1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል
ትምህርት

የተፈታኞች አስተያየት

ዓርብ፣ ነሐሴ 5 2009

የ12ኛ ክፍል የከፍተኛ ትምህርት ተቋም መግቢያ ፈተና ውጤት  ባለፈው ሳምንት ይፋ ሆኗል። ያነጋገርናቸው ተማሪዎች እንደገለፁልን፤ ውጤቱ እንደጠበቁት አልነበረም።  የዩኒቨርስቲ መግቢያ ውጤት ገና አልተቆረጠም።

https://p.dw.com/p/2i57Q
Schüler Lernen Mädchen Prüfung Klausur
ምስል Fotolia/Moritz Wussow

የዘንድሮው የ12ኛ ክፍል  ፈተና ውጤት ሐምሌ 28 ቀን 2009 ዓ.ም ይፋ መሆኑን የአገር አቀፍ የትምህርት ምዘናና ፈተናዎች ኤጀንሲ አስታውቋል። በኤጀንሲው መረጃም መሠረት 285,628 ተማሪዎች ፈተናውን ወስደዋል። በአፋር ክልል ከሚገኝ አንድ ትምህርት ቤት  አንድ ስሙን ለደህንነቱ ስንል መግለፅ ያልፈለግነው የዘንድሮ ተፈታኝ እንደነገረን ከትምህርት ቤቱ ያለፉት ሁለት ተማሪዎች ቢሆኑ ነው። እሱም ራሱን ከወደቁት ተርታ ይመድባል። የፈተናዎቹን ጥያቄዎች አያስታውስም። ፈተናው ከባድ ወይም ቀላል ነበርም ሊል አይችልም። ምክንያቱም እሱ እንደነገረን ፈተናውን የመለሰው ኮርጆ ነው። እንደ ወጣቱ ገለፃ፤ ተምሮ ባገኘው እውቀት ፈተናውን እንደማያልፍ ከመጀመሪያው ያውቅ ነበር። ስለሆነም ለተማሪው መውደቅ ተወቃሾቹ ሌሎች ናቸው።
የአገር አቀፍ የትምህርት ምዘናና ፈተናዎች ኤጀንሲ የህዝብ ግንኙነት እና ኮሚኒኬሽን ዳይሬክቶሬት ዳሬክተር አቶ ረዲ ሽፋ ፈፅሞ አስቀድሞ የወጣ መልስ እንዳልነበር ለዶይቸ ቬለ ተናግረዋል። እንደ ሃላፊው ከኩረጃ ጋር በተያያዘ በደረሰ ጥቆማ መሠረት ተማሪዎች ላይ ርምጃ ተወስዷል። አቶ ረዲ ርምጃ የተወሰደባቸው ተማሪዎች ከአፋር ክልል ስለመሆናቸው ግን መረጃ የላቸውም።  ሌሎች ያነጋገርናቸው ተፈታኞች እንደገለፁልንም የዘንድሮው ቁጥጥር ከፍተኛ ነበር። እንዲሁ ከአፋር ክልል እንደሆነ የገለጸልን አህመድ መሀመድ የዘንድሮውን ፈተና የሰራው በራሱ ነው። አህመድ ተፈትኖ ያገኘው ውጤት 265 ነው። ውጤቱ ምናልባትም ለማለፍ አያበቃውም። 
አቶ ረዲ እንገለጹልን የዩንቨርስቲው መግቢያው ውጤት ገና አልተወሰነም። ይፋ የሚሆነው ከአንድ አስር ቀን በኋላ ነው።  እስከዛው ማለፍ መውደቃቸውን በውሉ የማያውቁት ተማሪዎች በትዕግስት መጠበቅ ግድ ይላቸዋል። እንደ አቶ ረዲ ውሳኔው አልዘገየም። 
ሌላው የ12ኛ ክፍል ተፈታኝ የጅጅጋ ነዋሪ የሆነው ወጣት ዳንኤል ነው። እሱ ፈተናውን በወሰደበት ትምህርት ቤት ቁጥጥሩ ከፍተኛ ነበር ይላል።ዳንኤል ያገኘው ውጤቱ ዮንቨርስቲ ያስገባኛል ብሎ ያምናል። ውጤቱ 315 ነው። ካለፈ ምህንድስና ማጥናት ይፈልጋል። 
ዘንድሮ ለፈተና ከቀረቡት 126, 658 ሴት ተማሪዎች መካከል አንዷ የሆነችው ሰዓዳም ፈተናውን በራሷ ነው  የሰራችው፤ ኩረጃማ ድሮ ቀረ ትላለች። እንደ እሷ እምነት ያገኘችው 310 ነጥብ ከፍተኛ ተቋም ገብቶ ለመማር አያበቃትም። ሰዓዳ ከዚህ በላይ ጠብቃ ነበር።
ነጂብ ሁሴን እንደ ሰዓዳ የአዲስ አበባ ነዋሪና የዘንድሮ የ12ኛ ክፍል ተፈታኝ ነው። እሱም በተፈተነበት ትምህርት ቤት ከፍተኛ ቁጥጥር ነበር። ይሁንና መኮረጅ ከተፈለገ መንገድ ነበር ይላል። እሱም የኩረጃ መልስ ከፈተናው አስቀድሞ አግኝቶ ነበር።  ለፈተና ቀርቦ ጥያቄውን ከመልሱ ሲያስተያይ ስላልተጣጣመለት ያገኘውን መልስ ትቶ ፈተናውን በራሱ ለመመለስ ወስኖ ተፈትኗል። ያገኘው ነጥብ 340 ነው።  በውጤቱ ደስተኛ አይደለም። ነጂብ ጓደኞቹን ለመውደቅ የዳረጋቸው ተገኘ ያሉትን መልስ ይዘው ገብተው በመፈተናቸው ነው ብሎ ያምናል። 
ከአነጋገርናቸው የ12ኛ ክፍል ተፈታኞች መካከል ከፍተኛውን ነጥብ ያገኘው ዳዊት ነው። 360 ብሎናል። ዳዊት በአማራ ክልል ሰሜን ወሎ ራያ ቆቦ አካባቢ ነው የተፈተነው። በውጤቱ ብዙም ደስተኛ አይደለም። ዳዊት ህክምና ማጥናት ይፈልጋል። ይሁንና ያገኘው 360 ነጥብ ለዛ መብቃቱን እንደ ሌሎች ተማሪዎች ለጊዜው አያውቅም። 

12.06.2013 DW Online Karten Basis Äthiopien Englisch
የዘንድሮው የ12ኛ ክፍል  ፈተና ውጤት ሐምሌ 28 ቀን 2009 ዓ.ም ይፋ ሆኗል።
Schüler in einem Dorf in Äthiopien
የኢትዮጵያ ትምህርት ጥራት ላይ ጉድለት እንዳለ በተደጋጋሚ ተወስቷል።ምስል picture-alliance/ dpa
Symbolbild Spickzettel
የዘንድሮው ፈተና በከፍተኛ ቁጥጥር ቢካሄድም ኮረጅን የሚሉ አልጠፉም።ምስል Fotolia/lassedesignen


ልደት አበበ 
ሂሩት መለሰ