1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የ2010-የመልካም ተስፋ ምኞትና የጅምሩ እዉነት

ሰኞ፣ ታኅሣሥ 26 2002

ሶማሊያ እንደተተራመሰች፥ ኢራኖች-በምርጫ ዉጤት-እርስ በራሳቸዉ፥በኑክሌር ሰበብ ከአለም እንደተፋጠጡ፥የፍልጤም እስራኤሎች ጠብ መላ እንዳጣ፥ የባለኢንዱስትሪዉ አለም የሙቀት ልቀት ንረት እየተወራበት በረዶ-እንዳለበሰዉ፥ዙማ ለአምስተኛ ጊዜ የተሞሸሩበት---

https://p.dw.com/p/LKnm
ምስል DW/AP/ullstein-bild

04 01 12

በጎርጎሮሳዉያኑ 2010 ዋዜማና መበቻ የተሰማዉ የቤኔዲክት አስራስድስተኛ ፀሎት፣ የኦባማ ተስፋ፣ የሜርክል ምክር፣ የሳፓቴሮ እቅድ፣የዙማ ጥሪ የሌሎች ብዙዎች ብዙ ግን ተመሳሳይ ፀሎት ምኞት መልዕክት ባዲሱ አመት እንዲሰምር የማይፀልይ፣ የማይመኝ የለም-ካለም ለአለም ኢምንት ነዉ። ከአፍቃኒታን እስከ ሶማሊያ፣ ከኢራቅ እስከ ፓኪስታን፣ ከእስራኤል-ፍልስጤም እስከየመን ጦርነት፣ግጭት፣ሽብርን፣ ከኢራን-እስከ በርማ ዉዝግብን፣ ከአዉሮጳ እስከ አሜሪካ የምጣኔ ሐብት ድቀትን፣ ከአፍሪቃ እስከ እስያ ረሐብ አደጋን የወረሰዉ አመት ለፀሎት፣ ምኞቱ ስምረት ጥሩ መደላድል ማጣቱ፣ ጅምሩ አለማማሩ ነዉ ቀቢፀ-ተስፋዉ።እንዴት? ላፍታ አብረን እንጠይቅ።

Papst Benedikt Neujahr Rede 2010
ቤኔዲግት VIምስል AP

የሮማ ካቶሊካዊት ቤተ-ክርስቲያን ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ቤኔዲክት አስራ-ስድስተኛ እንደ መንፈሳዊ አባት ለሠላም፣ ለሰዉ ልጅ እኩልነት ፅናት ሲፀልዩ፥ እንደ ምድራዊ ምሁር የግጭት ፣ ጦርነት፣የዘረኝነት፣ የስግብግብነት ምክንያት-ዉጤቶችን እየተነተኑ፣ ሰዉ ከእኩይ ምግባራት እንዲታቀብ እንደአዛዉንት መከሩ።አርብ።

ቤኔዲክት አስራ-ስድስተኛ እንዳሉት የጦርነት፣ የአመፅ፣ የድሕነትና የተፈጥሮ ሐብት ጥፋት ጥቁር ጨለማ ባጠላበት አለም የሰዉ ልጅ ሠላምን አጥብቆ ይሻል።ሰላም የሚፀናዉ በፖለቲከኞች ስምምነት፣ ፍቃድ ወይም ቸሮታ ሳይሆን በፈጣሪ ነዉ።

የሰላም መሠረቱ ደግሞ ቤተሰብ ነዉ።ቤተሰብ እንዲኖር፣ ኖሮ-ለሰላም መሠረት እንዲጥል ፅንስን ማስወረድ መከልከል አለበት። ዉርጃ የሕዝብ ቁጥር ንረትን ለመቆጣጠር በዉጤቱም ድህነትን ለመቀነስ ይረዳል የሚለዉን የአንዳድ ፖለቲከኞችና የመብት ተሟጋቾችን መከራከሪያ ነጥብ ጳጳሱ መረጃ እያጠቀሱ አጣጥለዉ ነዉ-የተቹት።«የድሕነት መሠረቱ የተወሰነ የሕብረተሰብ ክፍል ሐብት ማጋበሱ ነዉ።»እንደሳቸዉ።

