ሀገር ወደአንድነት ማምጣት የሚቻልበትን መንገድ መፈለግ ነዉ። ባለፈዉ በኮርያዉያን መካከል የነበረዉ ግንኙነት እንደታየዉ በአንድ ሀገር መሪዎች መካከል የሚደረገዉ መፋጠጥ የሚያመራዉ ወደጦርነት እንጂ ወደሌ እንዳልሆነ አመላክቷል።»

አያታቸዉ ኪም ሱንግ ሁለተኛ ከዚህ ዓለም በሞት ከተለዩበት ከጎርጎሮሳዊዉ 1994ዓ,ም ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ ከአንድ የሀገሪቱ መሪ እንደቀረበ በተገለፀዉ የአዲስ ዓመት መልዕክታቸዉም ኪም ዮንግ በሀገራቸዉ መሠረታዊ ለዉጥ እንደሚኖርም አመልክተዋል። 

Merkel Neujahrsansprache SPERRFRIST
አንጌላ ሜርክልምስል dapd

የጀርመን መራሂተ መንግስት አንጌላ ሜርክል በበኩላቸዉ በአዉሮጳ ብሎም በዩሮ የጋራ ሸርፍ ተጠቃሚ ሀገሮች በተከሰተዉ የፋይናንስ ቀዉስ ከባድ ኃላፊነት ለተሸከመች ሀገራቸዉ ህዝብ መጪዉን ጊዜ በጥንቃቄ ለማለፍ እንዲሰናዳ አመላክተዋል። ለዚህም  በቆራጥነትና በፅናት እንዲቆም ጥሪ አቅርበዋል፤

«አንድ ነገር ለመዘወርና ለመለወጥ መጀመሪያ ላይ የሚደረገዉ ሙከራ ሁልጊዜም ከባድና ዉጤቱም አነስተኛ ነዉ። የማኅበራዊ ተሃድሶ አራማጁ አዶልፍ ክሎፒንግ እንዳሉት «ቁርጠኝነትን የሚያሳይ ፅኑ ነዉ።» ይህ ከነጥቡ የሚያደርሰን ይመስለኛል። በአሁኑ ጊዜም ሀገራችን ዉስጥ ቆራጦጥና ሌሎችን ለመርዳት ዝግጁ የሆኑ በርካቶች አሉ።»  

ሜርክል በቴሌቪዝን በቀረበዉ ንግግራቸዉ አዲሱ ዓመት ካለፈዉ ዓመት ይበልጥ በኤኮኖሚዉ ረገድ ከበድ እንደሚል መግለፃቸዉ ዘገባዎች እንደሚሉት መልዕክታቸዉ ባለፈዉ ሳምንት አሮጌዉ ዓመት ከማለቁ አስቀድ ሞየገንዘብ ሚኒስትራቸዉ ከተናገሩት ጋ ይቃረናል። የገንዘብ ሚኒስትር ቮልፍጋንግ ሾይብለ በዩሮ ዞን በኤኮኖሚዉ ረገድ በግንባር ቀደምትነት ለምትገኘዉ ሀገር ክፉዉ ወቅት አልፏል ማለታቸዉም ተጠቅሷል። ሜርክል ከዚህም ሌላ የሀገሪቱም ወታደሮች፤ ፖሊሶችና የመንግስት ሠራተኞች በሀገራቸዉም ሆነ በተለያዩ የዓለም ክፍሎች ለሰላም ላደረጉ ትጥረት ማአስተዋፅኦም አመስግነዋል።

Zentralafrika Francois Bozize
ፍራንሲስ ቦዚዜምስል dapd

አፍሪቃ ዉስጥ አማፅያን ከመንበራቸዉ ሊገለብጧቸዉ የተቃረቡት የማዕከላዊ አፍሪቃ ሪፑብሊክ ፕሬዝደንት ፍራንሲስ ቦዚዜ ደግሞ አማጽያን ወደዋና ከተማ ባንጉዊይ እንዳይገቡ መማፀናቸዉ ተሰምቷል። አማፅያኑ መሳሪያቸዉን እንዲያስቀምጡ የጠየቁት ቦዚዜ እስከመጪዉ የጎርጎሮሳዊ 2016ዓ,ም ድረስም በስልጣን እንዲቆዩ ፋታ እንዲሰጧዉም ጠይቀዋል። በጎርጎሮሳዊዉ 2007ዓ,ም ቦዚዜ የገቡትን ቃል ማለትም ለአማፅያኑ መሪ ገንዘብና ስራ እሰጣለሁ ያሉትን አልፈፀሙም በሚል የሚቃወሟቸዉ አማፅያንም የእሳቸዉን ጥሪ በመቀበል እና ባለመቀበል ሃሳብ መከፈላቸዉን ሮይተርስ አመልክቷል።

በተለያዩ ሀገሮች የሚታየዉ ሁኔታም ዓመቱ የራሱ ተራ ሳይገባ ያለፈዉ ዓመት 2012 ያሻገረበትን ችግሮች ተሸክሞ መጀመር መገደዱን አመላክቷል።

ሸዋዬ ለገሠ

ሂሩት መለሰ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