1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ይነጥፋል የተባለው የስዑዲ ሃብት

ሐሙስ፣ ታኅሣሥ 7 2008

የሳውዲ አረብያ የተፈጥሮ ሃብት፣ ሃገሪቱን ባለፀጋ እና ተሰሚነት ያላት አገር እንድትሆን አድርጓል ። ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ግን የሳውዲ የሃብት ምንጭ የሆነው የነዳጅ ዘይት ዋጋ መውረዱና የየመኑ ጦርነት እንዲሁም በአካባቢው ከኢራን ጋር የሚካሄደው ሽኩቻ እስካሁን በገንዘብ አቅም የያዘችውን ቦታ ሳያሳጣት አይቀርም ።

https://p.dw.com/p/1HPPA
Saudi Arabien Gespräche 136th Golf Kooperationsrat GCC Themen Öl Syrien Yemen Salman bin Abdulaziz Sheikh Mohammed bin Rashid al-Maktoum
ምስል Getty Images/AFP/Fayez Nureldine

[No title]

በዓለም የገንዘብ ድርጅት ትንበያም የሃገሪቱ የሃብት ክምችት ከጥቂት ዓመታት በኋላ መንጠፍ ይጀምራል። የዶቼ ቬለውን የኒኮላስ ማርቲንን ዘገባ ኂሩት መለሰ አጠናቅራዋለች ።
ባለፀጋዋ ሳውዲ አረብያ በርዝመት ከዓለም የመጀመሪያውን ደረጃ ይይዛል የተባለ ህንፃ እየገነባች ነው ።ቁመቱ 1 ኪሎ ሜትር ይደርሳል የተባለው የዚህ ህንፃ ግንባታ ከ3 ዓመት በኋላ ይጠናቀቃል ተብሎ ይጠበቃል ። የሳውዲ አረቢያ መሪዎች ሃገራቸው የተከበረች ዘመናዊና በሁሉም መስክ የላቀ ደረጃን የምትይዝ ሃገር እንድትሆን ነው የሚፈልጉት።ሆኖም መሪዎቿ ለሃገራቸው የሚመኙት ገፅታ ከአሁኑ መሰነጣጠቅ ጀምሯል ይላል የኒኮላስ ማርቲን ዘገባ። ባለፈው ጥቅምት ዓለም ዓቀፉ የገንዘብ ድርጅት በምህፃሩ IMF እንደተነበየው የሳውዲ አረብያ ንጉሳዊ አገዛዝ አሁን እንደሚያደርገው ገንዘብ ማውጣቱን መቀጠል የሚችለው ለሚቀጥሉት አምስት ዓመታት ብቻ ነው ። ከዚያ በኋላ እንደ IMF ሃብቷ እየተመናመነ መሄዱ አይቀርም ። ይህም በአንድ በኩል ከነዳጅ ዘይት ዋጋ መቀነስ ጋር የተጎዳኘ መሆኑ ይገለፃል ። አንድ ዓመት ለሚጠጋ ጊዜ የአንድ በርሜል ድፍድፍ ነዳጅ ዘይት ዋጋ ከ40 እስከ 50 ዶላር በሚደርስ ዋጋ ነበር የሚሸጠው ። እንዲያውም ከ6 ዓመታት ወዲህ ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ ከ40 ዶላር በታች የወረደበትም ጊዜ ነበር ። በነዳጅ ዋጋ መቀነስ ምክንያት ለኤኮኖሚ ክስረት የተዳረገችው ሳውዲ አረቢያ የነዳጅ ዋጋ እስኪጨምር ድረስ መጠበቅ እንደሌለባት በያዝነው በታህሳስ ወር የወጣ አንድ ጥናት አመልክቷል ። ከዚያ ይልቅ ጥናቱ ሃገሪቱ በተቻለ ፍጥነት የተሃድሶ እርምጃዎችን እንድትወስድ ሃሳብ ያቀርባል ።