በጥንት በጠዋትዋቷ ካቶሊካዊት ሐገር ስጳኝ ዉስጥ አንዲት እርጉዝ በሕጋዊ መንገድ ፅንስ ማስወረድ የምትችለዉ ተደፈራ የፀነሰች ወይም ፅንሱ ለጤናዋ የሚያሰጋ ከሆነ ብቻ ነዉ።

በስልጣን ላይ ያለዉ የጠቅላይ ሚንስትር ሆሴ ልዊስ ሮድሪጎስ ሳፓቶሬ ሶሻሊስታዊ ፓርቲ ነባሩን ሕግ ሽሮ ፀናሾች ሃያ-ሁለት ሳምንት ያልሞላዉን ፅንስ የማወስረድ መብት እንዲኖራቸዉ ሁለቴ አዲስ ሕግ አስረቅቆ ለሐገሪቱ ምክር ቤት አቅርቦ ነበር።ከአንድ ቢሊዮን የሚበልጠዉ የአለም የካቶሊክ ክርስቲያን የመንፈስ አባት ዉርጃን፣ ስግብግብነትን ባወገዙበት ዕለት-አርብ የሳፓቶሬዋ ስጳኝ ለስድስት ወር የሚቆየዉን የአዉሮጳ ሕብረትን የፕሬዝዳትነት ሥልጣን ተረከበች።

ሳፓቶሬም መልዕክት ነበራቸዉ።ዕቅዳቸዉ።

«እስጳኝ የአዉሮጳ ሕብረት የፕሬዝዳትነት ሥልጣንዋ በሚቆይበት በስድስቱ ወራት ዉስጥ አዉሮጳን እናጠናክራለን።እስጳኝ በአዉሮጳና በአለም ያላትን ሚና እናጠናክራለን።ምጣኔ ሐብቱ እንዲያንሰራራ፣ ለወደፊቷ አዉሮጳ አዳዲስ ፈጠራዎች የሚበረታታ፥ የተረጋጋ፥ በጣም በተቀራረበችዉ አለም ጠንካራ ተፎካካሪ ምጣኔ ሐብት እንዲኖራት እንጥራለን።ይሕ ነዉ ግባችን።»

የድሕነት መሠረቱ-ሐብት ማከማቸት ነዉ-ይላሉ ቤኔዲግት አስራ-ስድስተኛ፥ ሳፓቴሮ-ለአዉሮጳ ሐብታምነት ይጥራሉ።የሳፓቴሮ መልዕክት የተሰማ ዕለት የአይስላንድ ባንኮች ያከሰሩት የብሪታንያና የኔዘርላንድስ ዜጎች ተቀማጭ ገንዘብ ከሐገረሪቱ ካዝና እንዲከፈል ምክር ቤቷ ወሰነ። አምስት ቢሊዮን ዶላር።ምክንያት አይስላንድ የአዉሮጳ ሕብረት አባል ለመሆን ያላት ምኞት-እንዳይደናቀፍ።በሳልስቱ ሃያ-ሰወስት ከመቶ የሚበልጠዉ ሕዝብ የምክር ቤቱን ዉሳኔ እንቢኝ አለ።ሕዝቡን ካስተባበሩት አንዱ ምክንያቱን ይናገራሉ።

«የመከራከሪያ ነጥባችንን ለፕሬዝዳቱ ማቅረብ ችለናል።በዚሁ አጋጣሚ ፕሬዝዳቱ ሕጉን እንዳያፀድቁት የሚጠይቀዉን ከመራጩ ሕዝብ ሩብ ያሕሉ የፈረመበትን አቤቱታ አስረክበናል።አይስላድ (ለከሰረዉ) የቁጠባ ገንዘብ እንድትከፍል የተወሰነዉ የወለድ መጠን የጠቅላላ ሐገሪቱን የስድስት ወር የጤና አገልግሎት የሚሸፍን ነዉ።»

