1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የፀረ-ወባ ዘመቻና ዉጤቱ

ሐሙስ፣ ሚያዝያ 14 2002

ሥልቱን ለማስፈፀም በዉጤቱም የአስር-አመቱን እቅድ ገቢር ለማድረግ የአለም ጤና ድርጅት በየአምቱ አምስት ቢሊዮን ዶላር እንደሚያስፈልግ አስታዉቆ ነበር።ድርጅቱ ባለፈዉ ዘጠኝ አመት ከመንፈቅ ያገኘዉ ግን 2.7 ቢሊዮን ብቻ ዶላር ነዉ።

https://p.dw.com/p/N3Al
ምስል DW-TV

22 04 10

የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት አባል ሐገራት እንደ ጎርጎሮሳዉያኑ አቆጣጠር በ2001 ባፀደቁት ሥምምነት መሠረት በአስር አመት ዉስጥ በወባ በሽታ የሚመሞቱና የሚታመሙ ሰዎች ቁጥር በግምሻ መቀነስ አለበት።በስምምነቱ የተያዘዉ የአስር አመት ገደብ ሊጠናቀቅ የወራት እድሜ ነዉ የቀረዉ። እስካሁን የተገኘዉ ዉጤት ግን ብዙ የሚያወላዳ አይደለም።የወባ በሽታ ከሚያጠቃቸዉ ሐገራት እቅዱን ገቢር ያደረጉት በጣም ትንሽ ናቸዉ።ብዙዎቹ ግን እቅዱን ገቢር ማድረግ አልቻሉም።አዙምፕታ ላቱዝ የዘገበችዉን ነጋሽ መሐመድ አጠናቅሮታል።


አንድ መቶ ስምንት ሐገራት ለወባ የተጋለጡ ናቸዉ።ወባ በነዚሕ ሐገራት በየአመቱ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎችን ትገላለች።ብዙ ሚሊዮኖችን ታሰቃያለች።በ1992 ግድም የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት «የፀረ-ወባ አስርት» ያለዉ እቅዱ በአስር አመት ዉስጥ ወባ የሚትገድል-የምታሳምመዉን ሰዉ ቁጥር በግማሽ ለመቀነስ ያለመ ነበር።

አባል ሐገራት ያፀደቁትን እቅድ ከግብ ለማድረስ የአለም ጤና ድርጅት WHO በእንግሊዝኛ ምሕፃሩ እንደ ሁነኛ ብልሐት ያየዉ በሽታዉ በተሰረጨባቸዉ አካባቢዎች ለሚኖረዉ ቢያንስ ሰማንያ በመቶ ለሚሆነዉ ሕዝብ የወባ ትንኝ መከላከያ የመረብ አጎበር ማከፋፈል ነዉ።አጎበሩ ርካሽ ዉጤቱ በአለም ጤና ድርጅት የፀረ-ወባ መርሐ ግብር አስተባባሪ ፕሮፌሰር አዋ ማሪ ኮል-ሴክ እንደሚሉት አጥጋቢ ነዉ።ምሳሌያቸዉ-ኢትዮጵያ።

«አጎበሩን በመጠቀም ብቻ እድሜያቸዉ አምስት አመት ባልሞላ ሕፃት ላይ የሚደርሰዉን ሞት ሃያ አምስት ከመቶ መቀነስ ይቻላል።በጣም የሚያሰቃይ የወባ በሽታን ደግሞ በሐምሳ ከመቶ መቀነስ ይቻላል።የኢትዮጵያን ሁኔታ ምሳሌ ብጠቅስላችሁ።እነሱ በሁለት አመት ጊዜ ዉስጥ ወደ ሃያ ሚሊዮን አጎበር ማከፋፈል ችለዋል።ይሕ ደግሞ በበሽታዉ የሚሰቃየዉን ሰዉ ብዛት በሐምሳ ከመቶ እንዲቀንስ አድርጓል።»

