1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የ 2012 ሟርትና እውነታው፣

ረቡዕ፣ የካቲት 7 2004

እውን 2012 ጎርጎሪዮሳዊው ዓመት የኅልፈተ ዓለም ዘመን ሊሆን?!ነገ ፤ ወደፊት፣ በተጨባጭ ሁኔታ ሊከሠት ስለሚችለው የፕላኔታችን ዕጣ -ፈንታ፣ የሥነ ፍጥረት ጠበብት ፣ በእርግጥ በአጭርና በረጅም ጊዜ ስለሚሆነው፤ ምናልባትም ስለለሚያጋጥመው፤

https://p.dw.com/p/143rS

  አሥፈሪ ሁኔታ ሊያሳምን የሚችል መላ- ምት ማቅረብ  ይችላሉ ወይ? የሥነ-ቴክኒክና የማኅበራዊ ኑሮ መስተፋጥናዊ ለውጦች ስለወደፊቱ  መጻዔ-ዕድል ለመተንበይ ፤የሳይንቲስቶች፤ መነሻ ምክንያቶች ምን ይሆኑ? በዛሬው ሳይንስና ኅብረተሰብ የምንዳስሰው ጉዳይ ይሆናል።

ወደ ሳይንስ ጠበብት መላ-ምቶች ከማምረታችን በፊት እስቲ ተንባዮችም ሆኑ ሙዋርተኞች ካሉት በጥቂቱ እናንሳ።

እ ጎ አ ታኅሳስ 21 ቀን 2012 ዓ ም፣ በጥንታናውያኑ የማዕከላዊው አሜሪካ ነባር ተወላጆችና የጥንት ስልጣኔ ባለቤቶች፣ ማያዎች ትንቢት መሠረት፣  ዓለም በውሃ  ተጥለቅልቃ ትጠፋና እንደገና አዲስ ህይወት ይጀመራል። ከክርስቶስ ልደት በፊት በ 3114 ዓመተ ዓለም፣ ለመጀመሪያ ጊዜ ፕላኔታችን በውሃ ተጥልቅልቃ የጥፋት ውሃ ሰለባ እንደነበረች የማያዎች ትረካ ያስረዳል። እንደማያዎች እምነት፣ ፍጥረተ ዓለም (ዩኒቨርስ በተለያዩ ዘመናት ፣ ዑደታዊ ጥፋትና  ድኅነት የሚፈራረቅበት መሆኑ እንደተፈጥሮ ህግ የሚታይ ጉዳይ ነው።  ምንም እንኳ፤ የትንቢቱ መያዝ አለመያዝ አነጋጋሪነቱ እንዳለ ቢሆንም፤ የማያዎች ሥልጣኔ፤ የሂሳብና የሥነ ፈለክ ምርምር ችሎታቸው የሚያስደንቅ እንደነበረ  ነው የሚነገረው። የዘመን አቆጣጠራቸው የጨረቃን ዑደት መሠረት ያደረገና ፣ 23 ሴኮንድ ድረስ ፍጹም ትክክለኛነት የሚንጸባርቅበት ነበረ። የማያዎች የቀን መቁጠሪያ ያለፉትን  5000 ዓመታት በትክክል የሚቃኝና፣ ስሌቱ በዚህ ረገድ ያልተዛባ መሆኑ ነው የሚመሠከርለት። የማያዎች ትንቢት፤ ዓለም፣ በጥፋት ውሃ፤ በእሳትና በሚያሳቃዩ አጋንንት መከራ እንደሚደርስበት ነው የሚገልጸው። በአያሌ ዘመናቱ ጥንታዊ ሥልጣኔአቸው ፤ ማያዎች፤  በፒራሚድ ፣ በአብያተ-መንግሥት፣   በሃውልትና በመሳሰለው ሥራቸውም የታወቁ ነበሩ። በታኅስስ ወር 2005 ፤ ወይም  እ ጎ አ ታኅሳስ 21 ቀን 2012 ዓ ም ፣ ማያዎች እንደተነበዩት ዓይነት ጣፋት ይደርሳል ካሉት መካከል እ ጎ አ ከ (1503 -1566) የኖረው መድኃኒት ቀማሚ፤ ሀኪምና ኮከብ ቆጣሪ Michel de Nostredame ወይም ኖስትርዳመስ ይገኝበታል። ኮከብ ቆጠራን አስመልክቶ በስንኞች በደረደረው ግጥም ላይ እ ጎ አ  በ 2003  እና  2022 ዓ ም መካከል  እጅግ አስከፊ የአየር ንብረት  መዛባት እንደሚያጋጥም ተንብዮአል። በ 2012 ዓ ም፤ 3ኛውና የመጨረሻው የዓለም ጦርነት እንደሚካሄድና ፣ ጦርነቱ ካከተመ  በኋላ፣ ፍጹም ሰላም ይሠፍናል ነው የሚለው ፤ ኖስትራዳመስ! በፍጥረተ ዓለም አዳዲስ ክስተቶች አጋጥመው ፣   ለፕላኔታችን በመጀመሪያ ጥፋት፣ በኋላም ድኅነት  እንደሚያስገኙ ያትታል። ያ ከመሆኑ በፊት ግን  መሬት የተፈጥሮ አቅዳዊ ሂደትን ባዛባ መልኩ በራሷ ዛቢያና በፀሐይ ዙሪያ  የምታደርገው መሽከርከር እንደሚናጋ ፤ የሰሃራ ምድረ በዳ ሳይቀር እጅግ አስከፊ ማጥለቅለቅ  እንደሚያጋጥመው፤ የሰሜንና ደቡብ ዋልታዎች የበረዶ ተራሮች ይቀልጣሉ። በደቡብ አውሮፓና ፣ ጥቅጥቅ ያሉ  ደኖች በሚገኙባቸው፣ሞቃት ሃገራት፣ብርቱ የድርቅ አደጋ እንደሚያጋጥም፤ በኮሎኝና ቦን አቋርጦ የሚያልፈው የራይን ወንዝ እንኳ  የሚፈስበትን አቅጣጫ እንደሚለውጥ ፤ በኢጣልያ አዳዲስ ባህሮች እንደሚፈጠሩ፣ ሲሲሊ፣ ማርሴይ አካባቢ ያለው የፈረንሳይ ግዛት፤ እንዲሁም ብሪታንያ እንደሚሰጥሙም  (ውቅያኖስ እንደሚውጣቸው)ነው የኖስትራዳመስ  ትንቢት የሚያወሳው።  