Spanien EU Ratsvorsitz 2010
ሳፓቶሬምስል AP

አፍቃኒስታን የዘመቱ ሰባት-የአሜሪካ ሰላዮች የተገደሉበት ያለፈዉ አመት የመጨረሻ ወር ለአሜሪካኖች አሳዛኝ ከመሆኑ እኩል አስደሳችም ነበር።ኢራቅ የሠፈረዉ የአሜሪካ ጦር ከሁለት ሺሕ ሰወስት ጀምሮ-አንድም ወታደር ሳይገደልበት ወር የደፈነዉ በሁለት ሺ ዘጠኙ መጨረሻ ነበር።ታሕሳስ።

አልቃኢዳ ያዘመተዉ ናይጄሪያዉ ወጣት-የመንገደኞች አዉሮፕላን ለማጋየት ያደረገዉ ሙከራ መክሸፉ፥ የአሜሪካ ምጣኔ ሐብት በጥቂቱም ቢሆን ማንሰራራቱ ፕሬዝዳት ባራክ ኦባማ መጪዉን አመት በበጎ ተስፋ እንዲያማትሩ ምክንያት አድርገዉት ነበር።

«በመላዉ ሐገሪቱ የሚኖሩ አሜሪካዉያን ከቤተ-ሰብ ወዳጆቻቸዉ ጋር በተሰበሰቡት በዚሕ ምሽት የደስታና የጤና አዲስ አመት እንዲሆንላችሁ እመኛለሁ።ያንዱን አመት ፍፃሜ የሌላዉን አመት ጅምር የምናከብርበት ይሕ ወቅት ምንግዜም የተስፋ ጊዜ ነዉ።ሁለት ሺሕ ዘጠኝ ለብዙዉ አሜሪካዊ አስቸጋሪ አመት እንደነበረ ሁሉ አመቱን መለስ ብለን ስናስታዉስ ከፊታችን ብሩሕ ዕለታት እንዳሉ በማሰብ መሆን አለበት።»

የኦባማ ብሩሕ ዕለታት-አርብ አንድ ሲሉ አሜሪካ ለፀረ-ሽብር ዉጊያ በቢሊዮን የሚቆጠር ዶላር የምታንቆረቁርላት ፓኪስታን-በሽብር ጎዙዋ መቀጠሏን አስመሰከረች።በሐገሪቱ ሰሜን-ምዕራብ ግዛት አንድ አጥፍቶ ጠፊ መኪና ላይ ያጠመደዉን ቦምብ ኳስ ሜዳ በተሰበሰበ ሕዝብ መሐል አፈንድቶ-ለመቶ ሁለት ፈሪ ገደለ።

የፕሬዝዳት ኦባማ የአዲስ አመት የብሩሕ ተስፋ መልዕክት አስገምግሞ ሳያበቃ-ሁለት ሺሕ አስር የሽብር-ፀረ-ሽብሩን የዉጊያ ቀጠና ከኢራቅ፥ ከአቅፍቃኒስታን ከፓኪስታን የመን ማሻገሩ እንደምይቀር የአሜሪካዉ ጦር የማዕከላዊ ዕዝ አዛዥ ጄኔራል ዳቪድ ፔትሮዉስ አስታወቁ።

«አል-ቃኢዳ ሁል ጊዜ መሠረት የሚጥሉበትን ሥፍራ እንደፈለጉ ነዉ።ከጥቂት አመታት በፊት ያኔ እኔ ገና ኢራቅ እያለሁ የመን ዉስጥ የአል-ቃኢዳ ሕዋስ በማቀጥቀጥ ላይ እንደነበረ እናዉቅ ነበር።እርግጥ የሥለላና የመረጃ ልዉዉጥ ነበር።የየመን የሥለላ ምንጮችም በጣም አስተማማኞች ናቸዉ።የሚደረጉ እንቅስቃሴዎች ግን ነበሩ።የከሸፈዉ የአዉሮፕላን ጥቃት የእንቅስቃሴዎቹ አንድ ዉጤት ነዉ።»

ጄኔራል ፔትሮዉስ የመን የመሸጉ-የአል-ቃኢዳ አባላትን ሥለሚወጉበት ሥልት ሰነዓ ዉስጥ ከየመን ባለሥልጣናት ጋር መክረዉ ሲመለሱ፥ ካቡል-ላይ ሙስናን የሚዋጋ፥ አደንዛዥ ዕፅን የሚያጠፋ፥ ከሁሉም በላይ አል-ቃኢዳና ታሊባንን የሚዋጋ ጠንካራ መንግሥት ይመሰርታሉ ተብለዉ የተጠበቁት ሐሚድ ካርዛይ ከምክር ቤቱ ጋር መላተማቸዉ ተሰማ።