በወባ የሚሞትና የሚሰቃየዉን ሕዝብ ቁጥር ለመቀነስ የወጣዉን የአስር አመት እቅድ ገቢር በማድረጉ ሒደት ከአንድ መቶ ስምንቱ ሐገራት ኢትዮጵያን ያክል እንኳን የተሳካላቸዉ ጥቂት ሐገራት ብቻ ናቸዉ።ዘጠኝ።ታንዛኒያ ደግሞ የሁለት ተቃራኒ እዉነት ሐገር ናት።ደሴቲቱ ዛንዚባር በወባ-የሚሞትና የሚታመምባትን ሕዝብ አርባ በመቶ ለመቀነሱ ተሳክቶላታል።ዋና ምድሯ ግን ትንሽ ከተሳካላቸዉ አንዷ ናት።

የአንዲቱ ሐገር ሁለት ገፅታ ምክንያት በርግጥ ብዙ ነዉ።ዋናዉ ግን ከአስተዳደራዊዉ ልዩነት አይዘልም።የዛንዚያባር የጤና ጉዳይ አስተዳዳሪዎች ከግማሽ ሚሊዮን የሚበልጥ አጎበር አከፋፍለዋል። ከሁለት መቶ አስራ-ሰወስት ሺሕ በሚበልጡ መኖሪያ ቤቶችን በሰወስት ዙር ዘመቻ ፀረ-ትንኝ ረጭተዋል።

Kampagne gegen Malaria in Kenia
ፀረ-ወባ ዘመቻምስል picture-alliance/dpa

የደሴቲቱ የወባ መቆጣጠሪያ ማዕከል ሐላፊ ምዊኒይ ምሰለም እንደሚሉት ጤና ጣቢያዎቻቸዉም የወባ በሽታን መመርመር እንዲችሉ አደራጅተዋል።
«ከዛንዚባር የጤና ተቋማት ሰባ አራት ከመቶ የሚሆኑት የአጭር ጊዜ የወባ በሽታ ምርመራ ያደርጋሉ።ሃያ ስድት ከመቶ ያሕሉ ተቋማት ደግሞ ረቂቅ ምርመራ የማድረግ አቅም አላቸዉ።ተመርማሪዉ የወባ በሽታ እንዳለበት ካረጋገጥን በሽተኛዉ ቅይጥ የፀረ-ወባ መድሐኒት እንዲወስድ እናደርጋለን።»

ወባን ለመቆጣጠር አጎበር ማዳል፥ ቤቶችን መርጨት፥ በሽተኛዉን ፈጥኖ ማከም እና የወባ ትንኝ መራቢያ ሥፍራዎችን ማጥፋት አለም አቀፉ ድርጅት ከነደፋቸዉ ሥልቶች ዋነኞቹ ናቸዉ።ሥልቱን ለማስፈፀም በዉጤቱም የአስር-አመቱን እቅድ ገቢር ለማድረግ የአለም ጤና ድርጅት በየአምቱ አምስት ቢሊዮን ዶላር እንደሚያስፈልግ አስታዉቆ ነበር።ድርጅቱ ባለፈዉ ዘጠኝ አመት ከመንፈቅ ያገኘዉ ግን 2.7 ቢሊዮን ብቻ ዶላር ነዉ።

የገንዘቡ እጥረት እቅዱ በአብዛኞቹ ሐገራት ላለመሳካቱ አንድ ግን ትልቅ ምክንያት ነዉ።ሁለተኛዉ ፕሮፌሰር ኮል-ሴክ እንደታዘቡት በወባ የሚታመም-የሚሞተዉ ሕዝብ ሥለመከላከያዉ በቂ ግንዛቤ አለማግኘቱ ነዉ።

«ይሕ የጎንዮሽ ታሪክም አለዉ።አንዳድ ሰዎች የአጎበሩን መረብ-ለአሳ ማስገሪያነት ተጠቅመዉበታል-የሚል ታሪክ።ይሕ የተከሰተዉ በአንዳድ ሐገራት ሰዉ ሥለ አጎበሩ አጠቃቀም ምንም በማያዉቅበት ወይት ነበር።»

ፕሮፌሰሯ እንዲሕ አይነቱን ችግር ለማስወገድ ለማሕበረሰቡ ሥለ አጎበር አጠቃቀምና ሥለ ወባ መከላከያ ትምሕርት እየተሰጠ መሆኑን አስታዉቀዋል።ለእቅዱ ገቢራዊነት ግን በርግጥ አልደረሰም።

አዙምፕታ ላቱዝ

ነጋሽ መሐመድ

አርያም ተክሌ