እንደ ጥናቱ እስካሁን ሲሠራበት የቆየው ውሃ የማጠጣት ዓይነት አሠራር የትም የሚያደርስ ሆኖ አልተገኘም ።ንጉሣዊው አገዛዝ የአገልግሎት ሰጭና የፍጆታ ዘርፎችን ይደጉማል። በዚህ ረገድ የኃይል የጋዝና የውሐ አገልግሎት ክፍያዎች ዝቅተኛ ናቸው ።መንግሥት የገቢ ግብር አይቀበልም ። በዚህ የተነሳም የሳውዲ ዜጎች አባካኝ ሆነዋል ይላሉ የውጭ ጉዳዮችን የሚያጠናው የጀርመን ማህበረሰብ በተባለው ተቋም የምሥራቅ አፍሪቃ ጉዳዮች አጥኚ ዜባስቲያን ዞንስ ። ሆኖም በርሳቸው አስተያየት ድንገተኛ ለውጥን ተግባራዊ ማድረጉ በፖለቲካው አካሄድ የሚቻል አይደለም ።
« ሙሉ በሙሉ የገንዘብ ድጋፍ ማግኘትን በለመደ ማህበረሰብ ይህን መሰሉን እርምጃ መወሰድ አስቸጋሪና ጎጂ ነው የሚሆነው »
በሳውዲ አረብያ የሥራ አጡ ቁጥር 6 ከመቶ ነው ። እድሜያቸው ከ26 ዓመት በታች ለሆኑ ዜጎች ደግሞ ሁኔታዎች የባሱ ናቸው ። 30 በመቶ ያህሉ ሥራ የላቸውም ።ይህም በዚህ የህብረተሰብ ክፍል ውስጥ አለመረጋጋትን አስከትሏል ይላሉ ዞንስ ።
«በየዓመቱ ወደ 100 ሺህ የሚሆኑ ወጣቶች ከዩኒቨርስቲዎች ይመረቃሉ ።ሥራ ግን አያገኙም ። ምክንያቱ የሚያገኙት ገንዘብ ትንሽ ስለሆነ ወይ በግሉ ዘርፍ ገብተው መሥራት አይፈልጉም ፤ አለያም ሥራ በሌለባቸው በመንግሥት መሥሪያ ቤቶች መቀጠር አይሹም ። ይህ የሆነው በሚያገኙት ገንዘብ ማነስ ብቻ ሳይሆን በማህበራዊ ተፅእኖዎችም ምክንያት ነው »
የአካባቢው ኃያል የምትባለው ሳውዲ አረብያ ከደቡባዊ ድንበሯ ባሻገር የመን ውስጥ ውጊያ የሚያካሂዱትን የሁቱ አማፅያን እየወጋች ነው ።ከሰሜናዊ ድንበሯ ተሻግራም ኢራን በአካባቢው የምታሳድረውን ተፅእኖ ለመከላከል እየጣረች ነው ።ሃገሪቱ ትልቅ ቦታ የምትሰጠው የውክልና ጦርነት ደግሞ ሶሪያ እየተካሄደ ነው ። የመን አሁን ወታደር ብቻ ሳይሆን ብዙ ገንዘብም እያስወጣች ነው ። ነው ።ሳውዲ አረብያ ለሶሪያው ጦርነት ብቻ 100 ቢሊዮን ዶላር የሚገመት ገንዘብ አፍሳለች።
ስለዚህ ይላሉ ዞንስ ሳውዲ አረብያ ከአሁን በኋላ አቅምዋን ያገናዘበ እርምጃ መውሰድ አለባት ።
«በቀጣይነት መወሰድ ያለበት እርምጃ ሃገሪቱ በአካባቢው የምትጫወተውን ሚና መቀነስ እና ገቢራዊ ሊሆን የሚችል ተጨባጭን ሁኔታ ያገነዘበ ፖሊሲ መከተል ነው ።»

Saudi-Arabien König Salman
የስዑዲ ንጉስ ሳልማንምስል picture-alliance/dpa/O. Douliery
Karte Saudi-Arabien englisch
ምስል DW

ኂሩት መለሰ

አዜብ ታደሰ