ካርዛይ ላዲሱ ካቢኔ ካጩቸዉ ሃያ-አራት ሚንስትሮች ምክር ቤቱ የአስራ-ሰባቱን ሹመት ዉድቅ ማድረጉ በአፍቃኒስታን የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ልዩ መልዕክተኛ ካይ ኢዴ እንዳሉት ለአፍቃኒስታን ታላቅ ፖለቲካዊ ድቀት፥ ለአለም አቀፉ ማሕበረሰብ ጥረት ደግሞ አፍራሽ ነዉ።

የጀርመንዋ መራሒተ መንግሥት የአዲስ አመት መልክት በርግጥ ጥንቃቄ የተሞላበት ነበር።

USA Gesundheitsrefom Obama Biden
ኦባማና ምክትላቸዉምስል AP

«ያለፈዉ አመት በዘመናችን ታላቅ አለም አቀፍ የምጣኔ ሐብት ድቀት የታየበት ነበር።ሁለት ሺሕ አስር ይሕን ድቀት ማስወገድ መቻል-አለመቻላችን የሚወሰንበት ነዉ።ደጋግሜ የምለዉ ነዉ።የምጣኔ ሐብቱ ድቀት የሚጠገንበት ጊዜ እንዲሕ በቀላሉ ያልፋል ብለን መጠበቅ የለብንም።በአዲሱ አመት ሰዎች የተሻለ ነገር ከማየታቸዉ በፊት ከባዱን መጋፈጥ አለባቸዉ።»

የሜርክል መልዕክት የአዉሮጳን ትልቅ ኢኮኖሚ የሚዘዉረዉን የጀርመን ሕዝብ ምናልባትም ብዙዉን አዉሮጳዊ ቀበቶዉን ጠበቅ እንዲያደርግ አነሳስቶ ሳያበቃ-የነባሪቱ የአዉሮጳ ሐያል የብሪታንያ ጠቅላይ ሚንስትር ጎርደን ብራዉን አዲሱ አመት አይደለም-አዲሱ አስርትም-«የገዳይ ፅንፈኛ ሙስሊሞች ርዕዮተ-አለም» ያሉት አስተሰሰብ የምናዋጋበት ነዉ አሉ።እሁድ።

Merkel nah Neujahrsansprache 2009/2010
ሜርክልምስል AP

የዚያኑ እለት ሰነዓ የሚገኙት የብሪታንያና የዩናይትድ ስቴትስ ኤምባሴዎች የአሸባሪዎች ጥቃትን ፍራቻ ተዘጉ።አመቱም ሰወስተኛ ቀኑን ጨረሸ።የደቡብ አፍሪቃ ፕሬዝዳት ያኮብ ዙማ-ባዲስ አመት መልዕታቸዉ አፍሪቃም-ሐገራቸዉም ለመጀመሪያ ጊዜ ለሚያስተናግዱት ለአለም እግር ኳስ ግጥሚያ ስምረት ሕዝባቸዉ እንዲተባበር ነዉ-የጠየቁት።

-----------------------------------------------------------------------

ሶማሊያ እንደተተራመሰች፥ ኢራኖች-በምርጫ ዉጤት-እርስ በራሳቸዉ፥በኑክሌር ሰበብ ከአለም እንደተፋጠጡ፥የፍልጤም እስራኤሎች ጠብ መላ እንዳጣ፥ የባለኢንዱስትሪዉ አለም የሙቀት ልቀት ንረት እየተወራበት በረዶ-እንዳለበሰዉ፥ዙማ ለአምስተኛ ጊዜ የተሞሸሩበት፥ የአሜሪካ ጦር ከኢራቅ የሚወጣበት፥ የኦባማ አመራር የሚፈተነበት፥የብራዋን ዘመነ-ሥልጣን የሚበየንበት 2010-አራት ቀን ተነሳለት።ነጋሽ መሐመድ ነኝ ቸር ያሰማን።

Dw,Agenturen

Negash Mohammed

Shewaye Legesse