በ 2012 ጎርጎሪዮሳዊው ዓመት ፣ (ማለትም በታኅሳስ ወር 2005) በተፈጥሮና በሰው ሠራሽ ተደራራቢ ጥፋት ቢያጋጥም ፣ ተንባዮች ራስን ለማዳን ፣ በዓለም ዙሪያ 5 አካባቢዎችን የጠቀሱ ሲሆን ከእነዚህም መካከል የኢትዮጵያ አምባዎች ይገኙበታል።

ይህ ሁሉ እንግዲህ ትንበያ ምናልባትም ሟርት ልንለው እንችል ይሆናል።

ሳይንስን እንመርኮዝ የሚሉት ወገኖችስ  ምንድን ነው የሚሉት?

«2020 እፁብ ድንቅ ዘመን ይሆናል፤ በህክምናው ዘርፍ የሚደረጉ ምርምሮች፣ እርጅናን  በእጅጉ ለመግታት የሚያስችል ይሆናል። 100 ዓመት የሆናቸው ሰዎች፤ በዚያ ዕድሜ ፣ህይወትን የሚያጣጥሙ እንጂ የሚያማርሩ አይሆኑም። በ 2010 ( እ ጎ አ)በማስተዋል ይበልጥ  አስተዋይነትን የሚያጎናጽፉ ክኒኖች ገበያ ላይ ይውላሉ፤ በአነዚህ ክኒኖች እርዳታ ሁሉም ምጡቅ ዕውቀት ገብዪ ይሆናል። ባክቴሪያንም ሆነ ተኀዋሲን መፍራት ተገቢ አይሆንም ። እ ጎ አ ከ 2000 ዓ ም አንስቶ ክትባት መሰል፤ መርፌ  መስጠት ተጀምሯል። ማንኛውም በጤንነት ላይ እክል ለመፍጠር የሚዳዳውን ሁሉ፤ በዘመናዊ ህክምናና  መድኃኒት አስቀድሞ መከላከልም ሆነ ማስወገድ አዳጋች አይሆንም።

ተክሌ የኋላ

ሒሩት መለሰ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